አምላክ ሰው ነው?

 

አምላክ ሰው ነው?

 


3. ኢየሱስ ሰው መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ በብዙ ቦታዎች ላይ ይናገራል (አሕመዲን ለዚህ ማስረጃ የሚሆኑ 20 ጥቅሶችን ጠቅሰዋል)፡፡ አምላክ ከሆነ ለምን በርካታ ስፍራ ላይ “የሰው ልጅ” “ሰው” ተባለ? አምላክ ሰው ነውን? የሚከተሉት ጥቅሶች አምላክ ሰው እንዳልሆነ ይገልጻሉ፡-

ሀ) “ይዋሽ ዘንድ እግዚአብሔር ሰው አይደለም፤ ይፀፀትም ዘንድ የሰው ልጅ አይደለም፡፡” (ዘኁልቁ 23:19)

ለ) “የእስራኤል ክብር የሆነው እግዚአብሔር አይዋሽም፤ አይፀፀትም፤ እርሱ ይፀፀት ዘንድ ሰው አይደለምና፡፡” (1ኛ ሳሙኤል 15:29)

ሐ) “እኔ በመካከላችሁ ያለሁ ቅዱስ አምላክ ነኝ እንጂ ሰው አይደለሁምና፤ በቁጣ አልመጣም፡፡” (ትንቢተ ሆሴዕ 11:9)

“ኢየሱስ ፍፁም ሰው፣ ፍፁም አምላክ ነው” ስንል “አምላክ ሰው ነው” እያልነው ነው፡፡ ይህ ታድያ አምላክ ሰው እንዳልሆነ የተገለፀውን መፃረር አይደለምን?

በመጽሐፍ ቅዱስ መሠረት “የሰው ልጅ” የሚለው ማዕርግ ጠያቂው ካሰቡት በተፃራሪ ኢየሱስ በሥጋ የተገለጠ አምላክ መሆኑን ያሳያል (ዳንኤል 7፡13፣ ይህንን ጥቅስ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ደጋግመን ስለምናነሳው የክርስቶስን አምላክነት በተመለከተ የሚሰጠንን ምልከታ ግልፅ እናደርጋለን)፡፡ ክርስቲያኖች ኢየሱስ ፍፁም ሰው ፍፁም አምላክ እንደሆነ እንጂ ሰው ብቻ፣ አምላክ ብቻ፣ ግማሽ ሰው ግማሽ አምላክ፣ ወደ ሰው የተለወጠ አምላክ፣ ወዘተ. እንደሆነ አያምኑም፡፡ ጠያቂው ይህንን ጥያቄ ያቀረቡት ከራሳቸው የተሳሳተ መረዳት በመነሳት ነው፡፡ ክርስቲያኖች “አምላክ ሰው ነው” አይሉም፡፡ ነገር ግን “ኢየሱስ ፍፁም ሰው ፍፁም አምላክ ነው” በማለት ያምናሉ፡፡ ሰው የሆነው የኢየሱስ ባሕርይ አምላክ አይደለም፡፡ አምላክ የሆነውም የኢየሱስ ባሕርይ ሰው አይደለም፡፡ እነዚህ የኢየሱስ ሁለቱ ባሕርያት ሳይነጣጠሉና ሳይቀላቀሉ ይኖራሉ፡፡ ስለዚህ ሁለቱ ባሕርያት ስላልተቀላቀሉ በብሉይ ኪዳን ዘመን አምላክ ሰው አለመሆኑ መነገሩ በአዲስ ኪዳን አምላክ በሥጋ የመገለጡን እውነታ አይፃረርም፡፡ በተጨማሪም እነዚህ የብሉይ ኪዳን ጥቅሶች የሚናገሩት አምላክ እንደ ሰው ልጆች ኃጢአተኛና ቃሉን የሚያጥፍ አለመሆኑን እንጂ በእነዚህ የሰው ልጅ ችግሮች ባልተበከለ ሁኔታ በሥጋ መገለጥ አለመቻሉን እንዳልሆነ ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ በዘመነ ብሉይ እግዚአብሔር በሰው አምሳል የተገለጠባቸው ጊዜያት ነበሩ (ዘፍጥረት 18፡1-33፣ 32፡24-32)፡፡

 

አሕመዲን እንዲህ በማለት ይጠይቃሉ፡- ሌላው አጠያያቂ ነጥብ ሐዋርያት ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ወይም ከመላእክት የላቀ አካል መሆኑን ከተቀበሉ ክርስቶስን “ሰው” ብለው መጥራታቸው ለምን ይሆን? ሐዋርያት የኢየሱስን አምላክነት ከተቀበሉ በኋላ “ሰው” ነበረ ብለው ማስተማራቸው ክብሩን መንካትና ደረጃውን መቀመቅ መክተት አይሆንምን?

ሐዋርያት እርሱ ያልሆነውን አላሉም፡፡ ስለዚህ አምላክም ሰውም መሆኑን መናገራቸው የእርሱን ክብር የሚነካ አይደለም፡፡ ሰው እንዲሆን ያደረገው ለሰው ልጆች ያለው ፍቅር ነው፡፡ ይህ ከሰው ልጆች እጅግ ርቆ ለሚገኝ የምናብ “አምላክ” የሚቻል አይደለም፡፡ አምላካችን ግን የቅርብና አፍቃሪ አምላክ በመሆኑ ይህንን አድርጓል፡፡

ጠያቂው አሁንም ይቀጥላሉ፡- ሐዋርያት ኢየሱስን አይተውታል፡፡ አናግረውታል፡፡ አብረው ተመግበዋል፡፡ ይህን ሁሉ ሲፈጽሙ ግን ኢየሱስ ልክ እንደ እነሱ ሰብአዊ ፍጡር መሆኑን ቅንጣት ታህል ተጠራጥረው አያውቁም፡፡ ታድያ በዚህ ሁኔታ እያለ ኢየሱስ ሰው ሳይሆን “የዓለማት ፈጣሪ አምላክ ነው” ቢባል የሚሰማቸው ድንጋጤና ግርምት እኛ አንድ የምናውቀው ሰው አምላክ ወይም የዓለም ፈጣሪ ነው ብንባል የሚሰማንን ያህል ነው፡፡ ለምን? ቢሉ ኢየሱስ በርካታ ሰዋዊ ተግባራት ሲፈፅም ፤ ስኬትና ውድቀት ሲፈራረቅበት፤ ሀሴትና ሀዘን ሲመላለስበት ተመልክተዋል፡፡ ታድያ ይህ መሰሉ ሁኔታ የአምላክነት ክብርና ደረጃውን እንዲያስቡ አድርጓቸው ነበር ብሎ ማሰብ ያስኬዳልን? አይመስለኝም!

ለእርስዎ ባይመስልዎትም እነርሱ ግን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ የተገለጠ አምላክ መሆኑን ተቀብለውና ጽፈውልን አልፈዋል፡፡ ውድ አሕመዲን፣ ሁሉን ቻዩ አምላክ ወደ ምድር መጥቶ ሰው በመሆን በመካከላችን የመኖር ችሎታ ያንሰዋል ብለው ያምናሉን? እንደርሱ ብለው የሚያምኑ ከሆነ የፈጣሪን ሁሉን ቻይነት ስለካዱ ንስሐ መግባትና ሁሉን ቻይነቱን መቀበል ያሻዎታል፡፡ ሐዋርያት ምስክርነታቸውን ከሰጡ ከ 600 ዓመታት በኋላ ምስክር በሌለበት ወደ ዋሻ ገብቶ በመውጣት ይህ ሁሉ ነገር ትክክል እንዳልሆነ መልአክ እንደነገረው የነገርዎትን ሰው ስብከት በጭፍን ተቀብለው ከሆነ ደግሞ ከባድ ስህተት ፈፅመዋል፡፡ የሐዋርያትን ትምህርት የሚክደውን የሰውየውን ትምህርት ሲቀበሉ እውነት ስለመናገሩ ምን ያህል ጥናትና ምርምር አድርገዋል? ለእውነተኛነቱስ የሚያቀርቡት ማስረጃ ምንድነው? የአንድን ሰው ምስክርነት በጭፍን ከማመንና ቃላቸው እውነት መሆኑን እስከ ሞት ድረስ በመታመን የመሰከሩትን የዓይን ምስክሮች ዘገባ ከማመን የትኛው ይመረጣል? ትክክለኛ ውሳኔ መወሰን እንዲችሉ እግዚአብሔር ልቦና ይስጥዎት!

 

 

ለአሕመዲን ጀበል 303 ጥያቄዎች የተሰጠ መልስ ማውጫ