ቁርኣን አንድ ነውን? የኢብን መስዑድ እና የኡበይ ቢን ካዕብ ቁርአኖች

ቁርአን አንድ ነውን?

የኢብን መስዑድ እና የኡበይ ቢን ካዕብ ቁርአኖች

ሙስሊም ኡስታዞች ለሕዝባቸው ከሚመግቧቸው የሐሰት መረጃዎች መካከል ቀዳሚው “ቁርአን አንድ ነው፣ ምንም ዓይነት ልዩነት አያሳይም እንዲሁም ምንም ዓይነት መለዋወጥ አልደረሰበትም” የሚለው ነው፡፡ ነገር ግን የቁርአንን ታሪክ ስናጠና እውነታው ከዚህ በተጻራሪ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ቁርአን ከጅምሩ አንድ አለመሆኑንና የምዕራፎቹን ብዛት እንዲሁም ውስጣዊ ይዘት  አስመልክቶ በሙስሊም ሊቃውንት መካከል ውዝግብ እንደነበረ የሚያሳዩ አያሌ መረጃዎች በእስላማዊ ምንጮች ውስጥ ይገኛሉ፡፡ በምዕራፎች ርዝማኔና በይዘት ረገድ ውዝግብ አስነስተው ከነበሩት መካከል የአብዱላህ ኢብን መስዑድና የኡበይ ቢን ካዕብ ቁርአኖች ዋነኞቹ ናቸው፡፡ አብዱላህ ኢብን መስዑድ ሦስት የቁርአን ምዕራፎችን (ሱራ 1፣ 113 እና 114) “ጸሎቶችና መለማመኛዎች ብቻ ናቸው” በሚል ሰበብ ከቁርአን በመሰረዝ 111 ምዕራፎች ያሉትን የቁርአን ጥራዝ ያዘጋጀ ሲሆን ኡበይ ቢን ካዕብ ደግሞ ሱረቱ አል-ኸል እና ሱረቱ አል-ሐፍድ የተሰኙ ሁለት ምዕራፎችን በመጨመር 116 ምዕራፎች ያሉትን የቁርአን ጥራዝ አዘጋጅቶ ነበር፡፡ ነገር ግን በኡሥማን ትዕዛዝ በዘይድ የተዘጋጀው መደበኛው የቁርአን ቅጂ 114 ምዕራፎች ናቸው ያሉት፡፡ አብዱላህ ኢብን መስዑድ የሰረዛቸው ሦስቱ ሱራዎች ለሙሐመድ የወረዱለት የቁርአን ክፍሎች እንደሆኑ ያምን የነበረ ሲሆን ነገር ግን ከሌሎች የቁርአን ምዕራፎች ጋር በአንድ ጥራዝ በጽሑፍ እንዲሰፍሩ የታሰቡ አለመሆናቸውን ስለሚያምን ነበር ከገዛ ቁርአኑ የሰረዛቸው፡፡ በኢብን መስዑድ ጥራዝ ውስጥ የሚገኙት ሁለቱ ተጨማሪ ሱራዎች ደግሞ ለሙሐመድ እንደወረዱለት ቢታመንም ኡሥማንና ተባባሪዎቹ ከቁርአን አስወግደዋቸዋል፡፡  እነዚህ ሁለቱ ወገኖች ቁርአንን በቀጥታ ከሙሐመድ የተማሩ ከመሆናቸውም በላይ ቁርአንን ለሌሎች እንዲያስተምሩ ከሙሐመድ በቀጥታ ሥልጣንን ከተቀበሉ አራት ሰዎች መካከል በቀዳሚነት የተጠቀሱ መሆናቸው ደግሞ ጉዳዩን በቸልታ ለማለፍ የማይቻል ያደርገዋል፡፡ ይህ ጉዳይ የውይይት አጀንዳ መሆኑ “ቁርአን አንድ ነው” የሚለውን የሙስሊም ኡስታዞች መፈክር ዋጋ የሚያሳጣ በመሆኑ ምክንያት የማስተባበያ ሙግቶችን ለማቅረብ ተገድደዋል፡፡ በዚህ ጽሑፍ በአንድ ሙስሊም ኡስታዝ ተዘጋጅቶ በኢንተርኔት ላይ ሲዘዋወር ያገኘነውን አንድ ጽሑፍ እንፈትሻለን፡፡ ሙስሊሙ ኡስታዝ እንዲህ ሲል ይጀምራል፡-

አብዱል፡-

ቁርኣን አንድ ነው!

በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ እጅግ በጣም አዛኝ በሆነው፡፡

15፥9 *እኛ ቁርኣንን እኛው አወረድነው፡፡ እኛም ለእርሱ ጠባቂዎቹ ነን*፡፡ إِنَّا نَحْنُ نَزَّلْنَا الذِّكْرَ وَإِنَّا لَهُ لَحَافِظُونَ

የኡበይ ኢብኑ ከዐብ ቁኑት ነው፤ “ቁኑት” قنوت‎ ማለት “በየትኛውም ጊዜና ቦታ ላይ በሙስሊሞች ላይ ግፍ ወይም በደል ከደረሰ በሶላት ሩኩዕ በኋላ ኢማሙ የሚያደርገው ዱዓ ነው” የኡበይ ሁለት ቁኑት ቁኑቱል ኸል እና ቁኑቱል ሀፍድ ናቸው፦ አሥ-ሡዩጢ አል-ኢትቃን ፊ ዑሙል ቁርኣን: መጽሐፍ 1, ቁጥር 227

ቁኑቱል ኸል *አላህ ሆይ! አንተን ብቻ እንለምናለን፤ አንተ ብቻ ይቅርታህ እንጠይቃለን፤ እናመሰግንሃለን፤ አናስተባብልህም፤ አንተን ከሚያምጹ እንለያለን እንለያያለን*። اللَّهُمَّ إِنَّا نَسْتَعِينُكَ وَنَسْتَغْفِرُكَ وَنُثْنِي عَلَيْكَ وَلَا نُكْفُرُكَ وَنَخْلَعُ وَنَتْرُكُ مَنْ يَفْجُرُكَ

ቁኑቱል ሀፍድ *አላህ ሆይ! አንተን ብቻ እናመልካለን፤ ሶላትም ሡጁድም ለአንተ ነው፤ እሾትም ወደ አንተ ነው፤ የአንተን ምህረት ተስፋ እናደርጋለን፤ የአንተ ከባድ ቅጣት ከሃድያንን ልትቀጣበት ያለው ቅጣት እንፈራለን*። اللَّهُمَّ إِيَّاكَ نَعْبُدُ وَلَكَ نُصَلِّي وَنَسْجُدُ وَإِلَيْكَ نَسْعَى وَنَحْفِدُ نَرْجُو رَحْمَتَكَ وَنَخْشَى عَذَابَكَ إِنَّ عَذَابَكَ بِالْكُفَّارِ مُلْحَقٌ.

እነዚህ ቁኑቶች ዱዓዎች ሆነው ሳሉ ሱራዎች ናቸው የሚል ተሟጋች ካለ ከሐዲስ ወይም ከሰሃባዎች ከተገኘ ሪዋያህ መረጃ ማቅረብ ይጠበቅበታል፤ ያለበለዚያ ግን የሚሽነሪዎችን አርቲ ቡርቲ ይዞ መነታረክ መደዴ የቡና ወሬ ነው።

መልስ

ሙስሊሙ ሰባኪ ከተናገረው በተጻራሪ ሱረቱ አል-ኸል (የመለያየት ምዕራፍ) እና ሱረተ አል-ሐፍድ (የችኮላ ምዕራፍ)  በኡበይ ቢን ካዕብ ቁርአን ውስጥ ይገኙ የነበሩ ሱራዎች መሆናቸውን ሙስሊም ዑላማዎች በአንድ ድምፅ ይስማሙበታል፡፡ ለምሳሌ ያህል ዕውቅ የሱኒ ኢስላም የፋትዋ ድረገፅ የሆነው Islamqa.info አዝ-ዘርካሺን በመጥቀስ እንዲህ ሲል ጽፏል፡-

Az-Zarkashi said in al-Burhaan (2/37): The leading hadeeth scholar Abu’l-Husayn Ahmad ibn Ja‘far al-Manaadi said in his book an-Naasikh wa’l-Mansookh, concerning that which has been abrogated from the Qur’an but was not erased from what people had learned by heart, that this included the two soorahs that are recited in Qunoot in Witr prayer. He said: There is no difference of opinion among the earlier scholars that these two soorahs were written down in the mushafs that were attributed to Ubayy ibn Ka‘b, and it was narrated from the Prophet (blessings and peace of Allah be upon him) that he recited them, and they were called the soorahs of al-Khal‘ and al-Hafd.

“አዝ-ዘርካሺ በአል-ቡርሃን ቅፅ 2 ገፅ 37 እንዲህ ብለዋል፡- ዕውቅ የሐዲስ ሊቅ የሆኑት አቡል-ሁሴን አሕመድ ኢብን ጃዕፋር አል-መናዲ በመጽሐፋቸው አን-ናሲኽ ወል-መንሱኽ እንደተናገሩት ከቁርአን የተሻሩ ነገር ግን ከሰዎች ትውስታ ያልጠፉትን አስመልክቶ በዊትር ጸሎት ወቅት በቁኑት የሚነበነቡትን ሱራዎች ያጠቃልላል፡፡ እንዲህ አሉ፡- እነዚህ ሁለቱ ሱራዎች የኡበይ ቢን ካዕብ እንደሆኑ በተነገረላቸው ሙሳሂፎች ውስጥ የተጻፉ በመሆናቸውና ከነቢዩ የተላለፉ በመሆናቸው ላይ፣ እርሱም እንዳነበነባቸው እንዲሁም የአል-ኸል እና የአል-ሐፍድ ሱራዎች ተብለው በመጠራታቸው ላይ በቀደምት ሊቃውንት መካከል ልዩነት የለም፡፡” ምንጭ

ይኸው ታዋቂ የፋትዋ ድረገፅ ሲያጠቃልል እንዲህ ይላል፡-

“The most that may be said concerning this matter is that the du‘aa’ of Qunoot was part of the Qur’an in the beginning, then it was abrogated from the Holy Qur’an, but the text remained because all of the Sahaabah were using it.”

“ይህንን ጉዳይ አስመልክቶ ማለት የሚቻለው የመጨረሻው ነገር ቢኖር የቁኑት ዱዓ መጀመርያ ላይ የቁርአን አካል የነበረና ከዚያም ከቁርአን የተሻረ ሲሆን ነገር ግን ሰሓባዎች ሲጠቀሙት ስለነበረ ጽሑፉ ሊቆይ ችሏል፡፡” (ያለፈውን ምንጭ ይመልከቱ)

እነዚህ ጸሎቶች ሱራዎች መሆናቸውና የቁርአን አካል የነበሩ መሆናቸው አጠያያቂ አይደለም፡፡ ከኡበይ ቢን ካዕብ በተጨማሪ ኢብን አባስ በራሱ የቁርአን ጥራዝ ውስጥ እንዳካተታቸው አስ-ሱዩጢ ዘግቧል (al-Suyuti, Al-Itqan, p.152-153)፡፡ በተጨማሪም  አብዱላህ ኢብን መስዑድ የተሰኘው የሙሐመድ ወዳጅ በራሱ ኮፒ ውስጥ ያካተታቸው ሲሆን (al-Suyuti, Tafseer Dur al-Manthur, Volume 4 p. 421) ኋላ ግን ሌሎች ሦስት ሱራዎችን ጨምሮ ከራሱ ኮፒ ውስጥ አስወግዷቸዋል፡፡

ስለዚህ አል-ኸል እና አል-ሐፍድ ሱራዎች አይደሉም የሚለው የሙስሊሙ ሰባኪ አባባል የመረጃ እጥረት ነው፡፡ ሱራዎች የመሆናቸው ጉዳይ የሚያከራክር ባለመሆኑ እንለፈውና የቁርአን አካል ከነበሩ ከቁርአን የተወገዱት እውን ስለተሻሩ ነውን? የሚለውን ጥያቄ እንመልስ፡፡

ከቁርአን ለመወገዳቸው እንደ ምክንያት የሚጠቀሰው ጸሎቶች ብቻ የመሆናቸው ጉዳይ ነው፤ ነገር ግን በቁርአን ውስጥ የሚገኙ ሦስት ሱራዎች (1፣ 113 እና 114) ጸሎቶች ብቻ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ከአፍታ በኋላ እንደምንመለከተው አብዱላህ ኢብን መስዑድ ጸሎቶች ብቻ ናቸው በሚል ሦስቱንም ሱራዎች ከራሱ ኮፒ ውስጥ ሰርዞ የነበረ ቢሆንም ሌሎች ሙስሊሞች ግን ከሌሎች ሱራዎች እኩል በጽሑፍ መስፈር እንዳለባቸው ስላመኑ እነሆ እስከ ዛሬ ድረስ የቁርአን አካል ሆነው ቀጥለዋል፡፡ ስለዚህ ጸሎት ብቻ መሆን አንድን ሱራ ከቁርአን ለማስወገድ መስፈርት አይደለም ማለት ነው፡፡

እነዚህ ሱራዎች ኢብን አባስና ኡበይ ቢን ካዕብን በመሳሰሉ ታላላቅ የሙሐመድ ሶሓቦች የቁርአን አካል ተደርገው ተወስደው ከነበረና በኮፒዎቻቸው ውስጥ ተመዝግበው ከነበረ ከሌሎች የቁርአን ኮፒዎች ውስጥ ለምን እንደተወገዱ ጠንካራ መስረጃ ማቅረብ ያስፈልጋል፡፡ አንዳንዶች እንደሚሉት እነዚህ ሱራዎች በኡበይ ጥራዝ ውስጥ እንደ መጨረሻ ቅጥያ የተቀመጡ ሳይሆኑ በሱራ 113 እና 114 መካከል እንደሚገኙ ማስታወስ ያስፈልጋል (Theodor Nöldeke et. al., The History of the Qur’an, 2nd Edition,  p. 243-244)፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሱራዎች ከቁርአን የተሻሩ ስለመሆናቸው ከሙሐመድም ሆነ ከእነዚህ ወገኖች የተላለፈ መረጃ ወዴት አለ? ጥንታውያን ሙስሊሞች ስለ ቁርአን ይዘት እንዲህ የገዘፉ የአቋም ልዩነቶችን ይዘው በሚታዩበት ሁኔታስ ቁርአን አንድ እንደሆነ መናገርስ ስሜት የሚሰጥ ነውን?

አብዱል

ሚሽነሪዎች የዐብደላህ ሙስሐፍ ላይ 111 ሱራህ ብቻ ያየዘ ነው” ይላሉ፤ ነገር ግን የዐብደላህ ሙስሐፍ ላይ 111 ሱራህ ብቻ እንደነበረ እና ሱረቱል ፋቲሐህ፣ ሱረቱል ፈለቅ እና ሱረቱ አን-ናስን እንደማያካትት የሚያሳይ የሐዲስ መረጃ የለም።

መልስ

ቀደምት እስላማዊ ታሪኮችን ለማወቅ የሐዲስ መጻሕፍት ብቸኛ ምንጭ ናቸው ያለው ማን ነው? ስለ ቁርአን ጥንታውያን ጥራዞች ይዘት ለማወቅ የሚያስችሉ እጅግ በርካታ ተዓማኒ ምንጮች ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህ መካከል የኢብን አቢዳውድ “ኪታብ አል-ሙሳሂፍ” እና የአስ-ሱዩጢ “ኢትቃን ፊ ኡሉም አል-ቀርአን” መጻሕፍት ዋነኞቹ ናቸው፡፡ በአስ-ሱዩጢ መሠረት ኢብን መስዑድ ሦስቱም ሱራዎች (ሱራ 1፣ 113 እና 114) ለሙሐመድ ከአላህ የወረዱ ሱራዎች እንደሆኑ ቢያምንም በይዘታቸው ጸሎቶች በመሆናቸው ከሌሎች ሱራዎች ጋር በጽሑፍ መስፈር እንደሚገባቸው አያምንም ነበር፡፡

“Imam Fakhruddin said that the reports in some of the ancient books that Ibn Mas’ud denied that Suratul-Fatiha and the Mu’awwithatayni are part of the Qur’an are embarrassing in their implications… But the Qadi Abu Bakr said “It is not soundly reported from him that they are not part of the Qur’an and there is no record of such a statement from him. He omitted them from his manuscript as he did not approve of their being written. This does not mean he denied they were part of the Qur’an. In his view the Sunnah was that nothing should be inscribed in the text (mushaf) unless so commanded by the Prophet (saw) … and he had not heard that it had been so commanded.” – as-Suyuti, Al-Itqan fii Ulum al-Qur’an, p.186

“ኢማም ፈኽሩዲን እንደተናገሩት በአንዳንድ ጥንታውያን መጻሕፍት ውስጥ ኢብን መስዑድ ሱረቱል ፋቲሃ እና ሙዐዊሠተይን (ሱራ 113 እና 114) የቁርአን አካል መሆናቸውን ክዷል የሚሉት ዘገባዎች አሸማቃቂ ምልከታ አላቸው … ነገር ግን ቃዲ አቡ በከር እንዲህ ብለዋል፡- “የቁርአን አካል አይደሉም የሚል ተዓማኒ ዘገባ ከእርሱ አልተላለፈም፤ እንዲህ ብሎም መናገሩ አልተጻፈም፡፡ ከራሱ የእጅ ጽሑፍ ያስወገደበት ምክንያት በጽሑፍ መስፈር እንዳለባቸው ስላላመነ ነው፡፡ ይህ ማለት የቁርአን አካል መሆናቸውን ክዷል ማለት አይደለም፡፡ በእርሱ አመለካከት መሠረት ሱና ነቢዩ ያላዘዙት የትኛውም ነገር በጽሑፍ (ሙሳሂፍ) መስፈር የለበትም የሚል ነበር … እንደዚያ ዓይነት ትዕዛዝ መሰጠቱን ደግሞ አልሰማም፡፡” (አል-ኢትቃን ገፅ 186)

ስለዚህ ኢብን መስዑድ ሦስቱ ሱራዎች የቁርአን አካል እንደሆኑ ቢያምነም በጽሑፍ እንዲሰፍሩ የታለሙ መሆናቸውን ስላላመነ ከራሱ ጥራዝ አስወግዷቸዋል፡፡

ኢብን መስዑድ ሱረቱ አል-ፈለቅን እና ሱረቱ አን-ናስን በቁርአኑ ውስጥ እንዳላካተተ የሐዲስ መረጃ አለ፡-

“Ibn Mas‘ood did not write al-mu’awwizatayn in his mushaf.” (Musnad Ahmad bin Hanbal, (Beirut: ar-Resalah Publications, 2001) Hadith 21186

“ኢብን መስዑድ አል-ሙዐዊዘተይንን (አል-ፈለቅ እና አን-ናስን) በሙሳሂፉ ውስጥ አልጻፈም፡፡”

እዚያው ሙስናድ አሕመደድ ቢን ሐንበል ሐደስ ቁጥር 21186 ላይ እንዲህ ተብሏል፡-

“I told Ubayy, ‘your brother Ibn Mas‘ood erases them (surah 113 & 114) from his mushaf,’ and he did not object.”

“ኡበይን እንዲህ አልኩት “ያንተ ወንድም ሱራ 113 እና 114ን ከሙሳሂፉ ውስጥ ሰርዟቸዋል፡፡”፤ እርሱም ተቃውሞ አላቀረበም፡፡”

ስለዚህ የሙስሊሙ ሰባኪ አባባል ስህተት ነው፡፡ አል-ፋቲሃን በተመለከተ የሐዲስ ማስረጃ ከአፍታ በኋላ እናቀርባለን፡፡

አብዱል

ነገር ግን በነብያችን”ﷺ” ጊዜ ሁለቱ ሱራዎች ሱረቱል ፈለቅ እና ሱረቱ አን-ናስ ለዱዓ አገልግሎት ላይ ስለሚውሉ ዐብደላህ ኢብኑ መሥዑድ ሙዐወዛት የቁርኣን ክፍል አይደሉም ብሎ ሲናገር ኡበይ ኢብኑ ከዕብም የአላህን መልእክተኛን”ﷺ” ስለ እነርሱ ጠይቋቸው እርሳቸውም፦ “እነርሱ ወደ እኔ ተወርዶልኛል፤ የቁርኣን ክፍል አርገን እንቀራዋለን” ብለውታል፦ ኢማም ቡኻርይ : መጽሐፍ 65, ሐዲስ 4977

ዚር ኢብኑ ሑበይሽ እንደተረከው፦ *ኡበይ ኢብኑ ከዕብን፦ “አቢ ሙንዚር ሆይ! ወንድምህ ዐብደላህ ኢብኑ መሥዑድ፦ ሙዐወዛት የቁርኣን ክፍል አይደለም” ይላል ብዬ ጠየኩት፤ ኡበይ ኢብኑ ከዕብም፦ “የአላህን መልእክተኛ”ﷺ” ስለ እነርሱ(ሙዐወዛት) ጉዳይ ጠየኳቸው፤ እርሳቸውም፦ “እነርሱ(ሙዐወዛት) ወደ እኔ ተወርዶልኛል፤ የቁርኣን ክፍል አርገን እንቀራዋለን” አሉኝ። ስለዚህ የአላህ መልእክተኛ”ﷺ” እንዳሉት እኛም እንላለን*። عَنْ زِرٍّ، قَالَ سَأَلْتُ أُبَىَّ بْنَ كَعْبٍ قُلْتُ يَا أَبَا الْمُنْذِرِ إِنَّ أَخَاكَ ابْنَ مَسْعُودٍ يَقُولُ كَذَا وَكَذَا‏.‏ فَقَالَ أُبَىٌّ سَأَلْتُ رَسُولَ اللَّهِ صلى الله عليه وسلم فَقَالَ لِي قِيلَ لِي‏.‏ فَقُلْتُ، قَالَ فَنَحْنُ نَقُولُ كَمَا قَالَ رَسُولُ اللَّهِ صلى الله عليه وسلم‏.‏

ከዚያ በኃላ ዐብደላህ ኢብኑ መሥዑድ እነዚህ ሁለት ሱራዎች ላይ ምንም አይነት ቅሬታ እንደነበረው የሚያሳይ የሐዲስ መረጃ የለም። ገና ለገና በነብያችን”ﷺ” ጊዜ ሁለቱ ሱራዎች የቁርኣን ክፍል አይደሉም ብሏልና በዑስማን ኸሊፋነት ጊዜ ዘይድ ኢብኑ ሣቢትን ስለተቃወመ ሁለቱን ሱራህ ስለማይቀበል ነው ማለት ምንጭ አልባና ሰነድ አልባ ስሁት ሙግት ነው።

መልስ

ከላይ የሚገኘው ሐዲስ ሱራዎቹ የቁርአን አካል ስለመሆናቸው እንጂ በጽሑፍ መስፈር የሚገባቸው ስለመሆናቸው እንደማይናገር ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ቀደም ሲል ከአስ-ሱዩጢ መጽሐፍ እንደተመለከትነው የኢብን መስዑድ አመለካከት ሱራዎቹ የቁርአን አካል አይደሉም የሚል ሳይሆን በጽሑፍ የሰፈረው ቁርአን አካል አይደሉም የሚል ነው፡፡ ስለዚህም ከራሱ ጥራዝ እንዲወገዱ አድርጓል፡፡ ኢብን መስዑድ ሱራዎቹ ለሙሐመድ የተገለጡለት የቁርአን ክፍሎች መሆናቸውን ቢቀበልም በጽሑፍ መስፈር እንደሚገባቸው አያምንም ነበር፡፡ ስለዚህ ሙስሊሙ ሰባኪ ያቀረበው የሐዲስ ማስረጃ ሦስቱ ሱራዎች በኢብን መስዑድ ጥራዝ ውስጥ ስለመካተታቸው ማስረጃ ሊሆን አይችልም፡፡

እዚህ ጋ መነሳት ያለበት ትልቁ ጥያቄ የኢብን መስዑድና የዘይድ ቁርአን ፍፁም አንድ ከነበሩ ኢብን መስዑድ የከረረ ተቃውሞ ማስነሳቱና የዘይድን ቁርአን እንዳይቀበሉ የኢራቅ ሕዝቦችን ማስጠንቀቁ ለምን ነበር? የሚል ነው፡፡ አት-ትርሚዚ ሐዲስ ውስጥ ተከታዩ ዘገባ ሰፍሯል፡-

“አዝ-ዙህሪ እንዳስተላለፈው፤ ኡበይ ቢን አብዱላህ ቢን ኡጥባህ እንደነገረኝ አብደላህ ቢን መስዑድ ዘይድ ቢን ጣቢት ሙሳሒፉን በመጻፉ ደስተኛ ስላልነበረ እንዲህ ብሎ ነበር፡- ‹እናንተ የሙስሊም ሕዝቦች ሆይ! የዚህን ሰው ሙሳሒፍ እና የእርሱን ንባብ ከናንተ አስወግዱ፡፡ በአላህ እምላለሁ! እኔ እስልምናን ስቀበል በከሃዲ ሰው እርግብግቢት ውስጥ ነበር፡፡› አብደላህ ኢብን መስዑድ አክሎም እንዲህ አለ፡- ‹እናንተ የኢራቅ ሕዝቦች ሆይ! ከናንተ ጋር ያሉትን ሙሳሒፎች ያዟቸው፤ ደግሞም ደብቋቸው፡፡ አላህ እንዲህ ብሏልና ‘የሆነ ነገር የሚሰውር ሰው በዕለተ ትንሣኤ የሰወረውን ነገር ይዞ አላህን ይገናኘዋል፡፡’ ስለዚህ አላህን ሙሳሒፉን ይዛችሁ ተገናኙት፡፡› አዝ-ዙህሪ እንደተናገረው ‹ከተከበሩ የአላህ መልእክተኛ ባልደረቦች መካከል አንዳንዶቹ ይህንን የኢብን መስዑድ አመለካከት አልወደዱትም ነበር፡፡›” (English Translation of Jami‘ At-Tirmidhi. Compiled by Imam Hafiz Abu ‘Eisa Mohammad Ibn ‘Eisa At-Tirmidhi; translated by Abu Khaliyl; Darussalam Publishers & Distributors, First Edition, 2007, Vol. 5, pp. 414)

ኢብን መስዑድ እንዲህ ያለ የከረረ ተቃውሞ ማሰማቱ ያለ ምክንያት አልነበረም፡፡ የዘይድ ቁርአን ኢብን መስዑድ በጽሑፍ መስፈር እንደሌለባቸው ያመናቸውን ሦስቱን ሱራዎች ከማካተቱም በተጨማሪ በኢብን መስዑድ ውስጥ የሚገኙ ብዙ ንባባትን የቀነሰና የጨመረ ነበር፡፡ ኢብን አቢዳውድ “ኪታበ አል-ሙሳሒፍ” በተሰኘው መጽሐፋቸው እነዚህን ልዩነቶች ለመዘርዘር ወደ 19 ገፆች ያህል ፈጅተዋል! (Ibn Abi-Dawud al-Sijistani, Kitab al-Masahif, pp. 54-73)፡፡ እነዚህ ልዩነቶች በሳሂህ ሐዲሳትም ውስጥ ጭምር ተመዝግበዋል፡፡ ለመምሳሌ ያህል ሳሂህ አል-ቡኻሪ ውስጥ እንደተዘገበው አብዱላህ ኢብን መስዑድ ሱራ 92፡3 ላይ የሚገኘውን “ወንድንና ሴትን በፈጠረውም (አምላክ እምላለሁ)” የሚለውን አንቀጽ ሲያነብ “በወንድና በሴት እምላለሁ” በማለት ነበር፡፡ አቡ ደርዳ የተሰኘ ሌላ የመሐመድ ወዳጅ ይህንኑ ንባብ ከነቢዩ መስማቱን በመሐላ በማረጋገጥ የኡሥማንን ንባብ እንደማይቀበል ተናግሯል፡፡ (Sahih Al-Bukhari, Volume 5, Book 57, Number 105; Volume 6, Book 60, Number 468; Volume 5, Book 57, Number 85)

አብዱል

ዋናው ነጥብ እሺ እርሱ አልተቀበለም እንበል የአሐድ ዘገባ እኮ ቁርኣን ላይ ተቀባይነት የለውም፤ “አሐድ” آحاد ማለት አንድ ዘገባ በአንድ ሙስኒድ ከተተረከ ትረካው “አሐድ” ይባላል፤ ነገር ግን ቁርኣን በሙተዋቲር ብቻ ነው ተቀባይነት ያለው፤ “ሙተዋቲር” مُتَواتِر ደግሞ አንድ ዘገባ ከአንድ ኢስናድ ማለትም ሰንሰለት በላይ በጀመዓ የሚደረግ ዘገባ ነው።

መልስ

የቁርአን አስተላለፍ ልክ እንደ ሐዲስ በኢስናድ (የዘገባ ሰንሰለት) መሆኑን ብዙ ሙስሊሞች የማያውቁት እውነታ ነው፡፡ ብዙዎቹ በሁሉም የመጀመርያዎቹ ሙስሊሞች የሚታወቅ ምንም ዓይነት ልዩነት የማያሳይ አንድ ዓይነት ቁርአን ብቻ ተላልፎ እዚህ የደረሰ ይመስላቸዋል፡፡ እውነታው ግን እንደርሱ አይደለም፡፡ ከመጀመርያዎቹ የሙሐመድ ባልደረቦች የተላለፉ ብዙ ልዩነቶችን የሚያሳዩ ብዙ ዓይነት ቁርአኖች ነበሩ፤ አሁንም አሉ፡፡ ይህንን ካልን ዘንዳ ሙስሊሙ ሰባኪ ኢብን መስዑድን ለማጣጣል ያቀረበው ሙግት ለምን እንደማያስኬድ እንመልከት፡፡

ኢብን መስዑድ እንደ ማንኛውም ሰው ሳይሆን ሙሐመድ ራሱ ቁርአንን እንዲያስተምሩ ሥልጣን ከሰጣቸው አራት ሰዎች መካከል አንዱ ነበር፡፡ ከእርሱ ጋር ይህንን ሥልጣን የተቀበሉት ሦስቱ አነብናቢዎች ሰሊም፣ ሙዓዝና ኡበይ ቢን ከዕብ ነበሩ (Sahih al-Bukhari, Vol. 6, Bk 61, no. 521)፡፡ በዚህ ሁኔታ ኢብን መስዑድን እንደ ማንኛውም ሰው ቆጥሮ የእርሱን ምስክርነት ማጣጣል የሙሐመድን ሥልጣንና ተዓማኒነት ጥያቄ ላይ መጣል ነው፡፡ በተጨማሪም ኢብን መስዑድ ከሙሐመድ ጋር አብሮ የነበረና ከእርሱ በቀጥታ የተማረ በመሆኑ የኢስናድ ጥያቄ መነሳት ካለበት ከእርሱ ቀጥሎ ባሉት ሰዎች ላይ እንጂ በእርሱ ላይ አይደለም፡፡

የኢብን መስዑድ ተዓማኒነት በሌሎች አነብናቢዎች እስካልተረጋገጠ ድረስ ተዓማኒ አይደለም ከተባለ በየትኞቹ የሙሐመድ ባልደረቦች ምስክርነት ማረጋገጥ እንደሚቻል ማሰብ ያዳግታል፡፡ ምክንያቱም ከሙሐመድ ቁርአንን የተማሩት ሙስሊሞች ብዙ ልዩነተቶችን የሚያሳዩ የተለያዩ ቁርአኖችን ተቀብለው ስለነበር የማንኛቸው ትክክል እንደሆነ ማወቅ የሚቻልበት መንገድ የለም፡፡ ለምሳሌ ያህል ሙሐመድ ቁርአንን እንዲያስተምሩ በልዩ ሁኔታ ሥልጣን ከሰጣቸው አራቱ አነብናቢዎች መካከል ኡበይ ቢን ካዕብ ሁለት ሱራዎችን በራዙ ውስጥ አካቶ እንደነበር ቀደም ሲል ተመልክተናል፡፡ የእርሱ ቁርአን ከኢብን መስዑድም ሆነ ከዘይድ ቁርአኖች ጋር የማይስማሙ ንባቦችንም ያካተተ ነበር፡፡ ለአብነትም አብዱላህ ዩሱፍ አሊ የተሰኘው ዕውቅ የቁርአን ተርጓሚ ሱራ 33፡6 የንባብ ልዩነት እንደሚያሳይ ጠቅሷል፡፡ የኡሥማን ቅጂ እንደሆነ የሚታመነው በኛ ዘመን የሚገኘው ቁርአን እንዲህ ይነበባል፡-

“ነቢዩ በምእምናን ከነፍሶቻቸው ይበልጥ ተገቢ ነው፡፡ ሚስቶቹም እናቶቻቸው ናቸው፡፡”

ዩሱፍ አሊ የኡበይ ቢን ካዕብ ቅጂ “እንዲሁም እርሱ አባታቸው ነው” የሚል ሐረግ እንደሚጨምር በግርጌ ማስታወሻው ላይ ገልጿል (Abdullah Yususf Ali, The Holy Qur’an, p. 1104, foot note. 3674)፡፡ ስለዚህ ከሙሐመድ በቀጥታ ሥልጣንን የተቀበሉ ወገኖች ራሳቸው ግዙፍ የሆኑ ልዩነቶችን የሚያሳዩ ቁርአኖች ከነበሯቸው ኢብን መስዑድን በየትኛው ጀመዓ መዝነን ነው አቋሙን ውድቅ የምናደርገው?

ቁርአንን የማነብነብ ብቃቱ በሙሐመድ ተመስክሮለት እንዲያስተምር ተሹሞ የነበረው ኢብን መስዑድ ቁርአንን በአንድ ጥራዝ ለማሰባሰብ በኡሥማን ከተዋቀረው ኮሚቴ እንዲገለል መደረጉ አስገራሚ ነው፡፡ ከዚህ የተነሳም ቅሬታውን እንዲህ በማለት ገልፆ ነበር:-

“ሙስሊሞች ሆይ! ቁርአንን እንዳልጽፍ እኔን በማግለል እስልምናን ስቀበል [ገና ሳይወለድ] በአባቱ አካል ውስጥ በካፊርነት ለነበረው ሰው [ለዘይድ] ኃላፊነት ተሰጠ፡፡” (Ibn Abi Dawud al-Sijistani. p. 24-25; Cited in: The Qur’an Dilemma; Vol. 1, p. 54)

ኢብን መስዑድ በኡሥማን ትዕዛዝ በዘይድ ተዘጋጅቶ የነበረውን ቁርአን ጨምሮ ሕዝበ ሙስሊሙ የተጭበረበረ ንባብ የሚከተል መሆኑን በማሳወቅ በግልፅ ተቃውሟል (Ibn Sa’d’s Kitab al-Tabaqat al-Kabir, English translation by S. Moinul Haq, M.A., PH.D assisted by H.K. Ghazanfar M.A. [Kitab Bhavan Exporters & Importers, 1784 Kalan Mahal, Daryaganj, New Delhi- 110 002 India], Volume 2, p. 444)፡፡

የኩፋ ሕዝቦች በኡሥማን ውሳኔ የፀደቀውን አዲሱን ቁርአን እንዳይቀበል አድርጓል (Nöldoke, Tarikh al-Qur’ān 280, 339; Cited in: The Qur’an Dilemma; Vol. 1, p. 54)፡፡

በዚህም ምክንያት የኩፋ ሕዝብ አል-ሐጃጅ ኢብን ዩሱፍ አል-ሣቃፊ ሥልጣን እስከያዘበት ዘመን ድረስ የኢብን መስዑድን ቁርአን ተቀብሎ ኖሯል (Encyclopedia of the Qur’ān Vol. 1, p. 348; Cited in: The Qur’an Dilemma; Vol. 1, p. 54)፡፡

ኢብን መስዑድ ይህን ያህል ተፅዕኖ እንዲያሳድር ያደረገው ከሙሐመድ ጋር በነበረው ቅርበት ምክንያት ያተረፈው ተሰሚነት ነው፡፡ ነገር ግን ኸሊፋ ኡሥማን የራሱ አጀንዳ ስለነበረው ከኮሚቴው አባላት ሁሉ ይልቅ ተዓማኒ የነበረውን ሰው በማግለል አዲስ የቁርአን ቅጂ እንዲዘጋጅ አድርጓል፡፡ ቁርአን ፖለቲከኞች በወደዱት መንገድ ያዘጋጁት መጽሐፍ እንጂ መለኮታዊ መገለጥ አይደለም!

አብዱል

“አል-ሙዐወዘተይን” الْمُعَوِّذَتَيْن የሚባሉት ሁለቱ ሱራዎች ሱረቱል ፈለቅ እና ሱረቱ አን-ናስ ሲሆኑ የሲሕር ማክሸፊያ ሆነው መውረዳቸውን የአላህ መልእክተኛ”ﷺ” ከመነሻው ነግረውናል፦ ኢማም ሙስሊም መጽሐፍ 6 , ሐዲስ 319:

*የአላህ መልእክተኛ”ﷺ” አሉ፦ ዛሬ ምን አስደናቂ አንቀጾች ዛሬ ወርደዋል፤ ይህም ብጤአቸው ታይቶ አያውቅም! እነርሱም፦ “በል «በተፈልቃቂው ጎህ ጌታ እጠበቃለሁ” እና በል «በሰዎች ፈጣሪ እጠበቃለሁ» ናቸው*። قَالَ رَسُولُ اللَّهِ صلى الله عليه وسلم ‏”‏ أَلَمْ تَرَ آيَاتٍ أُنْزِلَتِ اللَّيْلَةَ لَمْ يُرَ مِثْلُهُنَّ قَطُّ ‏{‏ قُلْ أَعُوذُ بِرَبِّ الْفَلَقِ‏}‏ وَ ‏{‏ قُلْ أَعُوذُ بِرَبِّ النَّاسِ‏}‏ ‏”‏

ዓኢሻህ”ረ.ዐ.” ሱረቱል ፈለቅና ሱረቱ አን-ናስ ነብያችን”ﷺ” ሚቀሩት ሱራዎች መሆናቸውን መስክራለች፦

ሱነን ኢብኑ ማጃህ መጽሐፍ 31, ሐዲስ 3529

ዓኢሻህ”ረ.ዐ.” እንደተረከችው፦ *ነብዩ”ﷺ” ሲታመሙ ሙዐወዛትን ማለትም ሱረቱል ፈለቅና ሱረቱ አን-ናስ ይቀሩ ነበር*። عَنْ عَائِشَةَ، أَنَّ النَّبِيَّ ـ صلى الله عليه وسلم ـ كَانَ إِذَا اشْتَكَى يَقْرَأُ عَلَى نَفْسِهِ الْمُعَوِّذَات

ኢማም ቡኻርይ መጽሐፍ 80, ሐዲስ 16

ዓኢሻህ”ረ.ዐ.” እንደተረከችው፦ *መቼም ቢሆን የአላህ መልእክተኛ”ﷺ” ወደ አልጋ ሲሄዱ እጃቸውን እያወዛወዙ በተመሳሳይ ጊዜ ሙዐወዛትን ማለትም ሱረቱል ፈለቅና ሱረቱ አን-ናስ ይቀሩ ነበር*። عَنْ عَائِشَةَ ـ رضى الله عنها أَنَّ رَسُولَ اللَّهِ صلى الله عليه وسلم كَانَ إِذَا أَخَذَ مَضْجَعَهُ نَفَثَ فِي يَدَيْهِ، وَقَرَأَ بِالْمُعَوِّذَاتِ،

መልስ

ቀደም ሲል እንደተመለከትነው ኢብን መስዑድ ሦስቱ ሱራዎች በጽሑፍ መስፈር እንደሌለባቸው ያምን ስለነበር ከራሱ ቁርአን ውስጥ አስወገዳቸው እንጂ ለሙሐመድ መውረዳቸውንና በቃል መነብነባቸውን ስላልካደ ከላይ ከተጠቀሱት ሐዲሳት ጋር ፀብ የለውም፡፡ የኛ ጥያቄ በጽሑፍ ከሰፈሩት ቀዳሚያን የቁርአን ጥራዞች መካከል የአብዱላህ ኢብን መስዑድ ቁርአን ሦስት ሱራዎችን የቀነሰና የኡበይ ቢን ካዕብ እንዲሁም የኢብን አባስ ቁርአኖች ሁለት ሱራዎችን የቀነሱ ከነበሩ ቁርአን ከመጀመርያው አንድ እንደነበር እንዴት መናገር ይቻላል? የሚል ነው፡፡

አብዱል

ሱረቱል ፋቲሐህ በዐብደላህ ኢብኑ መሥዑድ ሙስሐፍ ላይ አልነበረችም የሚለው ምንም አይነት ኢስናድ የሌለው ዲቃላ ንግግር ነው፤ ሱረቱል ፋቲሐህ በቁርኣን ውስጥ ታላቂቱን ሱራህ እና የቁርኣን እናት ተብላ የምትታወቅ ሱራ እንደሆነች በቁና ማስረጃ ማቅረብ ይቻላል፤ ግን ጊዜና ቦታ ላለማጣበብ ይህ በቂ ነው፦

ኢማም ቡኻርይ: መጽሐፍ 66, ሐዲስ 57

ዐብደላህ ኢብኑ ሙገፈል እንደተረከው *በመካ ውድቀት ቀን የአላህ መልእክተኛ”ﷺ” በሴት ግመል ላይ ሆነው ሱረቱል ፋቲሐህን ይቀሩ ነበር*። حَدَّثَنَا حَجَّاجُ بْنُ مِنْهَالٍ، حَدَّثَنَا شُعْبَةُ، قَالَ أَخْبَرَنِي أَبُو إِيَاسٍ، قَالَ سَمِعْتُ عَبْدَ اللَّهِ بْنَ مُغَفَّلٍ، قَالَ رَأَيْتُ رَسُولَ اللَّهِ صلى الله عليه وسلم يَوْمَ فَتْحِ مَكَّةَ وَهْوَ يَقْرَأُ عَلَى رَاحِلَتِهِ سُورَةَ الْفَتْحِ‏.‏

መልስ

ኢብን መስዑድ አል-ፋቲሃን በራሱ የቁርአን ቅጂ ውስጥ አለማካተቱ የሚፈጥረውን ጥያቄ የፈሩ አንዳንድ ሙስሊም ሊቃውንት ይህንን ሐቅ ቢክዱም ታላቁ የሐዲስ ሊቅ ኢብን ሐጃር አል-አስቀላኒ በሳሂህ አል-ቡኻሪ ላይ በጻፉት ሐተታ ውስጥ እንዳሰፈሩት በኢብን መስዑድ ቁርአን ውስጥ አል-ፋቲሃ አልነበረችም፤ ደግሞም ዘገባው አስተማማኝ ኢስናድ ያለው ነው (as-Suyuti, Al-Itqan fii Ulum al-Qur’an, p.187)፡፡ በተጨማሪም አል-ቁርጡቢ በተፍሲሩ ውስጥ ኢስናድ ጠቅሶ ኢብን መስዑድ አልፋቲሃን በራሱ ጥራዝ ውስጥ አለማካተቱን ገልጿል (al-Qurtubi, al-Jami al-Ahkam al-Qur’an. Dar al-Kutab al-Misriyah, Cairo, 1964 vol.1 p.115)፡፡ አል-ቁርጡቢ የጠቀሰው ኢስናድ በአረብኛ በተከታዩ ገፅ ላይ የሚገኝ ሲሆን የኢስናዱ ዝርዝር አል-ሐሰን ቢን አል-ሐባብ፣ ሱሌይመን ቢን አል-ሸዓት፣ ኢብን አቢ ቁዳማህ፣ አል-አማሽ፣ ኢበራሂም፣ ይላል፡፡

فالجواب ما ذكره أبو بكر الأنباري قال : حدثنا الحسن بن الحباب حدثنا سليمان بن الأشعث حدثنا ابن أبي قدامة حدثنا جرير عن الأعمش قال : أظنه عن إبراهيم قال : قيل لعبد الله بن مسعود : لم لم تكتب فاتحة الكتاب في مصحفك ؟ قال لو كتبتها لكتبتها مع كل سورة . قال أبو بكر : يعني أن كل ركعة سبيلها أن تفتتح بأم القرآن قبل السورة المتلوة بعدها ، فقال : اختصرت بإسقاطها ، ووثقت بحفظ المسلمين لها ، ولم أثبتها في موضع فيلزمني أن أكتبها مع كل سورة ، إذ كانت تتقدمها في الصلاة .

http://www.quran7m.com/searchResults/001002.html

ስለዚህ ኢስናድ የለውም የሚለው የሙስሊሙ ሰበባኪ አባባል ቅጥፈት ነው፡፡

ኢብን መስዑድ አል-ፋቲሃ ከሌሎች ሱራዎች ጋር በጽሑፍ መስፈር እንደሌለበት እንጂ ለሙሐመድ እንዳልወረደለት ስላልተናገረ ሙሐመድ ሱራውን መቅራቱ ከርሱ አመለካከት ጋር የሚጋጭበት መንገድ የለም፡፡ ሙሐመድ አል-ፈቲሃን እንደ ቀራ ሁሉ የቁኑት ሱራዎችንም ይቀራ ነበር፤ ነገር ግን ሱራዎቹ በዛሬው ቁርአን ውስጥ አልተጻፉም፡፡ ስለዚህ ሙሐመድ አል-ፋቲሃን ስለቀራ ብቻ በጽሑፍ መስፈር የለበትም የሚለው የኢብን መስዑድ አቋም ውድቅ ሊሆን አይችልም፡፡

አብዱል

ኢማም ቡኻርይ: መጽሐፍ 66, ሐዲስ 28 አቢ ሠዒድ ኢብኑ ሙዐላ እንደተረከው *ሶላት ላይ ሆኜ ነብዩ”ﷺ” ጠሩኝ፤ ነገር ጥሪያቸውን አልመለስኩላቸውም፤ በኃላ ላይ፦ “የአላህ መልእክተኛ ሆይ! ሶላት ላይ ነበርኩኝ” አልኩኝ፤ እሳቸውም፦ አላህ፦ “(መልእክተኛው) በጠራችሁ ጊዜ ለአላህ እና ለመልክተኛው ታዘዙ”8፥24 አላለምን? ከዚያም፦ “በቁርኣን ውስጥ ታላቂቱን ሱራህ ላስተምርህን? እርሷም፦ “ምስጋና ለአላህ ይገባው የዓለማት ጌታ ለኾነው የምትለዋ የሚደጋገሙ የሆኑ ሰባት ሱረቱል ፋቲሐህን እና ታላቁ ቁርኣንን ተሰጠኝ”*። عَنْ أَبِي سَعِيدِ بْنِ الْمُعَلَّى، قَالَ كُنْتُ أُصَلِّي فَدَعَانِي النَّبِيُّ صلى الله عليه وسلم فَلَمْ أُجِبْهُ قُلْتُ يَا رَسُولَ اللَّهِ إِنِّي كُنْتُ أُصَلِّي‏.‏ قَالَ ‏”‏ أَلَمْ يَقُلِ اللَّهُ ‏{‏اسْتَجِيبُوا لِلَّهِ وَلِلرَّسُولِ إِذَا دَعَاكُمْ‏}‏ ثُمَّ قَالَ أَلاَ أُعَلِّمُكَ أَعْظَمَ سُورَةٍ فِي الْقُرْآنِ قَبْلَ أَنْ تَخْرُجَ مِنَ الْمَسْجِدِ ‏”‏‏.‏ فَأَخَذَ بِيَدِي فَلَمَّا أَرَدْنَا أَنْ نَخْرُجَ قُلْتُ يَا رَسُولَ اللَّهِ إِنَّكَ قُلْتَ لأُعَلِّمَنَّكَ أَعْظَمَ سُورَةٍ مِنَ الْقُرْآنِ‏.‏ قَالَ ‏”‏‏{‏الْحَمْدُ لِلَّهِ رَبِّ الْعَالَمِينَ‏}‏ هِيَ السَّبْعُ الْمَثَانِي وَالْقُرْآنُ الْعَظِيمُ الَّذِي أُوتِيتُهُ ‏”‏‏.‏
15፥87 *ከሚደጋገሙ የኾኑን ሰባትን እና ታላቁንም ቁርኣን በእርግጥ ሰጠንህ*፡፡ وَلَقَدْ آتَيْنَاكَ سَبْعًا مِّنَ الْمَثَانِي وَالْقُرْآنَ الْعَظِيمَ

የሚደጋገሙ ሰባት አንቀጾች ሱረቱል ፋቲሓህ ናት፤ ምክንያቱም ሱረቱል ፋቲሓህ ሰባት አናቅጽ አላት፤ በተጨማሪም ነብያችን”ﷺ” ነግረውናል፤ ይህቺ ሱራህ በቁርኣን ውስጥ ታላቂቱ ሱራ ብትባልም ከቁርኣን “ወ” وَ ማለትም “እና” በሚል መስተጻምር መለየቱ ሱረቱል ፋቲሓህ የቁርኣን እናት ማለት መሰረት መሆኗን ያሳያል፦

ጃምዒ አት-ተርሚዚ መጽሐፍ 47, ሐዲስ 3415

አቢ ሁረይራህ”ረ.ዐ” እንደተረከው፦ “የአላህ መልእክተኛ”ﷺ” እንዲህ አሉ፦ *አል-ሐምዱሊሏህ የቁርኣን እናት፣ የመጽሐፉ እናት እና ሰባት የተደጋገሙ ናት*። عَنِ ابْنِ أَبِي ذِئْبٍ، عَنِ الْمَقْبُرِيِّ، عَنْ أَبِي هُرَيْرَةَ، قَالَ قَالَ رَسُولُ اللَّهِ صلى الله عليه وسلم ‏ “‏ الْحَمْدُ لِلَّهِ أُمُّ الْقُرْآنِ وَأُمُّ الْكِتَابِ وَالسَّبْعُ الْمَثَانِي ‏”

መልስ

ኢብን መስዑድ አል-ፋቲሃ የቁርአን አካል መሆኗን ስላልካደ አሁንም ከእነዚህ ሐዲሶች ጋር ጠብ አይኖረውም፡፡ የእርሱ አቋም በጽሑፍ መስፈር የለበትም የሚል እንጂ ለሙሐመድ አልወረደም ወይም የቁርአን አካል አይደለም የሚል አልነበረም፡፡ ሱራ 17፡87 እና የአል-ቡኻሪ ዘገባ ሱረቱ አል-ፋቲሃንና ቁርአንን ለያይተው ማስቀመጣቸው የኢብን መስዑድን አቋም የሚደግፍ ይመስላል፡፡ “ከሚደጋገሙ የኾኑን ሰባትን እና ታላቁንም ቁርኣን በእርግጥ ሰጠንህ” ብሎ ሲል የሚደጋገሙ ሰባት የተባሉት የአል-ፋቲሃ ሰባቱ አንቀፆችና ታላቁ ቁርአን የተባለው መጽሐፍ ሁለት ነገሮች መሆናቸውን መገንዘብ ይቻላል፡፡ የአል-ቡኻሪ ሐዲስም ይህንኑ የሚያጠናክር ነው፡-

“…Shall I not teach you the most superior Surah in the Qur’an?” He said, ‘(It is), ‘Praise be to Allah, the Lord of the worlds. ‘ (i.e., Surat Al-Fatiha) which consists of seven repeatedly recited Verses and the Magnificent Qur’an which was given to me.”

“…በቁርአን ውስጥ ታላቂቱን ሱራ ላስተምርህ አይገባኝምን? እንዲህም አለ፡- ምስጋና ለአላህ ይሁን የዓለማቱ ጌታ ለሆነው (ማለትም ሱረቱ አል-ፋቲሃ) በተደጋጋሚ የሚነበነቡ ሰባት አንቀፆችን የያዘችውንና ለኔ የተሰጠኝ ታላቁ ቁርአን፡፡” (Sahih al-Bukhari፡ Book 66, Hadith 28)

በአል-ቡኻሪ ሐዲስ መሠረት አል-ፋቲሃ የቁርአን አካል ነው ደግሞም ከቁርአን ተለይቶ ታይቷል፡፡ ይህም ለሙሐመድ የወረደለት ቁርአን አካል ቢሆንም በጽሐፍ የሰፈረው ቁርአን አካል አይደለም የሚለውን የኢብን መስዑድን አቋም የሚደግፍ ነው፡፡

አብዱል

የሚያጅበው ነገር ቁርኣን ላይ ችግር እንዳይኖር አላህ በነብያችን”ﷺ” ሰሃባዎች ዘመን ሁሉን ነገር አስተካክሎታል፤ ቁርኣን እንደ በፊቶቹ መጽሐፍት ከፊቱና ከኃላው ሰዎች ውሸት እንዳይጨመሩበት የዓለማቱ ጌታ ይጠብቀዋል፦

41፥42 *ከኋላውም ከፊቱም ውሸት አይመጣበትም፤ ጥበበኛ ምስጉን ከኾነው ጌታ የተወረደ ነው*፡፡ لَّا يَأْتِيهِ ٱلْبَٰطِلُ مِنۢ بَيْنِ يَدَيْهِ وَلَا مِنْ خَلْفِهِۦ ۖ تَنزِيلٌۭ مِّنْ حَكِيمٍ حَمِيدٍۢ

15፥9 *እኛ ቁርኣንን እኛው አወረድነው፡፡ እኛም ለእርሱ ጠባቂዎቹ ነን*፡፡ إِنَّا نَحْنُ نَزَّلْنَا الذِّكْرَ وَإِنَّا لَهُ لَحَافِظُونَ

መልስ

ሐሰት! በሰው ልጆች ታሪክ እንደ ቁርአን በብዙ ውዝግቦች የተከበበና በትክክል አለመጠበቁ ግልፅ ሆኖ የሚታይ መጽሐፍ የለም ብንል ማጋነን አይሆንም፡፡ ይህንን ሃቅ በዚህ ድረገፅ ላይ በስፋት ስለጻፍንበት ለአሁን አንድ ምሳሌ ብቻ ጠቅሰን እናጠቃልላለን፡፡

የመጀመርያዎቹ ሙስሊሞች በርካታ የቁርአን ክፍሎች ጠፍተው መቅረታቸውን መስክረዋል፡፡ ለምሳሌ ያህል በኡበይ ቢን ካዕብ ምስክርነት መሠረት ሱረት አል-አሕዛብ መጀመርያ “ሲወርድ” ርዝመቱ የሱረት አል-በቀራ ያህል እንደነበርና ገሚሱ ጠፍቆ አሁን ያለው ብቻ ሊተርፍ ችሏል፡-

عن عاصم بن بهدلة عن زر قال

قال لي أبي بن كعب : كأين تقرأ سورة الأحزاب أو كأين تعدها قال قلت له ثلاثا وسبعين آية فقال قط لقد رأيتها وإنها لتعادل سورة البقرة ولقد قرأنا فيها الشيخ والشيخة إذا زنيا فارجموهما البتة نكالا من الله والله عليم حكيم

Narrated ‘Aasim ibn Bahdalah, from Zirr, who said:

Ubayy ibn Ka‘b said to me: How long is Soorat al-Ahzaab when you read it? Or how many verses do you think it is? I said to him: Seventy-three verses. He said: Only? There was a time when it was as long as Soorat al-Baqarah, and we read in it: “The old man and the old woman, if they commit zina, then stone them both, a punishment from Allah, and Allah is Almighty, Most Wise.”

ዓሲም ኢብን ባህደላህ ከአዚር ሰምቶ እንደተናገረው፡-

ኡበይ ኢብን ካዕብ እንዲህ አለኝ፡- አንተ ስታነበው ሱረት አል-አሕዛብ ምን ያህል ይረዝማል? ወይም ምን ያህል አንቀጽ ነው ብለህ ታስባለህ? ሰባሦስት አንቀጽ ነው ብዬ መለስኩለት፡፡ እርሱም ይህ ብቻ ነው? በማለት መለሰልኝ፡፡ የሱረት አል-በቀራ ያህል የሚረዝምበት ጊዜ ነበር፡፡ በውስጡም እንዲህ የሚል ነበር፡- “ጎልማሳ ወንድና ሴት ዝሙት ከፈፀሙ ሁለቱንም ውገሯቸው፤ ይህም ከአላህ ዘንድ የሆነ ቅጣት ነው፤ አላህ ሁሉን ቻይ ጥበበኛም ነው፡፡” (ሙስናድ አሕመድ ሐዲስ ቁጥር 21245)

ኢብን ሐዝም የተባለ ሊቅ ይህ ሐዲስ ሳሂህ መሆኑ የቀን ፀሐይ ያህል ግልፅ መሆኑን ተናግሯል፡፡ ኢብን ከሢር ደግሞ ኢስናዱ የሐሰን ደረጃ እንዳለው ተናግሯል፡፡ ታላላቅ ሙስሊም ሊቃውንት ይህ ሐዲስ እውነት መሆኑን ይስማሙበታል፡፡ ሱረት አል-በቀራ (የላሚቷ ምዕራፍ) 286 አንቀፆች ያሉት ሲሆን ሱረት አል-አሕዛብ ደግሞ 73 አንቀፆች ብቻ ናቸው ያሉት ስለዚህ 213 ያህል አንቀፆች ከአላህ መጽሐፍ ውስጥ ጠፍተዋል ማለት ነው፡፡

ቅዱስ ቁርአን