የቁርኣን ግጭቶች – አላህ ፍጥረቱን በቀጥታ ያናግራል ወይስ አያናግርም?

አላህ ፍጥረቱን በቀጥታ ያናግራል ወይስ አያናግርም?

ማሳሰብያ፡- በሰማያዊ የተጻፈው የኛ ሲሆን በጥቁር የተጻፈው የእርሱ ነው፡፡

ያናግራል፡-

ሱራ 4፡64 “ከዚህም በፊት በአንተ ላይ በእርግጥ የተረክናቸውን መልክተኞች፣ ባንተ ላይም ያልተረክናቸውን መልክተኞች እንደላክን ላክንህ። አላህም ሙሳን ማነጋገርን አነጋገረው።”

አያናግርም፡-

ሱራ 42፡51 “ለሰው አላህ በራእይ፣ ወይም ከግርዶ ወዲያ፣ ወይም መልክተኛን መልአክን የሚልክና በፈቃዱ የሚሻውን ነገር የሚያወርድለት ቢሆን እንጅ፣ በገሃድ ሊያናግረው ተገቢው አይደለም። እርሱ የበላይ ጥበበኛ ነውና።”

መልስ

4፥164 ከዚህም በፊት በአንተ ላይ በእርግጥ የተረክናቸውን መልክተኞች ባንተ ላይም ያልተረክናቸውን መልክተኞች እንደላክን ላክንህ፡፡ “አላህም ሙሳን ማነጋገርን አነጋገረው”፡፡

“አላህም ሙሳን ማነጋገርን አነጋገረው” የሚለው ሃይለ-ቃል ይሰመርበት። እዚህ አንቀጽ ላይ “በቀጥታ” የሚል ቃል የለም። ይህ የጠያቂው ቅጥፈት ነው። አላህ ሙሳን አነጋግሮታል ወይ? አዎ! ግን እንዴት? አላህ ነቢያትን በሦስት አይነት መንገድ የሚያነጋግረው፦

ቀጣፊው አንተ እንጂ እኔ አይደለሁም፡፡ በዚህ ጥቅስ ውስጥ “ማነጋገርን አነጋገረው” የተባለው አላህ ሙሴን በቀጥታ ማነጋገሩን እንደሚያሳይ የተናገረው ሙሐመድ ራሱ እንጂ እኔ አይደለሁም፡፡ ከሳሂህ አል-ቡኻሪ እጠቅስልሃለሁ፡-

Narrated Abu Huraira: The Prophet said, “Adam and Moses debated with each other and Moses said, ‘You are Adam who turned out your offspring from Paradise.’ Adam said, “You are Moses whom Allah chose for His Message and for His DIRECT talk, yet you blame me for a matter which had been ordained for me even before my creation?’ Thus Adam overcame Moses.” (Sahih al-Bukhari Vol. 9, Book 93, Hadith 606; Vol. 6, Book 60, Hadith 262)

Narrated Abu Huraira: Allah’s Apostle said, “Adam and Moses argued with each other. Moses said to Adam. ‘You are Adam whose mistake expelled you from Paradise.’ Adam said to him, ‘You are Moses whom Allah selected as His Messenger and as the one to whom He spoke DIRECTLY; yet you blame me for a thing which had already been written in my fate before my creation?”‘ Allah’s Apostle said twice, “So, Adam overpowered Moses.” (Sahih al-Bukhari Vol. 4, Book 55, Hadith 621)

በዚህ ሐዲስ ውስጥ አዳም ሙሴን “…አላህ .. በቀጥታ ለማነጋገር የመረጠህ…” ሲለው ይታያል፡፡ ስለዚህ አንተው ቀጣፊ ሆነህ የገዛ ነቢይህን ሰድበኸዋል፡፡

ከዚህ በኋላ የምትሰጠው ሐተታ ዋጋ የለውም፡፡ ነገር ግን “መልሴን ቆረጡብኝ” እንዳትል እንዳለ እናስቀምጠዋለን፡፡

42፥51 ለሰው” አላህ “በራእይ”፣ ወይም “ከግርዶ ወዲያ”፣ ወይም “መልክተኛን መልአክን” የሚልክ እና በፈቃዱ የሚሻውን “የሚያወርድለት” ቢሆን እንጅ በገሃድ “ሊያናግረው” ተገቢው አይደለም፤ እርሱ የበላይ ጥበበኛ ነውና።

እነዚህ ሦስት መንገዶች፦

አንደኛ መንገድ በሩዕያ ማናገር ነው፤ “ሩዕያ” رُّءْيَا ማለት “ራዕይ” ማለት ሲሆን ይህም ራዕይ በሪዕይ ውስጥ ሆነው የሚመጣላቸው ንግግር ነው፤ “ሪዕይ” رِءْي ማለት “እይታ” ማለት ሲሆን እውን ላይ ሆኖ ሳይተኛ በሰመመን ወይም በተመስጦ”contemplation” ላይ ሆነው ሲሆን ነው፤ የራዕይ አንዱ ገፅታ “መናም” مَنَام ማለት “ህልም” ሲሆን ይህም በነውም ሆነው የሚመጣላቸው ንግግር ነው፤ “ነውም” نَوْم ማለት “እንቅልፍ” ማለት ነው፤ በዚህ ሁኔታ አላህ ወህይ ካወረደለት ነቢይ መካከል ተጠቃሽ የሚሆነው የኢማን አባት የሆነው ኢብራሂም ነው፦

37፥102 ከእርሱ ጋርም ለሥራ በደረሰ ጊዜ «ልጄ ሆይ! “እኔ በሕልሜ እኔ  የማርድህ ሆኜ አያለሁ፡፡ ተመልከትም፤ ምን ታያለህ?» አለው”፡፡ «አባቴ ሆይ! የታዘዝከውን ሥራ፡፡ አላህ ቢሻ ከታጋሾቹ ሆኜ ታገኘኛለህ» አለ፡፡

37፥105 «ራእይቱን በእውነት አረጋገጥክ፡፡» እኛ እንደዚሁ መልካም ሠሪዎችን እንመነዳለን፡፡

ሁለተኛ መንገድ በተክሊም ማናገር ነው፤ “ተክሊም” تَكْلِيم ማለት በሁለት ማንነት መካከል የሚደረግ “ምልልስ”conversation” ሲሆን አላህ ያለ ራዕይና ህልም ወይም ያለ መልአክ ሳይታይ ከግርዶ ወዲያ ሆና የሚያናግርበት መንገድ ነው፤ በዚህ መልኩ አላህ ያናገረው ነብይ ለናሙና ያክል ሙሳ ተጠቃሽ ነው፦

19፥51 በመጽሐፉ ውስጥ ሙሳንም አውሳ፡፡ እርሱ ምርጥ ነበርና፡፡ መልክተኛ ነቢይም ነበር፡፡

19፥52 ከጡር ቀኝ ጎን በኩልም ጠራነው፤ ያነጋገርነውም ሲኾን አቀረብነው፡፡

ሶስተኛ መንገድ በመልአክ ማናገር ነው፤ “ረሱል” رَسُول የሚለው ቃል “ተላላኪ” ማለት ሲሆን “መለክ” مَلَك ማለትም “መልአክ” የሚለው ቃል ተለዋዋጭ”inter-change” ሆኖ የመጣ ነው፤ ይህም የወህይ መልአክ ጂብሪል”ዐ.ሰ.” ነው፤ በዚህ ሁኔታ አላህ ወህይ ካወረደለት ነብይ መካከል ነቢያችን ተጠቃሽ ናቸው፦

2፥97 ለጂብሪል ጠላት የኾነ ሰው በቁጭት ይሙት በላቸው፡፡ እርሱ ቁርኣኑን ከበፊቱ ለነበሩት አረጋጋጭ ለምእመናን መሪና ብስራት ሲኾን በአላህ ፈቃድ በልብህ ላይ አውርዶታልና፡፡

“በአላህ ፈቃድ በልብህ ላይ አውርዶታልና” የሚለው ሃይለ-ቃል እና “መልክተኛን መልአክን የሚልክ እና በፈቃዱ የሚሻውን የሚያወርድለት ቢሆን እንጅ” የሚለው ሃይለ-ቃል ይሰመርበት።

አላህ አንድን ነቢይ በራእይ ወይም በግርዶ አሊያም መልእክተኛ መልአክ በመላክ በእነዚህ ሦስት መንገዶች እንጂ ሊያናግር ተገቢው አይደለም። በተረፈ ሱረቱ አሽ-ሹራህ 42፥51 ላይ አላህ አያናግርም አላለም። ባይሆን በሦስት መንገድ እንደሚያናግር ቢገልጽ እንጂ። ይህ የሚያሳየው የጠያቂውን እጥረተ-ንባብ ነው።

የንባብ እጥረት ያለበት ማን እንደሆነ በግልፅ ታይቷል፡፡ እኔ የጻፍኩትን እንኳ በትክክል ማንበብ አልቻልክም፡፡ ጥያቄው “አላህ ያናግራል ወይስ አያናግርም?” የሚል ሳይሆን “አላህ በቀጥታ ያናግራል ወይስ አያናግርም?” የሚል ነው፡፡ ቁርኣን በአንዱ ቦታ ላይ አላህ ማንንም በቀጥታ እንደማያናግር የሚገልፅ ሲሆን በሌላ ቦታ ላይ ግን ሙሴን በቀጥታ ማናገሩ ተጽፏል፡፡ በሳሂህ ሐዲሳት እንደተዘገበው አላህ ሙሴን በቀጥታ እንዳናገረው ያንተው ነቢይ ምስክርነቱን ሰጥቷል፡፡ ይህም በመጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሙሴ የተነገረው ቃል ነፀብራቅ ነው፡-

“እርሱም፦ ቃሌን ስሙ፤ በመካከላችሁ ነቢይ ቢኖር፥ እኔ እግዚአብሔር በራእይ እገለጥለታለሁ፥ ወይም በሕልም እናገረዋለሁ። ባሪያዬ ሙሴ ግን እንዲህ አይደለም፤ እርሱ በቤቴ ሁሉ የታመነ ነው። እኔ አፍ ለአፍ በግልጥ እናገረዋለሁ፥ በምሳሌ አይደለም፤ የእግዚአብሔርንም መልክ ያያል፤ በባሪያዬ በሙሴ ላይ ትናገሩ ዘንድ ስለ ምን አልፈራችሁም? አለ።” (ዘኁልቁ 12፡6-8)

አል ባይዛዊን የመሳሰሉት ሙስሊም ሊቃውን ሙሴ ከአላህ ጋር ልክ ከመልአክ ጋር ፊት ለፊት እንደሚነጋገረው መነጋገሩን ይገልፃሉ http://www.bible.ca/islam/dictionary/M/moses.html ፡፡ በዚህ ረገድ ሙሴ ከነቢያት ሁሉ የተለየ መሆኑን ሙስሊም ሊቃውንት የሚቀበሉት እውነታ ነው፡፡ ለዚህ ነው በእስልምና “ከሊሙላህ” كليم الله‎  የሚል ማዕርግ የተሰጠው፡፡ ስለዚህ አላህ ፍጥረቱን በቀጥታ ወይም ፊት ለፊት ያናግራል ወይንስ አያናግርም? ግጭቱ እንዳለ ነው፡፡

የቁርኣን ግጭቶች