ካዕባ የእስልምና ጣዖት!

ካዕባ የእስልምና ጣዖት!

“ለስላሳና እርጥበታማ የሆነው ኃጢአተኛው ሰው አፉን ከእርሱ ላይ እንዳያነሳ ነው፡፡ ነቢዩ አላህ በምድር ላይ ያስቀመጠው ቃል ኪዳን እንደሆነ እንዲያውጅ ያደረገው ይህ ነው፡፡” ~ ኢብን ጁቤይር

ስለ እስልምና ዕውቀት የሌለውን ሰው “ስለ እስልምና ምን ታውቃለህ?” ብላችሁ ብትጠይቁት ወደዚያ ሰው አእምሮ ቀድሞ የሚመጣው በየቴሌቪዥን መስኮቶች የተመለከተው በርካታ ሙስሊሞች የሚዞሩትና የሚስሙት ጥቁር ድንጋይ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች ሙስሊሞች በመካ የሚገኘውን ጥቁር ድንጋይ ያመልካሉ ሲሉ ይደመጣሉ፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ይህንን ይቃወማሉ፡፡ ይሁን እንጂ እውነታዎችን ስናገናዝብ የመጀመሪያዎቹ ትክክል መሆናቸው ይገለጥልናል፡፡

ሙስሊሞች ምንም እንኳን “ካዕባን አናመልክም” ቢሉም እውነታው ግን ከዚህ በተቃራኒ ነው፡፡ አምልኮ ሲባል የአንደበት ንግግር ብቻ እንዳልሆነ ማወቅ አስፈላጊ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል አንድ ሰው አንድን አካል እንደሚያመልክ በአንደበቱ እየተናገረ በተግባሩ ላያመልከው ይችላል፡፡ በተጻራሪው ደግሞ አንድን አካል እንደማያመልክ በአንደበቱ እየተናገረ በተግባሩ ሊያመልክ ይችላል፡፡ ልክ እንደዚሁ ሙስሊሞች ካዕባን አናመልከውም ማለታቸው ላለማምለካቸው ማረጋገጫ ሊሆን አይችልም፡፡ መታየት ያለበት ተግባራቸው ነው፡፡ ሙስሊም ወገኖች ካዕባን የማያመልኩት ከሆነ አለማምለካቸውን በተግባራቸው ማሳየት ያስፈልጋቸዋል፡፡ ካዕባ በእስልምና ያለውን ቦታ ከማየታችን በፊት ካዕባ ምን እንደሆነ እንመልከት፡፡

ካዕባ በቅድመ-እስልምና ጊዜ

ከእስልምና በፊት ዓረቦች ድንጋዮችን ያመልኩ ነበር፡፡ አንድ ድንጋይ እያመለኩ ከዚያ የተሻለና ያማረ ድንጋይ ካገኙ አዲሱን ድንጋይ ያመልኩ ነበር፡፡

“አቡ ራጃ አል-ዑታሪደ እንዳወሳው፡- ከዚህ ቀደም ድንጋይ እናመልክ ነበር፡፡ እናመልክ ከነበረው የተሻለ ድንጋይ ካገኘን የመጀመሪያውን ትተን አዲሱን እናመልክ ነበር፡፡ ነገር ግን ድንጋይ ካላገኘን ከመሬት አፈር እንሰበስብ ና በበግ ወተት ለውሰን እንዞረው ነበር፡፡ …” (ሳሂህ አን-ቡኻሪ ቅፅ 5 መጽሐፍ 59 ሐዲስ 661)

በቅድመ እስልምና ዘመን ይመለኩ የነበሩ ድንጋዮች “ካዕባ” ተብለው ይጠሩ ነበር፡፡

“ጃሪር ቢን አብደላህ እንዳስተላለፈው፡- በቅድመ እስልምና ዘመን ዙል ኻላሳ የተባለ ቤት ነበር፡፡ በሌላኛው አጠራሩ አል-ካዕባ አል-የመኒያ (የየመን ካዕባ) ወይም ካዕባ አሽ-ሻሚያ ተብሎ ይጠራል፡፡” (ሳሂህ አል-ቡኻሪ 3823)

ይህ ብቻ አይደለም፡፡ ካዕባ በቅድመ እስልምና ዘመን የመራባት (ልጅን የሚሰጥ) አምላክ ተደርጎ ስለሚታመን ሰዎች በዙሪያው እርቃናቸውን ሰባት ጊዜ ይዞሩ ነበር፡፡ ይህንንም በሚከተለው ሐዲስ እናረጋግጣን፡፡

“ሒሻም ከአባቱ ሰምቶ እንዳወራው ቁረይሽ የሆኑ ሑሞች ሲቀሩ መላው ዓረቦችና ዘሮቻቸው ቤቱን ራቁታቸውን ይዞሩ ነበር፡፡ ሑሞች ልብስ እስከሚሰጧቸው ድረስ እርቃናቸውን ይዞሩት ነበር፡፡ …” (ሳሂህ ሙስሊም መጽሐፍ 15 ሐዲስ 164 ወይም 1219)

“ኢብን አባስ እንዲህ አለ፡- ሴቶች ካዕባ እርቃናቸውን ይዞሩ ነበር፡፡” (ሱናን አን-ናሳኢ ቅፅ 3 መጽሐፍ 24 ሐዲስ 2959)

“አቡ ሁረይራ እንዲህ አለ፡- በሐጅ ጊዜ (አቡ በከር የሐጅ መሪ ነበር) እኔን በናህር ቀን ከአዋጅ ነጋሪዎች ጋር ወደ ሚና ለማወጅ ላከኝ፡፡ “ከዛሬ በኋላ ማንም ጣዖት አምላኪ ሐጅ እንዳያደርግ፡፡ ደግሞም ማንም ሰው በካዕባ ዙሪያ እርቃኑን ታዋፍ እንዳያደርግ” ብለን አወጅን፡፡” (ሳሂህ አል-ቡኻሪ ቅፅ 6 መጽሐፍ 60 ሐዲስ 178)

ጉዳዩ ከዚህም የከፋ ነው፡፡ እንደ እስልምና ምሁራን ከሆነ ካዕባ ከሰማይ ሲወርድ እንደ ወተት ነጭ ነበር፡፡ ልጅ እንዲሰጣቸው ለመማፀን በዙሪያው ሰባት ጊዜ የሚዞሩ ሴቶች የወር አበባ ደማቸውን ይቀቡት ስለነበረ አሁን የምናየውን ጥቁረት እንደጠቆረ የሚናገሩ ሊቃውንትም አልጠፉም፡፡ (ተፍሲር አል-ሐዊ ሱራ አል-በቀራ 127-129)

ካዕባ ከ300 ጣዖታት አንዱ ነበር!

ነቢዩ ሙሐመድ 622 ዓ.ም የገዛ ወገኖቼ አሳድደውኛል ብሎ ወደ መዲና ከተጓዘ በኋላ በመዲና 7 ዓመት ቆይቶ በመካ የሚገኙ ቁረይሾችን አጥቅቶ መካን ሲቆጣጠር በከተማዋ ውስጥ 360 ጣዖታት ነበሩ፡፡ ከእነዚያም መካከል አንዱ ካዕባ ነበር፡፡

“አብደላህ ኢብን መስዑድ እንዳወሳው ነቢዩ ወደ መካ በገባ ጊዜ ሦስት መቶ ስልሳ ጣዖታት በካዕባ ዙሪያ ነበሩ፡፡ በእጁ በያዘው ዱላ ጣዖታቱን እየወጋ “እውነቱ ተገለጠ ሐሰት ተሻረ” የሚለውን ጥቅስ ቀራ፡፡” (ሳሂህ አል-ቡኻሪ ቅፅ 3 መጽሐፍ 43 ሐዲስ 658)

ካዕባ በውስጡ የማርያምንና የክርስቶስን ምስል ይዞ ነበር!

ካዕባ በውስጡ የማርያምና የልጇ የክርስቶስ ምስል ነበረበት፡፡

“ኢብን ኢስሐቅ ከሐኪም ቢን አባድ ቢን ሐኒፍ እና ከሌሎች ትውፊቶች እንዳስተላለፈው ቁረይሾች የማርያም ልጅ ኢየሱስን እና እናቱ ማርያምን (በሁለቱ ላይ ሰላም ይውረድ) ጨምሮ ሌሎች ምስሎችን በካዕባ ውስጥ ያስቀምጡ ነበር፡፡ ኢብን ሺሃብ እንዲህ አለ፡- አስማ ቢንት ሻቅር እንዳለችው የጋሳን ሴት የዓረቦቹን ሐጅ (መንፈሳዊ ጉዞ) ተቀላቅላ ሄዳ በካዕባ ውስጥ የማርያምን ምስል ስትመለከት “አባቴ እና እናቴ ስላንቺ መስዋዕት ይሁኑ አንቺ በእውነቱ የዓረብ ሴት ነሽ” አለቻት፡፡ የአላህ መልእክተኛም ከኢየሱስና ከማርያም ምስል ውጭ የተቀሩትን በሙሉ አስፈረሰ፡፡” (ኢብን ኢስሐቅ፡ ሲራት ራሱል አላህ የጉይላም ትርጉም ገፅ 552)

ሙስሞች ለካዕባ ይሰግዳሉ!

ብዙዎቻችን እንደምናውቀው በእስልምና ስግደት የአምልኮ ክፍል ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ የአንገት ማጎንበስ እንኳን ለሰዎች አያጎነብሱም፡፡ ይሁን እንጂ ሙስሊሞች ለካዕባ ይሰግዳሉ፡፡

“ኢብን አባስ እንዳወሳው እርሱ ጥቁሩን ድንጋይ ይስመውና ይሰግድለት ነበር፡፡” (ቡልግ አል-ማራም መጽሐፍ 6 ሐዲስ 766)

ሙስሊሞች ካዕባን ይስሙታል!

“የአላህ መልእክተኛ መካ እንደደረሰ ካዕባን ሲስም እና ከሰባቱ ዙሮች የመጀመሪያዎቹን ሦስት ዙሮች በፍጥነት ሲዞር አየሁት፡፡” (ሳሂህ አል-ቡኻሪ 1603)

ካዕባ ድንጋይ ብቻ ነውን?

አንዳንድ ሙስሊሞች “ካዕባ ድንጋይ ብቻ ነው፡፡ በእኛ ላይ ምንም ለውጥ አያመጣም፡፡ የነቢዩን ሱና እንከተል ብለን እንጂ ባንስመው ምንም ችግር የለውም” ይሉናል፡፡ ይህ አስተሳሰብ በዘመንኛ ሙስሊሞች ብቻ ሳይሆን በቀደሙ የሙሐመድ ወዳጆችም ዘመንድ የነበረ ነው፡፡

“አቢስ ቢን ራቢአህ እንዲህ አለ፡- ዑመር ጥቁሩን ድንጋይ ተመለከተና “የአላህ መልእክተኛ ሲስምህ ባላይ ኖሮ አልስምህም ነበር” አለና ሳመው፡፡” (ሙስናድ አሕመድ መጽሐፍ 2 ሐዲስ 18)

“አቢስ ቢን ራቢአ እንዳወሳው፡- ዑመር ወደ ጥቁሩ ድንጋይ ቀረበና ሳመው፤ ከዚያም “አንተ ምንም የማትጠቅም እና የማትጎዳ ድንጋይ ብቻ መሆንህ ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ የአላህ መልእክተኛ ሲስምህ ባላይ ኖሮ አልስምህም ነበር” አለ፡፡” (ሳሂህ አል-ቡኻሪ 1597)

እነዚህን ሐዲሳት ስናነብ ነቢይ ነኝ ካለው ሙሐመድ ይልቅ ዑመር የተሸለ እንደሚያስብ እንገነዘባለን፡፡ ምክንያቱም ድንጋይ መሳም አንዳች ጥቅም እንደሌለው አእምሮ ላለው ሰው ሁሉ ግልፅ ነውና፤ ጣዖት (ድንጋይ) አምላኪ ለሆነ ሰው ካልሆነ በስተቀር፡፡

ይሁን እንጂ ይህንን አመለካከት የሚያራምዱ ሙስሊሞች ነቢያቸው ስለ ካዕባ የተናገረውን አያውቁም ማለት ነው፡፡ የሚያውቁ ከሆነ ደግሞ ነቢያቸውን አይታዘዙትም ማለት ነው፡፡

ካዕባ ከሰማይ የወረደ አዳኝ ነው!

“ኢብን አባስ እንዳስተላለፈው የአላህ መልእክተኛ እንዲህ አለ፡- ጥቁሩ ድንጋይ ከሰማይ ነው የወረደው፡፡ ሲወርድም እንደ ወተት ያለ ነጭ ሲሆን በአዳም ልጆች ኃጢአት ምንክያት ነው የጠቆረው፡፡” (ጃሚ አት-ትርሚዲ ቅፅ 2 መጽሐፍ 4 ሐዲስ 877)

በሐዲሱ ላይ እንደምንመለከተው ካዕባ ከሰማይ ሲወርድ ነጭ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የአዳም ልጆች ኃጢአት አጥቁሮታል፡፡ ይህ ማለት ሙስሊሞች ካዕባን ሲነኩት ኃጢአታቸው ወደሱ በመተላለፍ ይሰረይላቸዋል፡፡

“አብደላህ ቢን ዑበይድ እንዳወሳው አንድ ሰው እንዲህ አለ፡- አቡ አበዱራህማን ሀይ ለምንድነው ሁል ጊዜ ሁለቱን ጠርዞች ብቻ ስትነካቸው የማይህ? ብሎ ጠየቀው፡፡ እርሱም የአላህ መልእክተኛ እነርሱን መንካት ኃጢአትን ይደመስሳል ሲል ሰምቼዋለሁ አለ፡፡” (ሱናን አል-ናሳኢ 2919)

ልብ በሉ! ይህ ሐሳብ ክርስቲያኖች ስለ ኢየሱስ የሚያምኑት እምነት ነው፡፡ እንደ ክርስትናው እውነት ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኃጢአት የሌለበት ሲሆን ሰዎች ራሳቸውን ማዳን ስለማይችሉ ሊያድናቸውና በእነርሱ ፈንታ ምትካዊ ሞት ለመሞት ወደ ምድር ወርዷል፡፡ በመስቀል ላይም የሰዎችን ኃጢአት ተሸክሟል፡፡ በሙስሊሞች እምነት መሠረት ልክ እንደዚሁ ካዕባ ከሰማይ ነጭ ሆኖ የወረደ ሲሆን በሙስሊሞች ኃጢአት ምክንያት ጠቆረ፡፡ ሙስሊም ወገኖቻችን ንፁህ የሆነው የእግዚአብሔር ልጅ ኃጢአታቸውን ተሸክሞ ሊያነፃቸው እንደሚችል በመካድ ድንጋይ ኃጢአታቸውን መሸከም መቻሉን ማመናቸው የሚያስገርም ነው፡፡

ካዕባ በአላፍ ፊት ይመሰክራል!

“ኢብን አባስ እንዳስተላለፈው የአላህ መልእክተኛ ስለ ጥቁሩ ድንጋይ እንዲህ አለ፡- በአላህ እምላለሁ! በፍርድ ቀን የሚያይባቸው ሁለት ዓይኖች እና ማን እንደነካው የሚናገርበት ምላስ ይሰጠዋል፡፡” (ጃሚ አት-ትርሚዲ ቅፅ 2 መጽሐፍ 4 ሐዲስ 961)

እንግዲህ ሐዲሱ በግልፅ እንዳስቀመጠልን ካዕባ በፍርድ ቀን ስለሙስሊሞች ይመሰክራል፡፡ ታድያ እንዴት ነው አንዳንድ ሙስሊሞች ካዕባን ብንነካውም ባንነካውም ለውጥ የለውም የሚሉን? ኃጢአታቸው እንዲሰረይላቸው አይፈልጉምን? በፍርስ ቀን እንዲመሰክርላቸው አይፈልጉምን?

ዘመንኛ ሙስሊሞች ከዑመር ጋር ተስማምተው ካዕባን መንካት ነቢዩን ለመታዘዝ እንጂ ምንም መንፈሳዊ (ሃይማኖታዊ) ጥቅም የለውም ሲሉን ነቢያቸው እየዋሸ ነው ማለታቸው ይሆን?

ማጠቃለያ

ከላይ ያየናቸውን ነጥቦች በሙሉ በአንድነት ስናጤን ካዕባ የእስልምና ጣዖት ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

ከእስልምና በፊት ዓረቦች ድንጋይ ያመልኩ ከነበረ፤ የአምልኳቸው አካል ድንጋዩን መዞር እና መሳም ከነበረ፤ በዓረብ አገራት የሚመለኩ ድንጋዮች “ካዕባ” ተብለው ከተጠሩ፤ ካዕባ በመካ ከነበሩ 360 ጣዖታት አንዱ ከነበረ፤ ሙስሊሞች ደግሞ ያንኑ የዓረብ ድንጋይ አምልኮ ተግባር የሚፈፅሙ ከሆነ “ካዕባን አናመልክም” የሚሉበት አንደበት የላቸውም፡፡ ዓረቦቹ ድንጋዮቻቸውን እያመለኩ የሚያደርጓቸውን ተግባራት እነዚያኑ እያደረጉ እንዴት ነው “ካዕባን አላመለክንም” የሚሉን? ሙስሊሞች ካዕባን እያመለኩ ካልሆኑ ዓረቦቹም ድንጋይ ያመልኩ ነበር ተብለው ሊከሰሱ አይገባቸውም፡፡ ምክንያቱም ሁለቱም በድንጋዮቻቸው ዙርያ ተመሳሳይ ድርጊት ይፈፅማሉና፡፡

 

ለእስልምና ሙግቶች ምላሽ