ኢየሱስ አምላክ ከሆነ በማርቆስ 11:12-14 ላይ በለሲቱ ፍሬ እንደሌለባት ለምን አላወቀም?

 


32. በማርቆስ 11:12-14 ላይ “በማግስቱ ከቢታንያ ሲወጣ ተራበ ቅጠል ያለበት በለስ በሩቁ አይቶ ምናልባት አንዳች አገኘባት እንደሆነ ብሎ ወደርሷ መጣ፡ ነገር ግን የበለሰ ወራት አልነበረምና ከቅጠል በቀር ምንም አላገኘባትም፡፡ ከዚያም ዛፏን፡ ከአሁን ጀምሮ ለዘለዓለም ማንም ፍሬ ከአንቺ አይብላ አላት፡፡ ደቀመዛሙርቱም ይህን ሲናገር ሰሙት፡፡ ይላል፡፡ “አምላክ ነው” የሚበላው ኢየሱስ እርሱ እንኳን ባለበት ሆኖ ፍሬ ይኑራት አልያም አይኑራት የሚለውን ማወቅ ተስኖት ለማረጋገጥ ቀርቦ ቢያጣባት ለምን ይረግማታል? እርሷ ምን ታድርግ? የበለሰ ወቅት አልነበረም፡፡ ኢየሱስ አምላክ ቢሆን ኖሮ እንዴት ከፊቱ ራቅ ብላ ያለች በለሰ ፍሬ ይኑራት አይኑራት ማወቅ ይሳነዋል? በለሷንስ አምላክ አይደል ፍሬ እንድታፈራ የሚያደርጋት? አምላክስ ከበለስ ምን ጉዳይ ኖሮት ሲያጣባት ይረግማታል?

መጽሐፍ ቅዱስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኃጢአት ያልነካው ፍፁም ሰው እንደሆነ ይናገራል፡፡ ከሰማይ የወረደ የእግዚአብሔር ልጅ በመሆኑ ግን ሁሉን የሚያውቅ መለኮት ነው (ለጥያቄ ቁጥር 10 የተሰጠውን መልስ ይመልከቱ)፡፡ ስለዚህ የእውቀት ውሱንነት ቢታይበት ወይም ቢራብ ፍፁም ሰው መሆኑን የሚያረጋግጥ እንጂ መለኮታዊ ባሕርዩን የሚነካ አይደለም፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ የበለስ ወራት እንዳልሆነ እያወቀ ስለምን ሄደ? ለምንስ ረገማት? በለስ የፍሬ ወራትዋ ሲቀርብ ቅጠሏ ይለመልማል፡፡ በዚህ ጊዜ በጫፎቿ ላይ ለምግብነት ሊውሉ የሚችሉ በአረብኛ ታቅሽ የተሰኙ እንቡጦች ይኖሯታል፡፡ እነዚህ እንቡጦች ካልታዩ በለሲቱ በዚያን ዓመት ፍሬ የማፍራት ተስፋ የላትም፡፡ ስለዚህ በለሲቱ ለብዙዎች መሰናክል የሆነች፣ ብዙዎችን ያሳዘነች መካን ነበረች፡፡[7] ኢየሱስ በለሲቱን በመርገም እንድትደርቅ በማድረጉ እንቅፋትን ከማስወገዱም በላይ ሁለት መንፈሳዊ ትምህርቶችን አስተላልፏል፡፡ የመጀመርያው ለደቀ መዛሙርቱ እምነትን ማስተማር ሲሆን (ማርቆስ 11፡21,24) ሁለተኛው ደግሞ ለእስራኤል በተግባራዊ ምሳሌ የተደገፈ መልእክትን መስጠት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅደስ መሠረት በለስ የእስራኤል ምሳሌ ስትሆን ፍሬ ካላፈራች ወይም ፍሬዋ መልካም ካልሆነ እግዚአብሔር እንደሚያደርቃት በነቢያቱ በኩል በተደጋጋሚ ተናግሯል (ሆሴዕ 9፡10-16፣ ሚክያስ 7፡1-4፣ ናሆም 3፡12፣ ኤርምያስ 29፡15-19)፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የእስራኤልን እንደ ፍሬ አልባ በለስ መድረቅ አስቀድሞ ተናግሯል (ሉቃስ 12፡5-9)፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ መካኒቱ በለስ ፍሬ አልባ የሆነችው እስራኤል እንደምትደርቅ ተግባራዊ ምሳሌ እየሰጠ መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ ስለዚህ ይህንን ታላቅ መንፈሳዊ መልእክት ያዘለ ታሪክ ጠምዝዞ የኢየሱስን አምላክነት ለመቃወም መጠቀም አግባብ አይደለም፡፡

 

 

ለአሕመዲን ጀበል 303 ጥያቄዎች የተሰጠ መልስ ማውጫ