ሰይፍ የታጠቀው ነቢይ

ሰይፍ የታጠቀው ነቢይ

የትዳር አጋራቸው ከዲጃና አጎታቸው አቡጧሊብ ተከታትለው በመሞታቸው ምክንያት 619 ዓ.ም. ለሙሐመድ ጥሩ ዓመት አልነበረም፡፡ ሁለቱ ሰዎች ተሰሚነት ስለነበራቸውና አደጋ እንዳይደርስባቸው ከለላ ያደርጉላቸው ስለነበር ሁለቱንም በተከታታይ ማጣት ትልቅ ጉዳት ነበር፡፡ ይህ ሁኔታ ተጋላጭ እንዲሆኑና ስደት እንዲበረታባቸው ስላደረገ ሊመጣባቸው ካለው አደጋ ለማምለጥ በፈጣን አእምሯቸው መላ መምታት ነበረባቸው፡፡ ስለዚህም በጣም በተጠና ሁኔታ በሚስጥር በወቅቱ ያሥሪብ ተብላ በምትታወቀው (ኋላ ላይ መዲና በተሰኘችው) ከተማ ውስጥ ይኖሩ ከነበሩት የአረብ ጎሣ መሪዎች ጋር መረጃዎችን መለዋወጥ ጀመሩ፡፡

ያሥሪብ ከሞላ ጎደል የአይሁድ ከተማ ነበረች፡፡ ነገር ግን አውስና ኸዝራጅ የተሰኙ እሳትና ጭድ የሆኑ የአረብ ጎሣዎችም ይኖሩባት ነበር፡፡ እነዚህ ጎሣዎች በአይሁድ የበላይነትና ስኬት ይቀኑ ነበር፡፡ ሙሐመድ ሁለቱን ጎሣዎች የበላይ እንደሚያደርጉና አይሁድን እንደሚያዋርዱ ቃል በመግባት አስማምተዋቸው “የአቃባ ቃል ኪዳን” በመባል የሚታወቀውን ስምምነት ከተወካዮቻቸው ጋር ተፈራረሙ፡፡

ወደ ያሥሪብ ከመንቀሳቀሳቸው በፊት ከተማይቱን ማዘጋጀት ስለነበረባቸው ለሁለቱ የአረብ ጎሣዎች ጠላት የነበሩትን የመካ ቁረይሾች የሚያብጠለጥሉና አይሁድን የሚያሞጋግሱ “መገለጦችን” መናገር ጀመሩ፡፡ ይህም ልባቸው በቁረይሾች ጥላቻ የተሞላው ሁለቱ የአረብ ጎሣዎች በአዲሱ ነቢይ መሪነት ድል የሚነሱበትን ቀን እንዲናፍቁና አይሁድ ደግሞ ሙሐመድን እንደ ወዳጅ እንዲቆጥሯቸው አደረገ፡፡ አይሁድ በነዚህ መገለጦች ስለተዘናጉ ወዳጅ መስሎ በመቅረብ እነርሱን ለማጥፋት የተጠነሰሰውን ሤራ አላወቁም ነበር፡፡

ሙሐመድ አስፈላጊ የሆኑትን ዝግጅቶች ካጠናቀቁ በኋላ በ622 ዓ.ም. በሌሊት ከተወሰኑ ተከታዮቻቸው ጋር ወደ ያሥሪብ አቀኑ፡፡ ይህም ጉዞ “ሒጅራ” በመባል የሚታውቅ ሲሆን እስልምና ከአንዱ ምዕራፍ ወደሌላው የተሸጋገረበት ታሪካዊ ክስተት ነበር፡፡ ሒጅራ በእስልምና ውስጥ ካለው ጉልህ ሚና የተነሳ 622 የእስልምና ዘመን መቁጠርያ መጀመርያ ለመሆን በቅቷል፡፡ ከሒጅራ በኋላ የእስልምናው ነቢይ ሙሐመድ “ከሰላማዊ” ሰባኪነት ወደ ጦር አበጋዝነት ተለወጡ፡፡  በመዲና ኃይላቸውን ካጠናከሩ በኋላ አይሁድን የሚያሞጋግሱ “መገለጦቻቸው” እነርሱን በሚያንቋሽሹ መገለጦች ተተኩ፡፡ ባገኟቸው አጋጣሚዎች ሁሉ እነርሱን ማጥቃትና ማዳከም ተያያዙ፡፡ በመካ ነዋሪዎችም ላይ ጥቃቶችን ማድረስ ጀመሩ፡፡ ከዚህ በኋላ ጂሃድ የሕይወታቸው መዳፍና ፈለግ ሆነ፡፡

አክራሪ ሙስሊሞች የመጀመርያዎቹን የሙሐመድ ዓመታት “ዘመነ ብዕር” በማለት ይጠሯቸዋል፡፡ በመዲና የነበሩትን የመጀመርያዎቹን ዓመታት ደግሞ “ዘመነ ሚዛን” ይሏቸዋል፡፡ ይህም ማለት እንደየሁኔታው ብዕርንና ሰይፍን እያፈራረቁ መጠቀም፤ ማለትም ምቹ ሁኔታ ሲፈጠር ጠላትን ማጥቃት፤ ነገሮች ካልተመቻቹ ደግሞ ውጊያውን የሐሳብ ማድረግ ማለት ነው፡፡ ሙሐመድ በወታደራዊ አቅም ከተደራጁ በኋላ የሚገኙትን ዓመታት ደግሞ “ዘመነ ሰይፍ” በማለት ይጠሯቸዋል፡፡ ይህ ጊዜ ሰዎች በግድም ሆነ በውድ የሚሰልሙበት አለዚያ ደግሞ ተዋርደው ለእስልምና ግብርን እየከፈሉ የሚኖሩበት ዘመን ነበር፡፡ሙሐመድ “የነቢይነት” አግልግሎታቸውን ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ የመካ ከተማን በኃይል እስከተቆጣጠሩበት ጊዜ ድረስ እንቅስቃሴያቸው ሁሉ የተጠናና በሦስት ደረጃዎች የተከፋፈለ መሆኑን እናስተውላለን፡፡ በመካ ከተማ በነበሩ ጊዜ ተቃዋሚዎቻቸውን ገሃነም እንደሚገቡ ከማስፈራራት የዘለለ አካላዊ ጥቃት ሲያደርሱ አንመለከትም፡፡ ወደ መዲና በገቡ በመጀመርያዎቹ ዓመታት ደግሞ ለአዲሱ ሃይማኖታቸው እንቅፋት እንደሚሆኑ የገመቷቸውን ተቃዋሚዎቻቸውን

አል-በታል የሚል ስያሜ ያለው የነቢዩ ሙሐመድ እንደሆነ የተነገረለት ሰይፍ፤ በኢስታንቡል ከተማ ቶፕካፒ ቤተ መዘክር ውስጥ ይገኛል፡፡[1]

ሸማቂዎችን በመላክ አስገድለዋል፡፡ በመካ ነጋድያን ላይ ድንገተኛ ጥቃቶችን በመፈፀምም ያዘርፉ ነበር፡፡ ወታደራዊ ኃይላቸውን እስኪያደራጁ ድረስ ፊት ለፊት ከመጋፈጥ ይልቅ በጀርባ በኩል እነርሱን የሚያዳክሙ ሥራዎችን እየሠሩ በድርድርና የተለያዩ የሰላም ስምምነቶችን በመፈራረም ምቹ ጊዜ እስኪመጣላቸው ድረስ ይጠባበቁ ነበር፡፡ ትልቅ አቅም የሚጠይቁ ከባባድ ጦርነቶችን ከማድረግ ይልቅ በግለሰቦችና በአናሳ ቡድኖች ላይ በማነጣጠር እዚያም እዚህም ፈጣን ጥቃቶችን በመፈፀም ጠላቶቻቸውን ያሸብሩ ነበር፡፡ ከጠላቶቻቸው አቅም ጋር የሚመጣጠን በቂ ወታደራዊ ኃይል እንዳደራጁ ካረጋገጡ በኋላ ግን ቀደም ሲል የተፈራረሟቸውን የሰላም ስምምነቶች በማፍረስ ትልልቅ የውጊያ ግንባሮችን መክፈት ጀመሩ፡፡ ዋና ጠላቶቻቸው የነበሩትን ቁረይሾችንም በመግጠም ድል ነሷቸው፡፡ የመካ ከተማንም ተቆጣጠሩ፡፡ በማስከተልም መላውን የአረብ ባህረ ገብ ምድር በኃይል አሰለሙ፡፡[2]

ሙሐመድ በመዲና በኖሩባቸው 10 ዓመታት ውስጥ 27 ውጊያዎች ላይ በአካል መሳተፋቸውን ኢብን ኢስሐቅና አል-ጦበሪ ዘግበዋል፡፡[3] እነዚህም የውጊያ ግንባሮች የሚከተሉት ናቸው፡-

•  አል አብዋእ

•  ቡወጥ

•  አል ዑሻይራህ

•  የመጀመርያው የበድር ጦርነት

•  ታላቁ የበድር ጦርነት

•  በኒ ሱለይመን

•  አል ሰዊቅ

•  ገተፈን

•  በኒ ሊህየን፡፡

•  ዙ ቀደር፡፡

•  በኒ አል-ሙስጠሊቅ

•  ሁደይቢያ

•  ኸይበር

•  የመካ መያዝ

•  ሁነይን

•  አል ጣኢፍ

•  ተቡክ

•  ባህረን

•  በኒ ቀይኑቃዕ

•  ኡሁድ

•  ሐመር ዑል-አሰድ

•  በኒ ናዲር

•  የነኽል ዘቱልሪቃ

•  የበድር የመጨረሻው ጦርነት

•  ዱመት ዑል-ጀንደል

•  አል-ኸንደቅ

•  በኒ ቁረይዛ

ሙሐመድ እራሳቸው በዘጠኝ ጦርነቶች ውስጥ በአካል በመግባት ሰይፍ መዘዋ፡- በድር፣ ኡሁድ፣[4] አል-ኸንደቅ፣ ቁረይዛ፣ አል-ሙስጠሊቅ፣ ኸይበር፣ [መካን] መያዝ፣  ሁነይን እና አል ጣኢፍ፡፡ በተጨማሪም ኢብን ኢስሐቅ በሙሐመድ ትዕዛዝ ተከታዮቻቸው የፈፀሟቸውን 35 ጥቃቶች ዘርዝረዋል፡፡[5]

ድንቄም የሰላም ነቢይ!

—————-

[1] በተከታዩ ድረ-ገፅ ላይ 9 የሚሆኑ የነቢዩ ንብረት እንደነበሩ የሚነገርላቸው ሰይፎች ከነምስላቸው ይገኛሉ፡-

http://www.usna.edu/users/humss/bwheeler/swords/index_of_swords.html

[2] Mark A. Gabriel. Islam and Terrorism: What the Qur’an Really Teaches about Christianity, Violence and the Goals of the Islamic Jihad; Charisma House Publishers, 2002, p. 88

[3] Guillaume. The Life of Muhammad; pp. 659-660

[4] የኡሁድ ጦርነት ነቢዩ የተሸነፉበት ጦርነት ነበር፡፡ በዚህ ጦርነት ላይ አጎታቸው ሐምዛ የሞቱ ሲሆን ሙሐመድ እራሳቸው ከንፈራቸው ተሰንጥቆ የፊት ጥርሶቻቸው ረግፈዋል፡፡ የሙሐመድ እንደሆኑ የሚነገርላቸው ሁለት ጥርሶች ዛሬ በኢስታንቡል ሙዚየም ውስጥ ተቀምጠው ይገኛሉ፡፡ (Paul Fregosi. Jihad in the West, Muslim Conquest from 7th to 21st Centuries; 1998, p. 53)

[5] Guillaume. The Life of Muhammad; pp. 659-660

 

ነቢዩ ሙሐመድ