ኢየሱስ፣ እግዚአብሔር ወልድ

ኢየሱስ፣ እግዚአብሔር ወልድ

ኢየሱስ ማነው? ይህ በምድር ላይ የሚኖር ሁሉም ሰው ሊመልሰው የሚገባ ወሳኝ ጥያቄ ነው፡፡ እርሱ ታላቅ የሃይማኖት መምህር ነበርን? ወይንስ አእምሮውን የሳተ ሰው? አምላክ ነበር ወይንስ ሰው ብቻ? የእርሱን ማንነትና ሥልጣን በተመለከተ ትልቅ ክርክርና ጭቅጭቅ አለ፡፡ ብዙ ሰዎች ትህትናን የተሞላ ሥነ ምግባርን ያስተማረ ሥርኣት ላለው ማሕበረሰብ ምሳሌ ሊሆን የሚችል ሰው ብቻ አድርገው ያቀርቡታል፡፡ ነገር ግን ሕይቱንና ትምህርቱን በጥንቃቄ ካጠናን ይህ አማራጭ ውድቅ ይናል፡፡

ሲ ኤስ ሌዊስ የተሰኘው ዝነኛ የእንግሊዝ ጸሐፊና ፈላስፋ ስለ ኢየሱስ እንዲህ ብሎ ነበር፡- “እንደ ሞኝ ሰው ቆጥራችሁት ዝም ልታሰኙትና እንደ ክፉ ጋኔን ቆጥራችሁ ልትገድሉት ትችላላችሁ፡፡ ይህ ካልሆነ ግን በእግሮቹ ስር ተንበርክካችሁ ጌታዬና አምላኬ ብላችሁ ልትጠሩት ይገባል፡፡ ነገር ግን ታላቅ የሆነ ሰብዓዊ መምህር ብቻ ነበር የሚለውን የቂላቂል ንግግር አንናገር፡፡ ያንን አማራጭ እንድንይዝ ምንም ክፍተት አልተወልንም፡፡ በጭራሽ አላሰበውም፡፡” (1)

እውነታው ኢየሱስ አምላክ መሆኑ ነው፡፡ የስህተት ትምህርቶችን የመለያ ጥሩ መንገድ ስለ ኢየሱስ ምን እንደሚያስተምሩ መመርመር ነው፡፡ ኑፋቄዎችና ሐሰተኛ አብያተ ክርስቲያናት በአጠቃላይ የክርስቶስን አምላክነት ይክዳሉ፡፡ ለክርስቲያኖች ስለ ኢየሱስ የምናምነው ነገር ደህንነታችንን ይወስናል፡፡ ስለ እርሱ ያለን ዕውቀት ስለ እግዚአብሔር ባሕርይና ዓላማ ያለንን መረዳት እንዲሁም ከእርሱ ጋር ያለንን ግንኙነት ይወስናል፡፡

ሰዎች ማንነቱን በተመለከተ ግራ ቢጋቡም እውነተኛ ተከታዮቹ እንደሚያውቁትና እርሱም እንደሚያውቃቸው ኢየሱስ ተናግሯል (ማቴ. 7፡21-23)፡፡ ስለዚህ የኢየሱስን ማንነት ጠንቅቆ መረዳት በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡ እግዚአብሔር በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ራሱን ስለገለጠልን ስለ ኢየሱስ ለማወቅ ዋነኛ ምንጫችን እርሱ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ኢየሱስ የሚናገረው ነገር ብዙ ጎን ያለው ምስል ይሰጠናል፡፡ ኢየሱስ ስለ ራሱ የተናገረውንና ሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊያን የተናገሩትን በማየት እግዚአብሔርን የበለጠ ልናውቀው እንችላለን፡፡

መለኮትነቱ

ዛሬ በጣት የሚቆጠሩ ሰዎች የኢየሱስን ሰው መሆን ይጠራጠራሉ ነገር ግን አምላክነቱን የሚክዱት እጅግ ብዙ ናቸው፡፡ ሆኖም የእግዚአብሔር መገለጥ ገና ከጅምሩ ኢየሱስ አምላክ መሆኑን ይነግረናል፡፡ ለምሳሌ ያህል ኢሳይያስ የኢየሱስን ልደትና ንግሥና አስቀድሞ በተነበየበት ትንቢቱ ውስጥ አምላክነቱን ይናገራል፡- “ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል፡፡” (ኢሳ. 9፡6)

ኢየሱስ ራሱ “እኔና አብ አንድ ነን” ብሎ በማወጅ አምላክነቱን ተናግሯል (ዮሐ. 10፡33)፡፡ የዘመናችን ምሑራንና ተጠራጣሪዎች ኢየሱስ ምን ማለቱ እንደሆነ ሊከራከሩ ይችላሉ ነገር ግን በእርሱ ዘመን የነበሩት አድማጮቹ በትክክል ተረድተውታል፡፡ ጥቅሱ እንዲህ ይላል፡- “ስለ ስድብ፤ አንተም ሰው ስትሆን ራስህን አምላክ ስለ ማድረግህ ነው እንጂ ብለው መለሱለት፡፡” (ዮሐ. 10፡33)

ኋላ ላይ ደቀ መዛሙርቱ ተቃውሞና አለመረጋጋት በበዛበት ሰዓት ኢየሱስ “እኔን ያየ አብን አይቷል” በማለት አረጋገጠላቸው (ዮሐ. 14፡9-13)፡፡ በዚህ ሁኔታ ኢየሱስ አብን ሊገልጠው ነው የመጣው (ዮሐ. 1፡18)፡፡ አምላክ መሆኑንና ከአብ ጋር ያለውን ቁርኝት በግልፅ ስለ ተናገረ ተከታዮቹ ሊረዱና በዚህ እውነት ሊፅናኑ ይችላሉ፡፡

በብሉይ ኪዳን የኢየሱስ አምላክነት ከመነገሩና ኢየሱስ ራሱ እግዚአብሔር ወልድ መሆኑን ከመናገሩ በተጨማሪ የአዲስ ኪዳን ጸሐፊያንም መለኮት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የክርስቶስን ታላቅነትና የዘፍጥረትን የፍጥረት ጅማሬ ትረካ በማመላከት ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ አለ፡- “እርሱም የማይታይ አምላክ ምሳሌ ነው፤ የሚታዩትና የማይታዩትም፥ ዙፋናት ቢሆኑ ወይም ጌትነት ወይም አለቅነት ወይም ሥልጣናት፥ በሰማይና በምድር ያሉት ሁሉ በእርሱ ተፈጥረዋልና፡፡” (ቆላ. 1፡16) የመፍጠር ሥልጣን የእግዚአብሔር መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ይህንን ሥልጣን ከኢየሱስ ጋር አያይዞታል፡፡

የዕብራውያን መጽሐፍ ጸሐፊ የኢየሱስን አምላክነት በተመለከተ አስገራሚ ነገር ይናገራል፡- “እርሱም የክብሩ መንጸባረቅና የባሕርዩ ምሳሌ ሆኖ፥ ሁሉን በስልጣኑ ቃል እየደገፈ፥ ኃጢአታችንን በራሱ ካነጻ በኋላ በሰማያት በግርማው ቀኝ ተቀመጠ፡፡” (ዕብ 1፡3) በዚህ ቦታና በመላው አዲስ ኪዳን ውስጥ እንደተገለጠው የኢየሱስ አምላክነት የተልዕኮውና የአገልግሎቱ ማዕከላዊ ነገር ነው፡፡ ሰዎች ይህንን እውነት ቢቀበሉም ቢቃወሙም ከልባቸው ሊክዱት አይችሉም፡፡

ሰውነቱ

ከአምላክነቱ በተጻራሪ ኢየሱስ ሰው መሆኑን የሚክዱ ሰዎች ብዙም አያጋጥሙንም፡፡ ይህም ጠንካራ ታሪካዊ ማስረጃ በመኖሩ ምክንያት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ኢየሱስ ሰው ብቻ መሆኑን ሳይሆን ሰውም አምላክም መሆኑን ነው የሚያስተምረው፡፡ ዮሐንስ 1፡1-14 ኢየሱስ የእግዚአብሔር ቃል መሆኑን በማወጅ ይህንን አስደናቂና ምስጢራዊ እውነት ያስተዋውቃል፡- “በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ… ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን፡፡” በሌላ አባባል ስናስቀምጠው ኢየሱስ መቶ በመቶ አምላክ መቶ በመቶ ሰው ነው፡፡ ሁለት ባሕርያት ያሉት አንድ ማንነት፤ ሰውም አምላክም ነው፡፡

በምድር በነበረ ጊዜ ልክ እንደ እኛው የሰው ኖሮን ኖሯል፡፡ ህመም፣ ኀዘን፣ ደስታና ኃላፊነት ተሰምቶታል፡፡ ፈተና፣ ጭንቀትና ደስታ አጋጥሞታል፡፡ ሰው ሆኖ ያሳለፈው ሁኔታ ለኛ ትልቅ ትርጉም አለው፡፡ የኛን ችግር እንደሚካፈል ወንድምና የቤተሰብ አባል ልንቆጥረው እንችላለን፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው ይህ ከኢየሱስ ጋር ያለን ቤተሰባዊ ትስስር እርሱ በሕይወታችን ውስጥ የሚፈፅመው  አገልግሎትና ደስታው ማዕከል ነው፡- “የሚቀድሰውና የሚቀደሱት ሁሉ ከአንድ ናቸውና… ወንድሞች ብሎ ሊጠራቸው አያፍርም፡፡” (ዕብ. 2፡11-13)

እንደ እውነተኛ ወዳጅ (የቅርብ ወዳጅ) ኢየሱስ ውስጣችንን እንደሚረዳና ሁሉንም ነገር ከኛ ጋር እንደሚካፈል ዮሐንስ ጽፏል (ዮሐ. 15፡13-15)፡፡ ፍፁም እንደ ሆነ መሪ ድካማችንን ተረድቶ ያግዘናል ምክንያቱም እርሱ ራሱ ኃጢአት ባይሠራም ተፈትኗልና (ዕብ. 4፡14-16)፡፡ ሰው ሆኖ የመጣ አምላክ ብቻ ሊያደርገው በሚችለው መንገድ እንደ ታላቅ ወዳጅ ራሱን ስለኛ መስዋዕት አድርጓል (2ቆሮ. 5፡21፣ 1ጴጥ. 2፡21)፡፡

መሲህ መሆኑ

ስለ ኢየሱስ አምላክነትና ሰው መሆን ከሚናገሩት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች እንደምንረዳው ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣው ለዓላማ ነበር፡፡ በብሉይ ኪዳን ውስጥ እግዚአብሔር ሕዝቡን ነፃ የሚያወጣ መሲህ ወይም ንጉሥ ወደ ምድር እንደሚልክ ደጋግሞ ቃል ገብቷል፡፡ የዚህን መሲህ ምስል በተመለከተ ሁለት እርስ በርሳቸው የሚቃረኑ የሚመስሉ ነገሮች ተብለዋል፡፡ ኢሳይያስ 53፡1-6 “የህማም ሰው” ስለሆነው ለሕዝቡ ኃጢአት የሚሞት አገልጋይ ይናገራል፡፡ ሌላ ቦታ ደግሞ ኢሳይያስ የእግዚአብሔርን ጠላቶች ድል ነስቶ የማያልቅ የሰላም መንግሥት ስለሚመሠርት ነፃ አውጪ ንጉሥ ይናገራል (ኢሳ. 9፡6)፡፡

ስለ መሲሁ ባሕርይ የሚናገሩት እነዚህ ሁለቱ የሚጣረሱ የሚመስሉ ምስሎች ፖለቲካዊና ባሕላዊ ነፃ መውጣትን እንደሚያመጣ ያምኑ ለነበሩት አይሁዶች ትልቅ ችግር ፈጥረው ነበር፡፡ ሁለቱን ትንቢቶችና ተስፋዎች ለማስታረቅ ጥረት ያደርጉ ስለነበር መሲሁ ሲመጣ ሊያውቁት አልቻሉም ነበር፡፡ መጀመርያ የመጣው መከራን የሚቀበል አገልጋይ ሆኖ ስለነበር መስፈርታቸውን አላሟላም ነበር፡፡ ኢየሱስ መሲሁ ወይም ክርስቶስ (የተቀባ) መሆኑን ተናግሮ ነበር፡፡ ነፍሱን በመስጠትና ዳግመኛ ሞትን ድል በመንሳት እንደተነሳ አምላክ-ሰው በመጽሐፍ ቅዱስ የተነገሩትን የመሲሁ ትንቢቶች መፈጸም የቻለው እርሱ ብቻ ነው፡፡ መጀመርያ ስለ ኃጢአታችን ሞቶ ከእግዚአብሔር ጋር ሊያስታርቀን  መከራን እንደሚቀበል አገልጋይ ሆኖ ነበር የመጣው፡፡ “እንዲሁ የሰው ልጅም ሊያገለግልና ነፍሱን ለብዙዎች ቤዛ ሊሰጥ እንጂ እንዲያገለግሉት አልመጣም፡፡” (ማር. 10፡45፣ ዮሐ. 3፡14-15፣ 1ጴጥ. 3፡18፣ 1ዮሐ. 2፡2)

ኢየሱስ ሕዝቡን ከኃጢአትና ከዓለም ጥፋት ነጻ ለማውጣት ዳግመኛ እንደ ድል ነሺ ንጉሥ እንደሚመጣም ተስፋ ሰጥቷል፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ የእግዚአብሔርን መንግሥት መምጣት እንዲህ በማለት ነበር ያወጀው፡- “በኋላም፥ መንግሥቱን ለእግዚአብሔር ለአባቱ አሳልፎ በሰጠ ጊዜ አለቅነትንም ሁሉና ሥልጣንን ሁሉ ኃይልንም በሻረ ጊዜ፥ ፍጻሜ ይሆናል፡፡ ጠላቶቹን ሁሉ ከእግሩ በታች እስኪያደርግ ድረስ ሊነግሥ ይገባዋልና፡፡” (1ቆሮ 15፡24-25፣ ዮሐ. 14፡1-3፣ ራዕ. 9፡11-16)

ኢየሱስ ማነው? ኢየሱስ ፍፁም ሰውና ፍፁም አምላክ፣ ከዚህ ቀደም የመጣና ተመልሶ ዳግመኛ የሚመጣ መሲህ መሆኑ እግዚአብሔር በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ገልጧል፡፡ በእርሱ የመለኮት ሙላት ሁሉ በሰውነት ተገልጦ ይኖራል (ቆላ. 2፡10)፡፡ ስለዚህ ኢየሱስን እንደ አምላክ ልናመልከው፣ እንደ ምሳሌያችን ልንከተለውና እንደ አዳኛችን ልንታመነው ይገባል፡፡

ማጠቃለያ

እግዚአብሔር በወልድ በኩል እንዴት ራሱን እንደገለጠ በማጥናት የበለጠ ልናውቀው እንችላለን፡፡

  • ብሉይና አዲስ ኪዳናት የኢየሱስን አምላክነት ያውጃሉ፡፡
  • ኢየሱስ ራሱ አምላክ መሆኑን ተናግሯል፡፡
  • ኢየሱስ ፍፁም አምላክ ፍፁም ሰው ነው፡፡
  • ኢየሱስ ሰው እንደመሆኑ መጠን ከኛ እንደ አንዱ ነው፣ ይረዳናል፣ እኛን ይወክለናል፣ ምሳሌም ይሆነናል፡፡
  • ኢየሱስ መከራን ተቀባይ አገልጋይና ነፃ አውጪ ንጉሥ የሆነው መሲህ መሆኑን ተናግሯል፡፡

ማስታወሻ

(1) C.S. Lewis, Mere Christianity (San Francisco: Harper, 2001), 52.

ኢየሱስ አምላክ መሆኑን የሚያረጋግጡ ጥቅሶች

  1. አምላክ ተብሏል፡፡

ዮሐ. 1:1፣14፣18፣ 10:30፣ 20:28 2ተሰ. 1:12፣ ሮሜ 9:5 ቲቶ 2:13፣ ቆላ. 2:9 ዕብ. 1:3

  1. እግዚአብሔርን አባቱ ብሎ በመጥራት “ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር እኩል አድርጓል፡፡”

ዮሐ. 5፡18

  • ከሰማይ የመጣ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑ ተነግሯል፡፡

ሲጠመቅ ማቴ. 3:16-17፣ ማር. 1:10-11፣ ሉቃ 3:21-22; ዮሐ. 1:32-34

በተራራው ክብር ወቅት፡ ማቴ. 17:5፣ ማር. 9:7፣ ሉቃ 9:35; 2ጴጥ. 1:17

  1. ኢየሱስ ከብሉይ ኪዳኑ ያሕዌ ጋር አንድ ነው፡፡

ሉቃ 1:76 ከሚል. 3:1

ሮሜ 10:13 ከኢዩ. 2:32

ሮሜ 14:9-11 ከኢሳ. 45:23-25 ጋር አነፃፅሩ፡፡

  1. ኢየሱስ መለኮታዊ ባሕርያት ሁሉ አሉት፡፡ እነዚህ ባሕርያት የፈጣሪ ብቻ ናቸው፡፡

ዘላለማዊ፡ ኢሳ. 9:6፣ ዮሐ. 1:1-2፣ 8:58፣ 17:5፣ ዕብ 1:8፣ ራዕ 1:8

በሁሉም ቦታ የሚገኝ፡ ማቴ. 18:20፣ 28:20፣ ዮሐ. 3:13፣ ኤፌ. 1:23

ሁሉን አዋቂ 9:4፣ ዮሐ. 2:24-25፣ 6:64፣ 16:30፣ 21:17፣ ቆላ 2:3

ሁሉን ቻይ፡ ኢሳ. 9:6፣ ማቴ. 28:18፣ ፊል. 3:21፣ ራዕ. 1:8

ራሱን በራሱ የሚያኖር፡ ዕብ. 1:10-12፣ 13:8

  1. ኢየሱስ አምላክ ብቻ የሚሠራቸውን ሥራዎች ሠርቷል፡፡

መፍጠር፡ ዮሐ. 1:3-10፣ ቆላ. 1:16-17፣ ዕብ. 1:2፣3፣10

መግቦት፡ ሉቃ. 10:22፣ ዮሐ. 3:35፣ 17:2፣ ኤፌ. 1:22፣ ቆላ.  1:17

ኃጢአትን ይቅር ማለት፡ ማቴ. 9:27፣ ማር. 2:5-10፣ ቆላ. 3:13

ሙታንን በማስነሳት ፍርድ መስጠት፡ ማቴ. 25:31-32፣ ዮሐ. 5:19-30፣ ሐዋ. 10:42፣ 17:31፣ ፊል. 3:21፣ 2ጢሞ. 4:1

ጸሎትና አምልኮን ተቀብሏል፡ ሉቃ. 24:51-52፣ ዮሐ. 5:23 14:14፣ ሐዋ. 7:59፣ 16:31፣ ፊል. 2:10፣11፣ ዕብ. 1:6