የሱራ 9፡31 ሁለት መሠረታዊ ችግሮች – ኢየሱስ አምላክ ነው አይደለም?

የሱራ 931 ሁለት መሠረታዊ ችግሮች

ኢየሱስ አምላክ ነው አይደለም?


“ከርሱ በቀር ሌላ አምላክ የሌለዉን አንድን አምላክ ሊገዙ እንጂ ያልታዘዙ ሲሆኑ ሊቃውንቶቻቸውንና መነኮሳታቸዉን የመርየምን ልጅ አልመሲሕንም ከአላህ ሌላ አማልክት አድርገው ያዙ፤ ከሚያጋሩት ሁሉ የጠራ ነው።” (ሱረቱ አል-ተውባህ 9፡31)

የመጀመርያው የዚህ ጥቅስ ችግር እስላማዊ አስተምህሮን በመጻረር ኢየሱስ አምላክ መሆኑን መናገሩ ነው፡፡ የአማርኛና ብዙ የእንግሊዝኛ ትርጉሞች ከላይ በሚገኘው መንገድ “የመርየም ልጅ አልመሲሕ” የሚለውን “ሊቃውንቶቻቸውንና መነኮሳታቸዉን” ከሚለው ጋር በመደመር ቢተረጉሙትም የአረብኛው ጽሑፍ “አልመሲሕ” የሚለውን ከአላህ በኋላ በማምጣት “ወ” (እና) በሚል መስተጻምር ያያይዛቸዋል፡-

اتَّخَذُوا أَحْبَارَهُمْ وَرُهْبَانَهُمْ أَرْبَابًا مِنْ دُونِ اللَّهِ وَالْمَسِيحَ ابْنَ مَرْيَمَ

“አትተኸዙ አሕባረሁም ወ ሩህባነሁም አርባባን ሚን ዱኒ አላሂ ወ አል-መሲሐ ኢብነ መርየም …”

ቀጥተኛው ትርጉም “ከአላህና ከአልመሲሕ የመርየም ልጅ ሌላ ሊቃውንቶቻቸውንና መነኮሳታቸዉን ጌቶች አድርገው ያዙ…” የሚል ነው፡፡ ለዋናው የአረብኛ ንባብ ሃቀኛ መሆን የፈለጉ አንዳንድ የእንግሊዝኛ ትርጉሞች በዚህ ጉዳይ የተፈተኑ ይመስላሉ፡፡ በዚህም ምክንያት በአረብኛው ጥቅስ ውስጥ የማይታይ የኮማ ስርዓተ ነጥብ በመጠቀም ለማስተካከል ሞክረዋል፡-

They have taken their doctors of law and their monks for lords besides Allah, AND (also) the Messiah son of Marium… (Shakir)

They take their doctors and their monks for lords rather than God, AND the Messiah the son of Mary… (Palmer)

They take their priests and their monks for [their] lords, besides God, AND Christ the son of Mary… (Sale)

ይህ የቁርኣን ጥቅስ ክርስቲያኖች ከአላህ እና ከመሲሑ ውጪ ሌሎችን ማምለክ የማይገባቸው ሆነው ሳሉ ሊቃውንቶቻቸውንና መነኮሳታቸዉን ያመልካሉ በማለት ወቀሳ ያቀርባል፤ ስለዚህ በጥቅሱ መሠረት ኢየሱስ አምልኮ የተገባው አምላክ ነው፡፡

ሙስሊም ሰባኪያን ይህንን እውነታ ለማስተባበል “መሲሐ” የሚለው حَ በፈትሃ ስለተጻፈ የዓረፍተ ነገሩ ባለቤት ሳይሆን ተሳቢ በመሆኑ ከሊቃውንትና መነኮሳት ጋር መቆጠር አለበት ይላሉ፡፡ ነገር ግን ይህ አጻጻፍ በቀዳሚያን ማኑስክሪፕቶች ውስጥ ያልነበረ ሲሆን ከጊዜ በኋላ የተጨመረ ነው፡፡ ጥንታዊው የአረብኛ አጻጻፍ አናባቢ ነቁጦች (diacritical marks) ስላልነበረው ከጊዜ በኋላ የተጨመረ ምልክት በመጠቀም መሞገት አሳማኝ አይደለም፡፡ የቁርኣን ደራሲ ይህንን ችግር ለማስወገድ ቢፈልግ ኖሮ በቀዳሚያን ማኑስክሪፕቶች መሠረት ክርስቶስ አምላክ መሆኑን በሚያረጋግጥ መንገድ ሐሳቡን ከመግለፅ ይልቅ አላህና መሲሑን ነጣጥሎ “አልመሲሕ” የሚለውን ቃል “ሊቃውንቶቻቸውንና መነኮሳታቸዉን..” ከሚለው በፊት ወይም በኋላ ማስቀመጥ ይችል ነበር፤ ነገር ግን አላደረገውም፡፡

ሁለተኛው የዚህ ጥቅስ ችግር ክርስቲያኖች የሃይማኖት አባቶቻቸውን እንደሚያመልኩ በሐሰት መክሰሱ ነው፡፡ በሙሐመድ ዘመን የነበሩ ሰዎች ይህንን ችግር በመረዳት “ክርስቲያኖች ሊቃውንትና መነኮሳትን አያመልኩም እኮ” በማለት ሙሐመድን ለማረም እንደሞከሩ እስላማዊ ምንጮች ይናገራሉ፡፡ የሙሐመድ ምላሽ የነበረው “አይሁድና ክርስቲያኖች ረበናትና መነኮሳት የተፈቀደውን ሲከለክሏቸው ወይም የተከለከለውን ሲፈቅዱላቸው ይታዘዟቸዋል፤ ይህ አምልኮ ነው” የሚል ነበር፡፡ (Tafsir Ibn Kathir (Abridged), 2000, Volume 4, pp. 409-410)

የተፈቀደውን የሚከለክልና የተከለከለውን የሚፈቅድን ሰው መታዘዝ አምልኮ ከተባለ በቁርኣን መሠረት ዒሳ የተከለከለውን የመፍቀድ ሥልጣን እንዳለውና የእርሱን ትዕዛዛት መከተል አስፈላጊ መሆኑ ስለተነገረ በተዘዋዋሪ ቁርኣን ኢየሱስን ማምለክ ትክክል መሆኑን ያረጋግጣል ማለት ነው!

“ከተዉራትም ከኔ በፊት ያልለዉን ያረጋገጥሁ ስሆን የዚያንም በናንተ ላይ እርም የተደረገዉን ከፊል ለናንተ እፈቅድ ዘንድ፥ (መጣኋችሁ) ከጌታችሁም በሆነ ታምር መጣሁዋችሁ አላህንም ፍሩ፤ ታዘዙኝም።” (ሱረቱ አሊ-ዒምራን 3:50)

እንደ እስልምና አስተምህሮ ሁሉ ነገር የተምታታበት አስተምህሮ በምድር ላይ ይገኝ ይሆን?

መሲሁ ኢየሱስ