ኢየሱስና አምላክ እኩል ቢሆኑ ኖሮ ለምን ኢየሱስ ለአምላኩ ጸለየ?

 


42. ኢየሱስ በተደጋጋሚ ለአምላኩ ሲጸልይ ነበር፡፡ ይህም በማቴዎስ 26:39፣ ማቴዎስ 26:42፣ ማቴዎስ 26:44፤ ማርቆስ 1:35 ማርቆስ 14:35፣ ማርቆስ 14:39፣ ሊቃስ 5:16፣ ዮሐንስ 17:1-3፣ ዕብራባዊያን 5:7 እና ሉቃስ 6:12 ላይ ተገልጿል፡፡ ኢየሱስና አምላክ እኩል ቢሆኑ ኖሮ ለምን ኢየሱስ ለአምላኩ ጸለየ? አምላክ የሚጸልይለት ሌላ አምላክ አለውን? ይጸልያልን? ኢየሱስ አምላክ ከሆነ ለማን ነው ልመናን ያቀረበው? አምላክ ከሆነ ለራሱ ነው ልመናን ያቀረበው ማለት ነው?

አሁንም ጠያቂያችን እስላማዊ መነፅራቸውን ማውለቅ ተስኗቸዋል፡፡ ኢየሱስ የጸለየው ወደ ራሱ ሳይሆን ወደ አብ ነው፡፡ የጸለየበት ምክንያት ደግሞ ፍፁም ሰው ሆኖ ወደ ምድር በመምጣቱ ነው፡፡ ፍፁም ሰው በመሆኑ አብ አምላኩ ተብሏል (2ቆሮንቶስ 1፡3፣ 11፡31፣ ኤፌሶን 1፡3፣ 1ጴጥሮስ 1፡3-5)፡፡ ፍፁም አምላክ በመሆኑ ደግሞ ለአብ የምንሰጠው ክብር ሁሉ ይገባዋል (ዮሐንስ 5፡22-23)፡፡ ኢየሱስ እንደ አምላክነቱ እንኳ ወደ አብ ቢጸልይ የጸሎት ክርስቲያናዊ ትርጓሜ ግልፅ እስከሆነ ድረስ ከአምላካዊ ባህርይ ጋር የሚጣረስበት ሁኔታ የለም፡፡ ጸሎት (ሰላት) በእስልምና አንድ ሰው ለአላህ መገዛቱንና ባርያ መሆኑን የሚገልፅበት ሥርኣት ሲሆን በክርስትና ግን የእግዚአብሔር ልጆች በመሆናችን ከእርሱ ጋር የምንነጋገርበት መንገድ ነው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ወልድ አንድያ የአብ ልጅ በመሆኑ ከአባቱ ጋር ቢነጋገር መለኮትነቱን አይቀንስም፡፡

 

 

ለአሕመዲን ጀበል 303 ጥያቄዎች የተሰጠ መልስ ማውጫ