የቁርኣን ግጭቶች – የዒሳ “አፈጣጠር” እንደ አደም ከአፈር ወይንስ በልደት?

36. የዒሳ “አፈጣጠር” እንደ አደም ከአፈር ወይንስ በልደት?

ማሳሰብያ፡- በሰማያዊ የተጻፈው የኛ ሲሆን በጥቁር የተጻፈው የእርሱ ነው፡፡

እንደ አደም፡-

3፡59 “አላህ ዘንድ የዒሳ ምሳሌ፥ እንደ አደም ብጤ ነዉ፤ ከዐፈር ፈጠረዉ፤ ከዚያም ለርሱ (ሰዉ) ሁን አለዉ፥ ሆነም።”

በልደት፡-

19፡22-23 “ወዲያዉኑም አረገዘችዉ፤ በርሱም በሆድዋ ይዛዉ ወደ ሩቅ ስፍራ ገለል አለች። ምጡም ወደ ዘንባባይቱ ግንድ አስጠጋት…”

መልስ

ሰው የተፈጠረው ከምድር ነው፤ “ምድር” የሚለው ቃል ተክቶ የመጣ “ሃ” ْهَا ማለትም “እርሷ” የሚል ተውላጠ-ስም አለ፤ “ሃ” በሚለው ቃል ላይ “ሚን” مِنْ ማለትም “ከ” የሚል መስተዋድድ መነሻ ቅጥያ አለ፦

ማንበብ ለሚችል ሁሉ ግልፅ የሆነ ግራመር መተንተን ምሑር አያሰኝም፤ ብስለት የማጣት ምልክት ነው፡፡

20፥ 55 ከእርሷ ከምድር ፈጠርናችሁ፡፡ በእርሷም ውስጥ እንመልሳችኋለን፡፡ ከእርሷም በሌላ ጊዜ እናወጣችኋለን፡፡

ይህ የሚያሳየው ሰው የተፈጠረው ከምድር ነው፤ ምድር ለአካል መሰራት ግኡዝ ንጥረ-ነገር ነው፤ አላህ ምድርን ወደ እራሱ በማስጠጋት እልቅና ክብር ለመስጠት “አርዲ” أَرْضِي ማለትም “ምድሬ” በማለት በአገናዛቢ ተውላጠ-ስም ይናገራል፦

29፥56 እናንተ ያመናችሁ ባሮቼ ሆይ! ምድሬ በእርግጥ ሰፊ ናት፤ ብትቸገሩ ተሰደዱ፡፡ እኔንም ብቻ አምልኩኝ፡፡

ይህንን ከምድር የተፈጠረውን ሰው አላህ በሩሕ ሕያው ያደርገዋል፤ “ሩሕ” رُوح ማለትም “መንፈስ” አላህ ግኡዛን ነገሮችን ህያው የሚያደርግበት ንጥረ-ነገር ነው። አላህ ከምድር በተፈጠረው አካል ከመንፈሱ ሲነፋበት ያ ግኡዝ አካል ሕያው ሆነ፦

38፥72 ፍጥረቱንም ባስተካከልኩ እና ከመንፈሴ በነፋሁበት ጊዜ ለእርሱ ሰጋጆች ኾናችሁ ውደቁ»

እዚህ አንቀጽ ላይ “ሩሕ” رُوح በሚለው ቃል ላይ “ሚን” مِنْ ማለትም “ከ” የሚል መነሻ ቅጥያ አለ፤ ይህ የሚያሳየው “ሩሕ” አካል ህያው የሚሆንበት ንጥረ-ነገር መሆኑን ነው፤ “ከ”ምድር “ከ”መንፈስ የሚለው ቃላት ይሰመርበት። አላህ ምድርን ወደ እራሱ በማስጠጋት እልቅና ክብር ለመስጠት “አርዲ” أَرْضِي ማለትም “ምድሬ” በማለት እንደተናገረ ሁሉ በተመሳሳይም ሩሕን ወደ እራሱ በማስጠጋት እልቅና ክብር ለመስጠት “ሩሒ” رُّوحِى ማለትም “መንፈሴ” በማለት በአገናዛቢ ተውላጠ-ስም” ተናግሯል። ምድርም መንፈስም የሰው ምንነት ነው፡፡

የአዳምን አፈጣጠር በሚናገሩት ከላይ በሚገኙት ጥቅሶች መካከል ግልፅ ግጭት አለ፡፡ በሱራ 3፡59 መሠረት አዳም ከአፈር በአላህ የይሁን ቃል ተፈጥሯል፡፡ ነገር ግን ቁርኣን በሌላ ቦታ ላይ እንዲህ ይላል፡-

“ጌታህ «ለመላእክት እኔ ሰውን ከጭቃ ፈጣሪ ነኝ ባለ ጊዜ» (አስታውስ)፡፡ ‹ፍጥረቱንም ባስተካከልኩና ከመንፈሴ በነፋሁበት ጊዜ ለእርሱ ሰጋጆች ኾናችሁ ውደቁ› (አልኩ)፡፡ መላእክትም መላውም ባንድነት ሰገዱ፡፡ ኢብሊስ ብቻ ሲቀር፡፡ ኮራ፤ ከከሓዲዎቹም ነበር፡፡ (አላህም) «ኢብሊስ ሆይ! በሁለት እጆቼ (በኃይሌ) ለፈጠርኩት ከመስገድ ምን ከለከለህ? (አሁን) ኮራህን? ወይስ (ፊቱኑ) ከትዕቢተኞቹ ነበርክ?» አለው፡፡” (ሱራ 38፡71-72)

በዚህ ጥቅስ መሠረት አላህ አዳምን ከጭቃ ከፈጠረው በኋላ “መንፈሱን” በመንፋት ሕያው አድርጎታል፡፡ በቀደመው ጥቅስ መሠረት ግን ከፈጠረው በኋላ “ኹን” በሚል ቃል ሕያው አድርጎታል፡፡ በቃሉ ሕያው ካደረገው መንፈሱን መንፋት ለምን አስፈለገ? በመንፈሱ ሕያው ካደረገው “ሁን” የሚለውን ቃል መናገር ለምን አስፈለገ?

አላህ ልክ አደምን ከዐፈር ሰርቶ ከመንፈሱ አካሉ ላይ ሲነፋበት ሰው እንደሆነ ሁሉ መርየም ውስጥ ያለውን አካል ከመንፈሱ ሲነፋበት ዒሣ ሰው ሆነ፦

21፥91 ያችንም ብልቷን የጠበቀቺውን ”በእርሷም ውስጥ ከመንፈሳችን የነፋንባትን” እርሷንም ልጅዋንም ለዓለማት ተዓምር ያደረግናትን መርየምን አስታውስ፡፡

ዐደም እና ዒሣ አፈጣጠራቸው የሚያመሳስላቸው ለዚህ ነው፦

3፥59 ”አላህ ዘንድ የዒሳ ምሳሌ እንደ አዳም ብጤ ነው፡፡ ከዐፈር ፈጠረው፡፡ ከዚያም ለእርሱ «ኹን» አለው፤ ኾነም”፡፡

ኸለቀ” خَلَقَ ማለትም “ፈጠረ” በሚለው ግስ መዳረሻ ቅጥያ ላይ “ሁ” هُۥ ማለት “እርሱ” የሚል ተሳቢ ተውላጠ-ስም አለ፥ ይህም የስም ምትክ “ኣደም” ءَادَم የሚለውን የተጻውዖ ስም ተክቶ የመጣ ነው። “ከአፈር” ፈጠረው የሚለው አደምን እንጂ በፍጹም ዒሣን አይደለም። ይህንን ለመረዳት አንድ የሰዋስው ሙግት እናቅርብ፦

2፥45 ”በመታገስ እና በሶላትም ተረዱ፡፡ እርሷም በፈሪዎች ላይ እንጅ በሌላው ላይ በእርግጥ ከባድ ናት፡፡

ሃ” َّهَا ማለትም “እርሷ” የሚለው ተውላጠ-ስም ተክቶ የመጣው ምንን ነው? “መታገስ” የሚለው ቃል ወይስ “ሶላት” የሚለው ቃል? ስልን፤ መልሱ የቅርብ ቃል “ሶላት” ስለሆነ “እርሷ” የሚለው ተክቶ የመጣው “ሶላት” የሚለውን ቃል ነው። በተመሳሳይ የቅርብ ቃል “አደም” ስለሆነ “እርሱ” የሚለው ተክቶ የመጣው “አደም” የሚለውን ቃል ነው።

ይህ ማብራርያ በሙግታችን ላይ የሚያመጣው ለውጥ ባይኖርም “እርሱ” የተባለው አዳም ስለመሆኑ ያቀረብከው ምሳሌ አጥጋቢ አይደለም፡፡ ሱራ 2፡45 ላይ “መታገስ እና ሶላት” በዓረፍተ ነገሩ ውስጥ እኩል ድርሻ እንዳላቸው ግልፅ ነው፡፡ ስለዚህ ለተውላጠ ስሙ ቅርብ የሆነውን ቃል በመመልከት “እርሷ” የተባለችው ሶላት መሆኗን መገንዘብ እንችላለን፡፡ ነገር ግን ሱራ 3፡59 አወቃቀሩ ከዚህ ጋር አይመሳሰልም፡፡ በዓረፍተ ነገሩ ውስጥ የትኩረት ማዕከል ዒሳ እንጂ አዳም አይደለም፡፡ “አላህ ዘንድ የዒሳ ምሳሌ እንደ አዳም ብጤ ነው” ሲል ዋና  ማዕከሉ ዒሳ ነው፡፡ “የዒሳ ምሳሌ እንደ አዳም ብጤ ነው” ብሎ ስለ ዒሳ እያወራ ሳለ ቀጥሎ “ከዐፈር ፈጠረው፡፡ ከዚያም ለእርሱ «ኹን» አለው፤ ኾነም” ሲል ቀጥተኛው መረዳት ስለ ዒሳ እያወራ ነው የሚል ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል “የመርከብ ሞተር ልክ እንደ መኪና ሞተር ነው፡፡ በነዳጅ ነው የሚሠራው፡፡” ብዬ ብል እያወራሁ ያለሁት ስለ መርከብ በመሆኑ ቀጥሎ የመጣው ዓረፍተ ነገርም መርከብን የተመለከተ ነው፡፡ ሌላ ምሳሌ ልጨምር፡- “የግብፅ ሕዝብ ልክ እንደ ሞሮኮ ሕዝብ ነው፡፡ አረብኛ ይናገራል፡፡” ብዬ ብል የዓረፍተ ነገሩ ማዕከል የግብፅ ሕዝብ በመሆኑ ተፈጥሯዊ የሆነው መረዳት ሁለተኛው ዓረፍተ ነገርም ስለ ግብፅ ሕዝብ የሚናገር እንደሆነ ነው፡፡ ስለዚህ “…የዒሳ ምሳሌ እንደ አዳም ብጤ ነው፡፡ ከዐፈር ፈጠረው፡፡” ሲል ሁለተኛው ዓረፍተ ነገር ዒሳን የተመለከተ አይደለም ብሎ ማለት አሳማኝ አይደለም፡፡

አደም እና ዒሣ የተመሳሰሉበት ነጥብ የተፈጠሩበት ንጥረ-ነገር ሳይሆን የተፈጠሩበት ሁኔታ ነው፣ ሁለቱም በታምር ኹን በሚለው ቃል መፈጠራቸው ነው። አላህ ዐደምን ከዐፈር ፈጥሮ ኹን እንዳለው እንደሆነ ሁሉ ዒሣን ከመርየም ኹን በማለት ፈጥሮታል፦

3፥47 ፡-ጌታዬ ሆይ! ሰው ያልነካኝ ስኾን ለኔ እንዴት ልጅ ይኖረኛል? አለች፡፡ ነገሩ እንዳልሽው ነው፡፡ አላህ የሚሻውን ይፈጥራል፤ አንዳችን በሻ ጊዜ ለእርሱ ኹን ይለዋል፤ ወዲውኑም ይኾናል አላት፡፡

ጥያቄ የተነሳበትን ጥቅስ ደግመን እናንብበው፡- 3፡59 “አላህ ዘንድ የዒሳ ምሳሌ እንደ አዳም ብጤ ነው፡፡ ከዐፈር ፈጠረው፡፡ ከዚያም ለእርሱ «ኹን» አለው፤ ኾነም”፡፡ ሁለተኛው ዓረፍተ ነገር ወደ አዳም የሚጠቁም ነው የሚለውን ሙግት እስኪ ትክክል ነው ብለን እንቀበል፡፡ በዚህ መሠረት የቁርኣን ጸሐፊ የአዳምና የዒሳ አፈጣጠር እንደሚመሳሰል ከተናገረ በኋላ በቀጣይ ዓረፍተ ነገር የጠቀሰው አዳም ከአፈር መፈጠሩንና ‹‹ኹን›› በሚል የአላህ ትዕዛዝ ሕያው መሆኑን ነው፡፡ “ይመሳሰላሉ” ካለ በኋላ በምን እንደሚመሳሰሉ ሲገልፅ የአዳምን ከአፈር መፈጠርና ‹‹ኹን›› በሚል ትዕዛዝ ሕያው መሆን ጠቀሰ፡፡ ስለዚህ ዒሳም ልክ እንደ አዳም ከአፈር ተፈጥሮ ‹‹ኹን›› በሚል ቃል ሕያው ሆኗል ማለት ነው፡፡

ይህ ጥቅስ በርግጥ በአፈጣጠር ብቻ የተገደበ አይደለም፡፡ “አላህ ዘንድ የዒሳ ምሳሌ እንደ አዳም ብጤ ነው” ሲል አፈጣጠርን ብቻ የተመለከተ ሳይሆን አጠቃላይ በሆነ መንገድ ዒሳና አዳም እንደሚመሳሰሉ የሚገልጽ ነው፡፡ በቀጣይ ዓረፍተ ነገር አፈጣጠር በምሳሌነት ቢነሳም ‹‹ምሳሌ›› አለ እንጂ ‹‹የአፈጣጠር ምሳሌ›› ስላላለ በአፈጣጠር ብቻ አልተገደበም፡፡ ስለዚህ ዒሳና አዳም ይመሳሰላሉ ወይ? የሚለውን ጥያቄ መመለስ አስፈላጊ ነው፡፡ በቁርኣን መሠረት ሁለቱ በፍፁም አይመሳሰሉም፡፡

  • ዒሳ ከድንግል ተወለደ፤ አዳም ግን አልተወለደም (ሱራ 3፡47፣ 19፡16-21)
  • ዒሳ ኃጢአት አልባ ነው፤ አዳም ግን አይደለም (ሱራ 19፡19፣ 3፡35፣ Sahih Al-Bukhari, Volume 4, Book 55, Number 641; see also Volume 4, Book 54, Number 506፣ ሱራ 20፡115-123፣ 7፡19-27)
  • ዒሳ የአላህ መንፈስና ቃሉ ነው፤ አዳም ግን በመንፈሱና በቃሉ የተፈጠረ ነው (ሱራ 3፡45፣ 4፡171)
  • ዒሳ ንጉሥ የሆነ መሲህ ነው፤ አዳም አይደለም (Tanwîr al-Miqbâs min Tafsîr Ibn ‘Abbâs; source ፣ ሱራ 3፡45)
  • ዒሳ በሚመጣው ዓለም የተከበረ ነው፤ ለአዳም ግን እንደርሱ አልተባለም (ሱራ 3፡45)
  • ዒሳ ወደ ሰማይ አርጓል፤ አዳም ግን ሞቷል (ሱራ 3፡55፣ 4፡158)
  • ዒሳ ተመልሶ በመምጣት ጀዳልን ይገድለዋል፤ አዳም እስከ ዕለተ ትንሣኤ ሞቶ ይቆያል Sahih Al-Bukhari, Vol. 4, Book 55, Number 657 ፣ ሱራ 43፡61)
  • ዒሳ ተዓምራትን አድርጓል፤ አዳም አላደረገም (ሱራ 3፡48-49፣ 5፡110)

ስለዚህ ቁርኣን ዒሳና አዳም ይመሳሰላሉ ማለቱ ስህተት ነው፡፡

ዒሳና አዳም እንደማይመሳሰሉ የበለጠ ለመረዳት Sam Shamoun: www.Answering-Islam.Org/quran/contra/jesus_unlike_adam.html ይጎብኙ፡፡

የቁርኣን ግጭቶች