የኢየሱስን ተዓምር ያዩ ሰዎች “ሰው” ብለው ካመኑ ክርስቲያኖች ለምን አምላክ ነው ትላላችሁ?

 


14. ኢየሱስ ተዓምር ሲያሳይ ተአምራቱን ያዩ ሰዎች ተደንቀዋል፡፡ በማቴዎስ 9፡8 ላይ “ሕዝቡም አይተው ተደነቁ፤ ለሰውም እንዲህ አለ ሥልጣን የሰጠ እግዚአብሔርን አከበሩ” ይላል፡፡ ታዲያ ይህን ተአምር ያየው ሕዝብ ሁሉ ከሃዲ ነውን? ለምን ቢሉ “ኢየሱስ አምላክ ስለሆነ በራሱ ስልጣን ተአምራቱን አደረገ” ብለው እንደ ዛሬዎቹ ክርስቲያኖች አላመኑም፡፡ “ለሰውም እንዲህ አለ ስልጣን የሰጠ እግዚአብሔርን አከበሩ” ይላል፡፡ ታዲያ ኢየሱስ አምላክ ቢሆንና በራሱ ስልጣን ቢኖረው ለምን እግዚአብሔር ይህን ተአምር እንደሰጠው ገለፀ? እግዚአብሔር የአብ የወልድና የመንፈስ ቅዱስ የጋራ ጥምረት ከሆነና “እግዚአብሔር” የሚለው ኢየሱስን የሚጨምር ከሆነ ህዝቦቹ እግዚአብሔርን ሲያከብሩ ኢየሱስንንም ይጨምሩት ነበር፡፡ ነገር ግን “ሰው ነው” ብለው አመኑበት፡፡ ታድያ ያንን ሁሉ ታላላቅ ተአምራት ያየውንና ኢየሱስን የተከተለውን ህዝብ እምነት ትተን በተቃራኒ ማመን አግባብ ነውን?

ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣው ፍፁም ሰው ሆኖ የገዛ ፈቃዱን ሙሉ በሙሉ ለአብ በማስገዛት ከአብ በተቀበለው ሥልጣንና በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ይሰራ ስለነበር ሕዝቡ አልተሳሳተም፡፡ ሆኖም ሕዝቡ የኢየሱስን አምላክነት ተረድቷል ብሎ ማለት አይቻልም፡፡ ሕዝብ በወቅቱ ካየውና ቀደም ሲል ከነበረው ቅድመ ግንዛቤ በመነሳት የተሳሳቱ ድምዳሜዎች ላይ መድረስ መቻሉ መረሳት የለበትም፡፡ ስለዚህ በሕዝብ አስተያየት ላይ በመመስረት ነገረ መለኮታዊ አስተምህሮን መገንባት ፈፅሞ የተሳሳተ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ውስጥ ሕዝብ ጳውሎስና በርናባስ ተዓምራትን ሲያደርጉ በማየቱ ምክንያት “አማልክት በሰው ተመስለው ወርደዋል” በማለት ሊሰዋላቸው ተነስቶ ነበር (የሐዋ. ሥራ 14፡11)፡፡ ኢየሱስን የተቀበለው ያው ሕዝብ እንዲሰቀል ጲላጦስን ተማፅኗል፡፡ ሕዝብ አንዳንዴ እውነትን ቢናገርም ነገር ግን አብዛኛውን ጊዜ የተሳሳተ ነገር ይናገራል፡፡ ስለዚህ አስተምህሯችንን የምንመሰርተው በሕዝብ አስተያየት ላይ ሳይሆን ኢየሱስ ራሱ በተናገረውና በእርሱ የተመረጡት ሐዋርያት ባስተማሩት ትምህርት ላይ ነው፡፡ አሕመዲን ኢየሱስ ጌታ፣ አምላክና አንድያ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን የመሰከሩትን የሐዋርያትን ምስክርነት ችላ በማለት ብዙ ጊዜ በመሳሳት የሚታወቀውን የሕዝቡን ምስክርነት ለመስማት መምረጣቸው ለምን ይሆን? (2ጴጥሮስ 1፡1-3፣ ዮሐንስ 1፡1-3፣ 1ዮሐንስ 5፡20፣ ዮሐንስ 20፡28-29)፡፡ ለሕዝብ አስተያየት ይህን ያህል ቦታ የሚሰጡ ከሆነ ነቢዩ ሙሐመድንና ከሊፋዎቹን ከመስማት ይልቅ እስልምናን ባለመቀበሉ ምክንያ በሰይፍ ስለት የታጨደውን ሌላውን ሕዝብ ለምን አልሰሙም?

 

 

ለአሕመዲን ጀበል 303 ጥያቄዎች የተሰጠ መልስ ማውጫ