ክርስቲያኖች “ኢየሱስን አምላክ ነው” እንደሚሉት ቢሆን ኖሮ አምላክን ማን ይልከዋል? አምላክ ሌላ የሚልከው አምላክ አለውን?

 


45. ኢየሱስ በአምላክ አንደተላከ በተደጋጋሚ ተገልጿል፡፡ ለአብነት በማቴዎስ 10:40፣ ማርቆስ 9:37 ፣ ሉቃስ 9:48፣ ሉቃስ 10:16፣ ዮሐንስ ወንጌል 4:34፣ ዮሃንሰ 5:24፣ 5:30 5:36፣ 6:57 7:16-18፣ 7:28-29፣ 7:33፣ 8:14-16፣ 8:18፣ 8:26፣ 8:28-29፣ 8:42፣ 9:4-5፣ 1:41:42፣ 12:44፣ 12:49፣ 13:20፣ 14: 24፣ 15:21፣ 16:5፣ 17:6-9፣ 17:18፣ 18:23 18:25፣ 20:21 እና 13:3 ላይ ተገልጿል፡፡ ክርስቲያኖች “ኢየሱስን አምላክ ነው” እንደሚሉት ቢሆን ኖሮ አምላክን ማን ይልከዋል? አምላክ ሌላ የሚልከው አምላክ አለውን?

በአሕመዲን መረዳት መሠረት አምላክ በአካልም በመለኮትም ነጠላ በመሆኑ ኢየሱስ እንደተላከ መነገሩ አምላክ አለመሆኑን ያሳያል፡፡ ይህ የሥላሴን ፅንሰ ሐሳብ ፍፁም የዘነጋና ከነጠላ አሃዳዊነት ንፅረተ ዓለም አስተሳሰብ አኳያ የቀረበ ጥያቄ በመሆኑ ክርስቲያኖችን የሚመለከት አይደለም፡፡ እኛ የነጠላ አሃዳዊነት አስተምህሮን ስለማንከተልና በአሃዱ ሥሉስ የምናምን ስለሆንን ኢየሱስ በአብ የተላከ መሆኑ ከምንከተለው አስተምህሮ ጋር የሚጣጣም እንጂ የሚጣረስ አይደለም፡፡ የተከበሩት ጠያቂያችን በገዛ ራሳቸው አጥር ውስጥ ተቀምጠው ለክርስቲያናዊ አስተምህሮ ባይተዋር ከሆነ አዕምሯቸው የመነጩ ጥያቄዎችን ከመጠየቃቸው በፊት ክርስትናን ቢያጠኑ ኖሮ የራሳቸውንም ሆነ የአንባቢዎቻቸውን ጊዜ ባላባከኑ ነበር፡፡