ሙሐመድ በአይሁድ ላይ የፈፀሙት ግፍ

ሙሐመድ በአይሁድ ላይ የፈፀሙት ግፍ

ከእስልምና በፊት ብዙ የአይሁድ ማሕበረሰቦች በአረብያ ውስጥ ለብዙ ክፍለ ዘመናት ኖረዋል፡፡ ጥንካሬያቸው ሲታሰብ በወታደራዊ ኃይል ሳይደራጁ እነዚህን ማሕበረሰቦች መጋፈጥ ጥፋትን መጋበዝ በመሆኑ ሙሐመድ ምቹ ጊዜ እስኪመጣ ድረስ በተቻለ መጠን እነርሱን አሳምኖ ከጀርባቸው ማሰለፍን ቀዳሚ ምርጫ አድርገው ነበር፡፡ “በመገለጦቻቸው” አሞጋግሶ ኩራት እንዲሰማቸው በማድረግ ለእስልምና ልባቸውን ማስከፈት የመጀመርያው ዘዴ ሲሆን ስለ አይሁድ ደግ ደጉን የሚናገሩት የቁርኣን ክፍሎች “ወረዱ” የተባሉት በዚያን ጊዜ እንደነበር ይነገራል፡፡

“የእስራኤል ልጆች ሆይ! ያችን በናንተ ላይ የለገስኳትን ጸጋዬንና እኔም በዓለማት ላይ ያበለጥኳችሁ (አባቶቻችሁን በጊዜያቸው ከነበሩት ዓለማት ያበለጥኩዋቸው)[1] መኾኔን አስታውሱ፡፡” (የላም ምዕራፍ 2፡47)

አብርሃምን የመሳሰሉትን በአይሁድ ዘንድ ከበሬታ ያላቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ ስብዕናዎች ማሞጋገስ የአይሁድን ልብ ለማማለል ጥቅም ላይ የዋለ ሌላው ዘዴ ነበር (2፡124፣ 117)፡፡ በተጨማሪም የስግደት አቅጣጫ (ቂብላ) ወደ ኢየሩሳሌም እንዲሆን ተደረገ፡፡ ሙሐመድም ወደ ኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ በሌሊት በተዓምር መሄዳቸውን የሚገልፅ ታሪክ ተወራ (17፡1)፡፡ ነገር ግን በጣት ከሚቆጠሩት በስተቀር አይሁድ ሙሐመድን እንደ ነቢይ ባለመቀበላቸው ምክንያት እነዚህ ሁሉ ጥረቶች መና ሆነው ቀሩ፡፡ ስለዚህ የሙገሳ መገለጡ ወደ እርግማንና ወደ ዘለፋ ተቀየረ፡-

ከነዚያ አይሁዳውያን ከኾኑት ሰዎች ንግግሮችን ከስፍራዎቹ የሚያጣምሙ አልሉ፡፡ «ሰማንም አመጽንም የማትሰማም ስትኾን ስማ» ይላሉ፡፡ በምላሶቻቸውም ለማጣመምና ሃይማኖትንም ለመዝለፍ ራዒና ይላሉ፡፡ እነሱም «ሰማን ታዘዝንም ስማን ተመልከተንም» ባሉ ኖሮ ለነሱ መልካምና ትክክለኛ በኾነ ነበር፡፡ ግን በክህደታቸው አላህ ረገማቸው፡፡ ጥቂትንም እንጅ አያምኑም፡፡ (የሴቶች ምዕራፍ 4፡46)

  ወደ ኢየሩሳሌም የነበረውም ቂብላ ወደ መካ ተመለሰ፡፡

“ከሰዎቹ ቂሎቹ «ከዚያች በርሷ ላይ ከነበሩባት ቂብላቸው ምን አዞራቸው?» ይላሉ፤ «ምሥራቁም ምዕራቡም የአላህ ነው፤ የሻውን ሰው ወደ ቀጥተኛው መንገድ ይመራል» በላቸው …. ያችንም በርሷ ላይ የነበርክባትን አቅጣጫ መልክተኛውን የሚከተለውን ሰው ወደ ክህደት ከሚመለሰው ሰው ልናውቅ (ልንገልጽ) እንጅ ቂብላ አላደረግናትም …. የፊትህን ወደ ሰማይ መገላበጥ በእርግጥ እናያለን፡፡ ወደምትወዳትም ቂብላ እናዞርሃለን፡፡ ስለዚህ ፊትህን ወደ ተከበረው መስጊድ (ወደ ካዕባ) አግጣጫ አዙር፡፡ የትም ስፍራ ብትኾኑም (ስትሰግዱ) ፊቶቻችሁን ወደርሱ አግጣጫ አዙሩ፡፡” (የላም ምዕራፍ 2፡142-144)

ከአይሁድ ወገን የሆኑ ሰዎች በአላህ ተረግመው ወደ ዝንጀሮነትና ወደ አሳማነት[2] እንደተቀየሩ የሚናገሩ የቁርኣን ጥቅሶች “ወረዱ”ተባለ (7፡166፣ 2፡65፣ 5፡60)፡፡ አይሁድንና ክርስቲያኖችን ተዋርደው ግብርን (ጂዝያ) እስኪከፍሉ ድረስ መዋጋት እንደሚያስፈልግም ተነገረ (9፡29)፡፡

በሙሐመድ ዘመን ብዙ ጠንካራ የአይሁድ ጎሣዎች በአረብያ ይኖሩ ነበር፤ ነገር ግን በሙሐመድ የተደራጀው የጂሃድ ጦር በቃላት ሊገለፅ የማይችል ግፍ ፈጽሞባቸዋል፤ ለአስከፊ ሰቆቃም ዳርጓቸዋል፡-

በኒ ቀይኑቃዕ – ሙሐመድ በበድር ጦርነት ላይ ድልን በመቀዳጀታቸው ምክንያት በሠራዊታቸው ዘንድ የነበረው ወኔ ከፍ ብሎ ነበር፡፡ በኒ ቀይኑቃዕ በመዲና ከተማ ጠረፍ ላይ የሚኖሩ የአይሁድ ጎሣ ነበሩ፡፡ ወርቅ በማንጠር ሥራ ስለሚተዳደሩ ባለጠጎች መሆናቸው አልቀረም፡፡ ሙሐመድ በቅርቡ በበድር ጦርነት ካሸነፏቸው ቁረይሾች ጋር አብረዋል በሚል ሰበብ ነገር ይፈልጓቸው ጀመር፡፡ በአንዲት ሙስሊም ሴትና በአንድ አይሁዳዊ ወንድ መካከል በተፈጠረ ግጭት ሌላ ሙስሊም ወንድ አይሁዳዊውን በመግደሉና አይሁድም ሙስሊሙን ሰው በመግደላቸው ምክንያት ሙሐመድ ሠራዊት በማዝመት አስከበቧቸው፡፡ ቀይኑቃዎች አብደላህ ቢን ኦበይ ከተሰኘ የኸዝራጅ ጎሣ መሪ ጋር ወዳጅነት ስለነበራቸው ሊታደጋቸው ሊመጣ እንደሚችል በመገመት ከበባውን ተቋቁመው ቆዩ፡፡ ነገር ግን አብደላህ በጊዜ ሊደርስላቸው ስላልቻለ ኃይላቸው ተሟጦ ተረቱ፡፡ ሙሐመድም እጆቻቸው ወደ ኋላ ታስረው ከምሽጋቸው እንዲወጡ አዘዙ፡፡ ለመገደልም “በእዝነቱ ነቢይ” ፊት ቀረቡ፡፡ ነገር ግን አብደላህ በአሥራ አንደኛው ሰዓት በመምጣት ሙሐመድን በብርቱ ስለለመናቸው ከተደገሰላቸው ጭፍጨፋ አመለጡ፡፡ ጭንቅላቶቻቸውን ከመቆረጥ ቢተርፉም ንብረታቸውን ተዘርፈው ከአገር ከመባረር ግን ሊተርፉ አልቻሉም፡፡[3]

በኒ ናዲር – ሙሐመድ ከዚህ የአይሁድ ጎሣ ጋር በሰላም ለመኖር የሰላም ውል ገብተው ነበር፡፡ ወታደራዊ ክንዳቸው ከፈረጠመ በኋላ ግን ቃል ኪዳን አፍርሰው ከመካውያን ጋር አብረዋል እንዲሁም ነቢዩን ለመግደል ከመዲና አስመሳዮች ጋር አሢረዋል የሚል ምክንያት በመፍጠር ሰኔ 4 – 625 ዓ.ም. ጦራቸውን አዘመቱባቸው፡፡ ሙስሊም ጂሃዳውያንም የአይሁድን ንብረት ማጥፋትና የፍራፍሬ ተክሎቻቸውን መቁረጥ ተያያዙ፡፡ በንብረታቸው ላይ የደረሰው ውድመት ወኔያቸውን ስለሰለበ አይሁድ እጅ ከመስጠት ሌላ ምርጫ አልነበራቸውም፡፡ በእስላማዊ ትውፊቶች መሠረት ከሁለት ወይም ከሦስት ሳምንታት ከበባ በኋላ ነበር የተረቱት፡፡ ሙሐመድ ባስቀመጡት ቅድመ ሁኔታ መሠረት የጦር መሣርያዎቻቸውን በማስረከብ ከአገር ለመሰደድ ተስማሙ፡፡ የሚወዷትን የመዲናን ከተማ በመልቀቅ ባዶ እጃቸውን እግር ወደመራቸው ሄዱ፡፡ ሙስሊም ጂሃዳውያንም ንብረታቸውን ዘረፉ፣ መሬታቸውንም ተከፋፈሉ፡፡[4]

በኒ ቁረይዛ – በኒ ናዲር ላይ ጥቃት በተፈፀመ ጊዜ በኒ ቁረይዛ “ከሙሐመድ ጋር የሰላም ስምምነት አለን” በሚል አጉል ታማኝነት ሳይረዷቸው ቀሩ፡፡ እነሆ የእነርሱም እጣ ከሁለት ዓመታት በኋላ ደረሰ፡፡ ሙሐመድ 3,000 ወታደሮችና 36 ፈረሰኞችን በማስከተል ድንገት በማለዳ ተከሰቱ፡፡ ከሁለት ወይም ከሦስት ሳምንታት በኋላ በኒ ቁረይዛ እጅ ሰጡ፡፡ ሴቶችና ህፃናትን ጨምሮ ቁጥራቸው ወደ 2000 ይሆን ነበር፡፡ ወንዶቹ ከሴቶችና ከህፃናት ተለይተው እጆቻቸው ወደ ኋላ ታስሮ እንዲቀርቡ ተደረገ፡፡ “የእዝነቱ ነቢይም” ሰቆቃቸውን በመመልከት ሀሴት ያደርጉ ነበር፡፡ ከዝያም ፍርዳቸው ምን መሆን እንደሚገባው ይወስን ዘንድ ሰዓድ ኢብን ሙኣዝ የተሰኘ ሰው ዳኛ አድርገው ሾሙ፡፡ ኢብን ሙኣዝ በወቅቱ በአንድ አይሁዳዊ በተወረወረ ቀስት ቆስሎ ስለነበር ልቡ በበቀል ተሞልቶ ነበር፡፡ ይህንንም አጋጣሚ በብዙዎች ላይ የሞት ፍርድ ለመፍረድ ተጠቀመበት፡፡ ከሰባት መቶ እስከ ስምንት መቶ የሚገመቱ አይሁድ ወንዶች እጆቻቸው ታስረው ወደ መዲና የገበያ ቦታ እንዲመጡ ተደረገ፡፡ ሙስሊሞች ሌሊቱን ጉድጓድ ሲቆፍሩ እነዚህ አይሁድ በጭንቀት ውስጥ ሆነው ምህረትን ይለምኑ ነበር፡፡ በሚቀጥለው ቀን ማለዳ ነቢዩ ከአጃቢዎቻቸው ጋር በመምጣት ተቀመጡ፡፡ የሞት ፍርድ የተፈረደባው አይሁድም ስድስት ስድስት ሆነው ወደ ጉድጓዱ እንዲቀርቡ ተደረገ፡፡ አንገታቸውን በጉድጓዱ አፋፍ ላይ አድርገው እንዲተኙ ከተደረጉ በኋላ ሁላቸውም በሰይፍ ታረዱ፡፡[5]

የኸይበር ወረራ – ኸይበር በአረብ በረሃ ውስጥ የሚገኝ አካባቢ ቢሆንም በልምላሜው ይታወቅ ነበር፡፡ የብዙ ምንጮች መገኛ በመሆኑ ምክንያት ፍሬ የሚያፈሩ ዛፎችም በብዛት ይገኙበት ነበር፡፡ በመስከረም ወር 628 ዓ.ም. ሙሐመድ 1,600 የጂሃድ ሠራዊት አስከትለው ድንገት ከተፍ አሉ፡፡ አይሁድ ለየዕለት ሥራዎቻቸው ማለዳ ሲነሱ “በእዝነቱ ነቢይ” የሚመራው የጂሃድ ሠራዊት እንደ ደራሽ ውኀ ፈሰሰባቸው፡፡ ወንዶች የራሳቸውንና የቤተሰባቸውን ሕይወት ከዚህ ምህረት የለሽ የሰባተኛው ክፍለ ዘመን የሽብር ሠራዊት መቅሠፍት ለመታደግ  በብርቱ ቢጋደሉም ተመጣጣኝ አቅም ስላልነበራቸው ተረቱ ፡፡ መሪያቸው የነበረው ወጣቱ ኪናናም ተያዘ፡፡ ሙሐመድ ኪናና ባለጠጋ መሆኑን ያውቁ ነበር፡፡ በሠርጉ እለት ብዙ የወርቅ ስጦታ እንደተቀበለና ለመካ ነዋሪዎችም እንደሚያበድር መረጃ ነበራቸው፡፡ ነገር ግን የወርቁን ማስቀመጫ የት እንደደበቀ ስላላወቁ ለማውጣጣት ዙበይር የተሰኘ አጃቢያቸው እርሱንና የአጎቱን ልጅ እንዲያሰቃያቸው ትዕዛዝ ሰጡ፡፡ ዙበይርም በዝርግ ብረት እሳት ደረታቸው ላይ በማስቀመጥ ክፉኛ አሰቃያቸው፡፡ በመጨረሻም ንብረቱ የት እንደተደበቀ ከተናገሩ በኋላ “የእዝነቱ ነቢይ” እንዲታረዱ አዘዙ፡፡ ሁለቱም የእስላም ካራ ሰለባዎች ሆኑ፡፡ ኪናና ሳፊያ የተሰኘች መልከ መልካም ሚስት ነበረችው፡፡ ሙሐመድም የ17 ዓመቷን ወጣት ሚስታቸው ትሆን ዘንድ ወሰዷት፡፡ ከሞት የተረፉትም አይሁድ የዚማ ቃል ኪዳን በመግባት ባርያዎች ተደረጉ፡፡[6]

ድንቄም የእዝነቱ ነቢይ!

——————–

[1] በቅንፍ የተጨመረው በአረብኛው ንባብ ውስጥ አይገኝም

[2] ፅንፈኛ ሙስሊሞች አይሁዶችን ብዙ ጊዜ “አሳማ” (ኸንዚር) በማለት ሲጠሩ መስማት የተለመደ ነው፡፡

[3] Guillaume. The Life of Muhammad; p. 363

[4] Ibid., p. 437

[5] Ibid., p. 461

[6] Ibid., p. 510

 

ነቢዩ ሙሐመድ