የቁርኣን ግጭቶች – ሙስሊሞች የማያምኑ ሰዎችን እንዲዋጉ ወይስ ይቅር እንዲሉ ነው የታዘዙት?

ሙስሊሞች የማያምኑ ሰዎችን እንዲዋጉ ወይስ ይቅር እንዲሉ ነው የታዘዙት?

ማሳሰብያ፡- በሰማያዊ የተጻፈው የኛ ሲሆን በጥቁር የተጻፈው የእርሱ ነው፡፡

እንዲዋጉ፡-

ሱራ 9፥29 “ከነዚያ መጽሐፍን ከተሰጡት ሰዎች፣ እነዚያን በአላህ በመጨረሻዉ ቀን የማያምኑትን፣ አላህና መልክተኛዉ እርም ያደረጉትንም እርም የማያደርጉትንና እዉነተኛዉንም ሃይማኖት የማይቀበሉትን እነርሱ የተዋረዱ ሆነዉ ግብርን በእጆቻቸው እስከሚሰጡ ድረስ ተዋጉዋቸው።”

ይቅር እንዲሉ፡-

ሱራ 45፥14 “ለነዚያ ለአመኑት ሰዎች ምሕረት አድርጉ” በላቸው፤ ለእነዚያ የአላህን ቀኖች ለማይፈሩት ይምራሉና፣ ሕዝቦችን ይሠሩት በነበሩት ነገር ይመነዳ ዘንድ ምሕረት አድርጉ” በላቸው።”

መልስ

“አህለ አዝ-ዚማህ” أهل الذمة ማለት በሙስሊም ሸሪዓህ ሕገ-መንግሥት የሚኖሩ ሙሥሊም ያልሆኑ ሰዎች ናቸው፤ አምላካችን አላህ ስለ አህለ አዝ-ዚማህ እንዲህ ይለናል፦

9፥29 “እነዚያን በአላህና በመጨረሻዉ ቀን የማያምኑትን፣ አላህና መልክተኛዉ እርም ያደረጉትንም እርም የማያደርጉትን እና “ከ”እነዚያ መጽሐፍን ከተሰጡት ሰዎች እዉነተኛዉንም ሃይማኖት የማይቀበሉትን እነርሱ የተዋረዱ ሆነዉ ግብርን በእጆቻቸው እስከሚሰጡ ድረስ ተዋጉዋቸው”።

አህለ አዝ-ዚማህ ትሁት ሆነዉ ጂዝያን በእጆቻቸው እስከሚሰጡ ድረስ ሸሪዓው ያስገድዳቸዋል። የሚከፍሉት “ግብር” የሚለው ቃል “ጂዝያህ” جِزْيَةَ ሲሆን አህለ አዝ-ዚማህ በሙሥሊም ሸሪዓ ህሕ-መንግሥት የሚከፍሉት ግብር ነው። ምዕመናን የሚከፍሉት ዘካና ሰደቃ ሲሆን አህለ አዝ-ዚማህ ደግሞ  ጂዚያህ ነው፤ የበለጠ የግብር ወጪ ያለው ምእመናን ላይ ነው። ነገር ግን የትም አገር ያለ ሰው ሕዝባዊ አገልግሎት ለማግኘት ግብር እንደሚከፍል ሁሉ ምእመናን ዘካ እና ሰደቃ እንዲሁ አህለ አዝ-ዚማህ ደግሞ ጂዚያህ  ይከፍላሉ፤ አላህ የሚለው እስኪሠልሙ ድረስ ተዋጉአቸው” ሳይሆን “ግብርን እስከሚሰጡ ድረስ ተዋጉዋቸው” ነው፤ ይህን ግብር መክፈል ፈርድ ነው፤ ይህን ፈርድ ያልከፈለ ቅጣት አለው። ምነው ምዕራባውያን ሰውን በነፃ ነው እንዴ የሚያኖሩት? ምነው ከደሞዛችን ላይ 27-31% ይጎመዱ የለ እንዴ?

ቁርኣን በሰላም የሚኖሩ ክርስቲያኖችና አይሁድን እንዲዋጉና እንዲያሰልሙ ለሙስሊሞች ትዕዛዝን ሰጥቷቸዋል፡፡ ሱራ 9፡29 ሙስሊሞች የወረራ ጦርነቶችን እንዲያደርጉ ከሚያበረታቱ ጥቅሶች መካከል አንዱ ነው፡፡ ይህንን ከአፍታ በኋላ በዝርዝር እንመለከታለን፡፡

ባይብሉስ ግብር ባለመክፈል አምፁ ይላልን? የባይብሉ ግብር ደግሞ ገንዘብ ብቻ ሳይሆን ሰውና እንስሳትም ጭምር ነው፦

ዘኍልቍ 31፥28 ከእነዚያም ከተዋጉት ወደ ሰልፍም ከወጡት ሰልፈኞች ዘንድ፥ ”ከሰዎችም ከበሬዎችም ከአህዮችም ከመንጎችም ከአምስት መቶ አንድ ለእግዚአብሔር ግብር አውጣ”።

ኢያሱ 16፥10 በጌዝርም የተቀመጡትን ከነዓናውያንን አላሳደዱአቸውም፥ እስከግብር ዛሬም ድረስ ከነዓናውያን በኤፍሬም መካከል ተቀምጠዋል፤ ”የጕልበት ግብርም ያስገብሩአቸው ነበር”።

ኢያሱ 17፥13 የእስራኤልም ልጆች በጸኑ ጊዜ ከነዓናውያንን ”የጕልበት አስገበሩአቸው”፥ ፈጽመውም አላሳደዱአቸውም።

አዲስ ኪዳን ላይም፦ “ግብር ለሚገባው ግብርን ስጡ” ይላል፦

ሮሜ 13፥7 ለሁሉ የሚገባውን አስረክቡ፤ ”ግብር ለሚገባው ግብርን፥ ቀረጥ ለሚገባው ቀረጥን፥ መፈራት ለሚገባው መፈራትን፥ ክብር ለሚገባው ክብርን ስጡ”።

ጂዝያ እንደ ሌሎች ግብሮች ሳይሆን በመጽሐፉ ሰዎች ላይ የተጫነ አዋራጅ የግፍ ቀንበር ነው፡፡ ከአፍታ በኋላ በዝርዝር እንመለከታለን፡፡

በኢሥላም ሸሪዓ ህገ-መንግሥት ያሉ አህለ አዝ-ዚማህ ቢሠልሙም በእርግጥ ተመሩ እምቢ ቢሉም በሙሥሊም ላይ ያለበት ሃላፍትና የኢሥላምን መልእክት ማድረስ ብቻ ነዉ። በኢሥላም ቅድሚያ ተውሒድ ነው፥ ቀጥሎ አል-ወላእ ወል በራእ ነው፥ ቀጥሎ ደግሞ ጂሃድ ነው። ኢሥላም ወሰን በማለፍ አይረዳዳም፤ በግድ እመኑ ብሎም አያስገድድም፤ ምክንያቱም በሃይማኖት ማስገደድ የለም፤ የፈለገ ያምናል፥ ያልፈለገ ይክዳል፥ በኃላ የትንሳኤ ቀን የሚተሳሰበው አላህ ነው፦

2፥256 በሃይማኖት ማስገደድ የለም፡፡ ቅኑ መንገድ ከጠማማው በእርግጥ ተገለጠ፡፡

18፥29 «እውነቱም ከጌታችሁ ነው፡፡ የሻም ሰው ይመን፤ የሻም ሰው ይካድ» በላቸው፡፡

በሸሪዓህ ማስገደድ እና በእምነት ማስገደድ ሁለት ለየቅል እሳቦት ናቸው፦

10፥99 ጌታህም በሻ ኖሮ በምድር ያሉት ሰዎች ሁሉም የተሰበሰቡ ሆነው ባመኑ ነበር፡፡ ታዲያ አንተ ሰዎችን አማኞች እንዲኾኑ ታስገድዳለህን?

11፥28 «ሕዝቦቼ ሆይ! ንገሩኝ ከጌታዬ በግልጽ ማስረጃ ላይ ብሆን ከእርሱም ዘንድ የሆነን ችሮታ ነብይነት ቢሰጠኝ እና በእናንተ ላይ ብትደበቅባችሁ እናንተ ለእርሷ ጠይዎች ስትሆኑ እርሷን በመቀበል እናስገድዳችኋለን?» አላቸው፡፡

እነዚህ ጥቅሶች ቁርኣንን የማያነበውንና የእስልምናን ታሪክና አስተምህሮ በወጉ የማያውቀውን ህዝብ ለማደናገር ከማገልገል ባለፈ ፋይዳ የላቸውም፡፡ የቁርኣን ሐታቾች እንደሚናገሩት በመካና መዲና ቀደምት ዘመናት የተነገሩት የሰላም ጥቅሶች በኋለኛው ዘመን በመዲና በወረዱት የሰይፍ ጥቅሶች ተሽረዋል፡፡ ለምሳሌ ያህል ኢብን ከሢር ሱራ 2፡256 ላይ ሲያትት የጥቅሱን ትክክለኛ ትርጉም፤ ማለትም ሰዎች እምነታቸውን እንዲቀይሩ ማስገደድ አስፈላጊ አለመሆኑን እንደሚናገር ካብራራ በኋላ እንዲህ ይላል፡-

“… ነገር ግን ይህ ጥቅስ በውጊያ ጥቅሶች ተሽሯል ስለዚህ ሁሉም የዓለም ህዝቦች ወደ እስልምና እንዲመጡ ጥሪ ሊደረግላቸው ይገባል፡፡ ማናቸውም ሰዎች ያንን ለማድረግ ፍቃደኛ የማይሆኑ ከሆነ ወይም ጂዝያን ለመክፈል እምቢ የሚሉ ከሆነ እስኪገደሉ ድረስ ውጊያ ሊደረግባቸው ይገባል…” (Tafsir of Ibn Kathir, Al-Firdous Ltd., London, 1999: First Edition, Part 3, pp. 37-38)፡፡

ቁርኣን የሰዎችን ሃይማኖት በኃይል ማስለወጥ እንደሚያስፈልግ እንዲህ ሲል ይናገራል፡-

“ሁከትም እስከማትገኝ ሃይማኖትም ሁሉ ለአላህ ብቻ እስከሚኾን ድረስ ተጋደሏቸው፡፡ ቢከለከሉም አላህ የሚሠሩትን ሁሉ ተመልካች ነው፡፡” (የጦር ዘረፋዎች ምዕራፍ 8፡39)

በእስላማዊ ትውፊቶች ውስጥ የሚከተለው ዘገባ ሰፍሮ እናገኛለን፡

“ኢብን ዑመር እንዳስተላለፈው የአላህ መልእክተኛ እንዲህ ብለዋል፤ ሰዎች ከአላህ በስተቀር ሊመለክ የሚገባው እንደሌለና ሙሐመድም ደግሞ መልእክተኛው መሆኑን እስኪመሰክሩ ድረስ እንዲሁም ሶላትን ደንቡን ጠብቀው እስኪሰግዱ ድረስና ዘካትን እስኪሰጡ ድረስ እንድዋጋቸው (በአላህ) ታዝዣለሁ፡፡ ይህንን የሚያደርጉ ከሆነ በእስልምና ሕግ ከተደነገገው በስተቀር ሕይወታቸውንና ንብረታቸውን ከእኔ ይታደጋሉ፤ ድርሻቸውም በአላህ ይታሰብላቸዋል፡፡” (Sahih Al-Bukhari; Vol. 1 Book 2, Number 24)

“ነቢዩ ‹ማንኛውንም እስልምናን ለቆ የሚወጣ ሰው ግደሉት› ብለዋል፡፡” (Sahih al-Bukhari, 52:260; 83:37; 84:57; 89:271; 84:58; Abu Dawud, 4346)

ሙሐመድና የእስላም ሊቃውንት እንዲህ የሚሉ ከሆነ አንተ ተቂያ እየፈፀምክ ነው ማለት ነው፡፡ እስላማዊ ምንጮች “በሃይማኖት ማስገደድ ደለም” የሚለውን ቃል በማፍረስ “በኃይል አስልሙ፤ ከሃይማኖቱ የሚወጡትን ግደሉ” ይላሉ፡፡ አንተ ግን “ኧረ በጭራሽ እንዲህ ያለ ነገር የለም” ብለህ ትዋሻለህ፡፡

በተረፈ ያለ ምንም በደል አህለ አዝ-ዚማህ የገደለ የጀነትን ሽታ እንኳ እንደማያሸት ነቢያችን በሐዲሳቸው ተናግረዋል፦

ኢማም ቡኻርይ መጽሐፍ 87, ሐዲስ 52,

ዐብደላህ ኢብኑ ዐምር እንደተረከው፦ “ነቢዩ እንዲህ አሉ፦ “የሙዓሀዳን ነፍስ የገደለ የጀነትን ሽታ እንኳ አያሸትም፤ የእርሷ ሽታ የአርባ ዓመታት የጉዞ ርቀት ላይ ይገኛል”።

“ሙዓሀዳ” مُعَاهَدًا በኢሥላም ሸሪዓ -መንግሥት ያሉ አህለ አዝ-ዚማህ ናቸው።

ሙሐመድ ዚሚዎች እንዳይገደሉ አጥብቆ መከልከሉ እውነት ቢሆንም ምክንያቱን ሲገልፅ ግን የሙስሊሞች የገቢ ምንጭ ስለሆኑ እንደሆነ ነው የተናገረው፡፡ (Sahih al-Bukhari, The Book of al-Jizya the Stoppage of War. Vol. 4, Book 58, No. 3166)፡፡ ይህ የሙሐመድን ፍትሃዊነት የሚያሳይ አይደለም፡፡

ክርስቲያኖችና አይሁድ በሙስሊም ማሕበረሰብ ውስጥ ሁለተኛ ዜጎች ናቸው፤ ብዙ ግፍና በደልም ይፈፀምባቸዋል፡፡ የጂዝያ ክፍያም ክርስቲያኖችን ለማዋረድ የታለመ ዝርፊያ እንጂ ፍትሃዊ የሆነ ግብር አይደለም፡፡ የዚሚ ማሕበረሰቦች ከጂዝያ በተጨማሪ የሚከፍሏቸው ብዙ የግብር ዓይነቶች ነበሩ፡፡ ሙስሊሞች ለንግድ ወይም ለመጓጓዣ የሚከፍሏቸው ሌሎች ቀረጦች በሙሉ ዚሚዎች በእጥፍ እንዲከፍሉ ይደረጋል፡፡ በጦርነት ምክንያት የሚወጡትን ወጪዎች ለማካካስ ሙስሊም ገዢዎች የዚሚ ማሕበረሰቦች የሚበዘበዙባቸውን ስልቶች ይነድፉ ነበር፡፡ ሙስሊም ሽፍቶችና አማፅያን ደግሞ ግለሰቦችን አፍኖ በመውሰድ ወጆ (የማስለቀቂያ ክፍያ) እንዲከፈል ያስገድዱ ነበር፡፡ ብዝበዛውን መቋቋም ካለመቻላቸው የተነሳ ብዙ ክርስቲያኖች ልጆቻቸውን ለባርነት እስከመሸጥ ደርሰዋል፡፡ (Bat Ye’or. Islam and Dhimmitude: Where Civilization Collide; 2002, p. 71)፡፡ ኢብን ከሢር በመጽሐፉ ውስጥ እንዲህ በማለት አስፍሯል፡-

“አላህ በቁርአኑ ‹የተዋረዱ ሆነው ጂዝያን እስኪከፍሉ ድረስ ተጋደሏቸው› ብሏል፡፡ ሙስሊሞች የዚማን ሕዝቦች ማክበር ወይንም ከሙስሊሞች በላይ ከፍ ማድረግ አልተፈቀደላቸውም፤ ምክንያቱም እነርሱ ዕድለ ቢሶች፣ ቆሌያቸው የተገፈፈና ወራዶች ናቸውና፡፡ ሙስሊም የተሰኘው ዘጋቢ ከአቡ ሁራይራ ሰምቶ እንዳስተላለፈው ነቢዩ እንዲህ ብለዋል፡- ‹አይሁድን ወይንም ክርስቲያኖችን ሰላም አትበሏቸው፤ ማናቸውንም በመንገድ ላይ ብታገኙ ወደ ጠባቡ የመንገዱ ጠርዝ ግፏቸው፡፡› ለዚህ ነው የታማኞች መሪ የነበረው ኡመር አል ከታብ (አላህ ይውደደውና) ሁላችንም የምናውቃቸውን ቅድመ ሁኔታዎቹን ክርስቲያኖች እንዲቀበሉ የጠየቀው፡፡ እነዚህም ቅድመ ሁኔታዎች ውርደታቸው፣ ቅለታቸውና እፍረታቸው ቀጣይነቱ እንዲረጋገጥ ለማድረግ የታለሙ ናቸው፡፡” (Tafsir Ibn Kathir, vol. 4:406-7; Quoted in፡- Durie. The Third Choic; p. 142)

ፕሮፌሰር ባት ዬኦርና ዶ/ር ማርክ ዱሪ የተሰኙ ሁለት ሊቃውን ስለ ዚማ ሕግጋትና ስለ ጂዝያ ክፍያ እስላማዊ ምንጮችንና የታሪክ መዛግብትን በጥልቀት በማጥናት ባለ ብዙ ገፅ ጥራዞችን አሳትመዋል፡፡ ተከታዮቹ ነጥቦች ከእነርሱ መጻሕፍት የተወሰዱ ናቸው፡፡ (Mark Durie. The Third Choice: Islam, Dhimmitude and Freedom; pp. 131-153. Bat Ye’or. Islam and Dhimmitue: Where Civilization Collide; 2002, pp. 50-110. በተጨማሪም በባት ዬኦር የተመሠረተውን www.dhimmitude.net በመጎብኘት መረጃዎችን ማግኘት ይቻላል፡፡)

የጂዝያ አከፋፈል ሥርዓት

  • ግብር በሚከፈልበት ቀን በቆሻሻ በተሞላ ዝቅተኛ ቦታ እንዲቆሙ ይደረጋል፡፡
  • ዚሚው የመጓጓዣ እንስሳትን በመጠቀም ሳይሆን በእግሩ እየሄደ ወደ ቦታው መምጣት አለበት – አንዳንድ ምንጮች በእጁና በጉልበቱ እየዳኸ መምጣት እንዳለበት ይናገራሉ፡፡
  • ተቀባዩ በመቀመጥ እርሱ ግን በመቆም ክፍያውን መፈፀም ይኖርበታል፤ – ተቀባዩ ከእርሱ በላይ ከፍ ብሎ ይቀመጣል፡፡
  • ዚሚው ወዲያና ወዲህ ክፉኛ ይገፈታተራል፤ እንዲፈራና እንዲርበተበትም ይደረጋል፤ ይዋረዳል፡፡
  • ግብር ተቀባዩ በእጁ ላይ ጅራፍ ይይዛል፡፡
  • ዚሚው ለምን እዛ እንደተገኘ የሚያውቅ ቢሆንም እንዲከፍል ቀጭን ትዕዛዝ ይሰጠዋል፡፡
  • ድብደባ ይፈፀምበታል፡፡
  • ሊገደል እየተወሰደ እንዳለ ምርኮኛ ልብሱን በመያዝ ወይም አንገቱ ላይ ገመድ ታስሮ በመጎተት ጎሮሮው ታንቆ ወደ ፊት እንዲደፋ ይደረጋል፡፡
  • ልክ እንደሚሰየፍ ሰው ወይም እንደሚታረድ ሰው ማጅራቱ ላይ ወይም ደግሞ ጎሮሮው ላይ ይመታል (በሰይፍ የእርድ ምልክት ይደረጋል)፡፡
  • ፀጉሩን ከግንባሩ አካባቢ እንዲቆርጥ ይታዘዛል፡፡ ይህም የሚደረገው አንገቱን ከመቆረጥ መትረፉን እንዲያስታውስ ነው፡፡
  • ሌላው አንገትን የመቆረጥ ምልክት የብረት ማነቆ በአንገት ላይ ማጥለቅ ነው፡፡
  • እንደሚሰየፍ ሰው ጢሙ ተይዞ ይጎተታል፡፡
  • ራሱ ላይ ቆሻሻ ይጣልበታል፡፡
  • ሙስሊሙ ሰው የዚሚው አንገት ላይ ይቆማል፡፡
  • ክፍያውን ከፈፀመ በኋላ ከሰይፍ ማምለጡን ለማመልከት ወደ ጎን ተገፍትሮ እንዲያልፍ ይደረጋል፡፡
  • የከፈሉበትን ደረሰኝ ይዘው የማይንቀሳቀሱ ወይም የጣሉ ዚሚዎች ሕይወታቸውን ለከፍተኛ አደጋ ያጋልጣሉ፡፡

የዚሚ ግዴታዎች

  • በእስልምና ስር ባለ ግዛት ውስጥ ወደ ክርስትና ወይም ወደ ይሁዲ የሚቀየር ሙስሊም ይገደላል፡፡ ሰዎች እምነታቸውን ይዘው እንዲቆዩ ተፈቅዷል ነገር ግን ወደ እስልምና ካልሆነ በስተቀር ወደ ሌላ እምነት መቀየር ክልክል ነው፡፡
  • አንድን ሙስሊም እምነቱን እንዲቀይር ለማድረግ መሞከር በሞት ሊያስቀጣ የሚችልና የተከለከለ ተግባር ነው፡፡
  • አንድ ዚሚ እስልምናን እንዳይቀበል እንቅፋት መሆን የተከለከለ ነው፡፡
  • አንድ ሙስሊም ወንድ ክርስቲያን ወይም አይሁዳዊት ሴት ማግባት ይችላል ነገር ግን ልጆቻቸው በሸሪኣ ሕግ መሠረት ሙስሊሞች ናቸው፡፡ ያ ቤተሰብ የሙስሊም ቤተሰብ ነው፡፡ ዚሚ ከሙስሊም ሴት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት ሊኖረው አይችልም፡፡ ይህንን ተግባር መፈፀም እስከ ሞት የሚደርስ ቅጣት ያስከትላል፡፡
  • ወደ እስልምና የሚቀየር ማንኛውም ሰው በቤተሰቡ ውስጥ ልዩ የውርስ መብት ይኖረዋል – የሚሰልም ወይም የምትሰልም የትዳር አጋር በፍቺ ወቅት ልጆችን የማሳደግ ልዩ መብት ታገኛለች ወይም ያገኛል፡፡
  • ከወረራ በኋላ አዲስ አብያተ ክርስቲያናትን መገንባት የተከለከለ ነው፡፡ ያረጁትንም ማደስ የተከለከለ ነው፡፡
  • ቅዱሳት መጻሕፍቶቻቸውን በማባዛት ማሰራጨት የተከለከለ ነው፡፡
  • የዚሚ ቤቶች ከሙስሊም ቤቶች ያነሱና ዝቅ ያሉ መሆን አለባቸው፡፡ ሲወጡና ሲገቡ እንዲያጎነብሱ የቤታቸው በር ጠባብና አጭር መሆን አለበት፡፡ በጥንቷ እስፔን ውስጥ የሚገኙ አይሁድ ይኖሩባቸው የነበሩ አጫጭር ቤቶች እስከ ዛሬ ድረስ ይታያሉ፡፡
  • ዚሚዎች በተለየ ሁኔታ መልበስና ከሙስሊሞች ያነሱ አልባሳትን መጠቀም ይኖርባቸዋል፡፡ [1]
  • እስላማዊ ስሞችን መጠቀም ክልክል ነው፡፡ ይህም በቀላሉ ተጋላጭ እንዲሆኑ የታለመ ነው፡፡
  • ዚሚ የሚቀመጥበትን ቦታና የሚሄድበትን መንገድ ለሙስሊም ሰው የመልቀቅ ግዴታ አለበት፡፡
  • ዚሚ የትህትና አቋቋም ሊኖረው ይገባል፡፡
  • ዚሚ በሙስሊም ሰው ላይ እጁን ማንሳት (መምታት) በሞት ወይንም አካልን በመቆረጥ የሚያስቀጣ በጥብቅ የተከለከለ ድርጊት ነው፡፡ በምንም ምክንያት አንድን ሙስሊም መምታት የተከለከለ ነው፡፡
  • ሙስሊሞችን መስደብ የተከለከለና በሞት የሚያስቀጣ ነው፡፡
  • ዚሚ መሳርያ ሊኖረው ወይንም ሊይዝ አይችልም፡፡ ክርስቲያኖችና አይሁድ ራሳቸውን የሚከላከሉበት ምንም መንገድ መኖር የለበትም ማለት ነው፡፡ (ዛሬ እንኳ በአንዳንድ የሙስሊም አገራት የሚኖሩ ክርስቲያኖች መሳርያ መያዝ ስለማይፈቀድላቸው የቤተ ክርስቲያን ዘበኞች ሙስሊሞች ናቸው፡፡)
  • የሙስሊም ሰው ደም ከዚሚ ሰው ደም ጋር እኩል አይደለም፡፡[2] ለምሳሌ ያህል አንድን ሙስሊም መግደል በሞት የሚያስቀጣ ቢሆንም የሸሪኣ ሕግ እንደሚናገረው ሙስሊም ያልሆነን ሰው በመግደሉ ምክንያት ማንም ሙስሊም በሞት መቀጣት የለበትም፡፡
  • ዚሚ ሌላውን ዚሚ ከገደለ በኋላ ቢሰልም ከቅጣት ሊያመልጥ ይችላል፤ ወደ እስልምና የሚቀየር ማንኛውም ሰው ከሚጠብቀው የሞት ቅጣት ያመልጣል፡፡
  • ክርስቲያኖችና አይሁድ ሕዝባዊ ሥልጣን ሊኖራቸው አይችልም፤ ወይንም በሥልጣን ከሙስሊሞች በላይ እንዲሆኑ አይፈቀድላቸውም፡፡
  • ሙስሊም ባርያ ሊኖራቸው አይችልም ወይም ከሙስሊም ባርያን መግዛት አይችሉም፡፡
  • በእስላማዊ ሸሪኣ ፍርድ ቤት ዚሚ በሙስሊም ላይ የሚሰጠው ምስክርነት ተቀባይነት የለውም፡፡
  • አንድ ሙስሊም ከፍተኛ ቅጣት በሚያስከትል ክስ አንድን ክርስቲያን ቢከስ የክርስቲያኑ ምስክርነት ራሱን ለመከላከል የሚበቃና ተቀባይነት ያለው አይደለም፡፡ አንድ ሙስሊም ወንድ ክርስቲያን ሴት ቢደፍር ቃሏ ተቀባይነት አይኖረውም፡፡
  • ዚሚዎች ሙስሊም ወታደሮችን የማስጠለልና የመመገብ ግዴታ አለባቸው፡፡ በስምምነቱ መሠረት ጂሃድን ሊደግፉ ይገባል፡፡
  • ዚሚዎች ከሙስሊም ጠላቶች ጋር መወዳጀት፣ እነርሱን መርዳትም ሆነ ከእነርሱ እርዳታን መቀበል የተከለከለ ነው፡፡
  • ዚሚዎች በእስልምና ቁጥጥር ስር ካለ አካባቢ ለቆ መሄድ የተከለከለ ነው፡፡
  • ዚሚዎች በአደባባይ እምነታቸውን በምንም ዓይነት መንገድ እንዲያንፀባርቁ አይፈቀድም፡፡ መስቀል ማሳየት አይችሉም፡፡ በሃይማኖታቸው መሠረት የቀብር ስርኣት መፈፀም አይችሉም፡፡ ደወል ሊኖራቸው አይችልም፡፡ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው መዘመርም ሆነ ማስተማር አይችሉም፡፡[3]
  • ዚሚዎች ልጆቻቸውን ስለ እስልምና ከማስተማር ተከልክለዋል፡፡ በሥርኣቱ ስር ተጨቁኖ መሠቃየት እንጂ የሥርኣቱን ምንነት ማወቅ የተከለከለ ነው፡፡
  • እስልምናን፣ ሙሐመድንና የዚማን ሥርኣት መተቸት በጥብቅ የተከለከለ ነው፡፡
  • ዚሚዎች ፈረስ እንዳይቀመጡ ተከልክለዋል ምክንያቱም በደረጃ ከሙስሊሞች በላይ ከፍ ያደርጋቸዋልና፡፡
  • አህያ እንዲቀመጡ የሚፈቀድላቸው ሲሆን እግራቸውን በማንፈራጠጥ እንስሳው ላይ መቀመጥ አይችሉም፡፡ ሁለቱም እግሮቻቸው ወደ አንድ አቅጣጫ ዞረው በጎን መቀመጥ ይኖርባቸዋል፡፡
  • በብዙ ቦታዎች ዚሚዎች ከሌላው እንዲለዩ በልብሳቸው ላይ የተለየ የቀለም ምልክት እንዲኖራቸው ይጠበቅባቸው ነበር፡፡
  • በብዙ ቦታዎች አንድ ዓይነት ጫማ እንዲጫሙ አይፈቀድላቸውም ነበር፡፡
  • በሕዝባዊ መታጠብያ ቦታዎች ከሙስሊም ተለይተው እንዲታወቁ የአንገት ማነቆዎችን ወይም ቃጭሎችን እንዲያጠልቁ ይገደዱ ነበር፡፡
  • በተለያዩ አካባቢዎች የዚሚን ማሕበረሰቦች የሚያዋርዱ የተለያዩ ተግባራት ጥቅም ላይ ይውሉ ነበር፡፡ ለምሳሌ ያህል የሞሮኮ አይሁድ የቆሻሻ መጣያዎችን እንዲያፀዱ፣ የሞቱ እንስሳትን እንዲያነሱና የሞት ፍርድ በተፈፀመባቸው ወንጀለኞች ጭንቅላት ላይ ጨው እንዲነሰንሱ ይገደዱ ነበር፡፡
  • ሙስሊም ያልሆኑ ሰዎች ርኩሶች እንደሆኑ ከሚናገረው የቁርኣን ቃል በመነሳት (9፡28) በ19ው ክፍለ ዘመን በሐመዳን (ኢራን አገር) ይኖሩ የነበሩ አይሁድ በበረዶና በዝናባማ ቀን ከቤት እንዳይወጡ ይከለከሉ ነበር፡፡ ይህም የተደረገበት ምክንያት ሰውነታቸውን የነካ እርጥበት ኋላ ላይ የሙስሊሞችን እግር በመንካት እንዳያረክሳቸው በሚል ነበር፡፡

በብዙ ንፁሃን ክርስቲያኖች ደም ለሰከረው ለዚህ የግፍ መንገድ ተከራካሪ ሆነህ በእግዚአብሔር ፍርድ ስር ከምትወድቅና ወደ ዘላለም እሳት ከምትጣል ዛሬ ቀን ሳለ ወደ ክርስቶስ ተመለስ!

የቁርኣን ግጭቶች