ክርስቲያኖች መንፈስ ቅዱስ የሚነዳቸው ከሆነ እንዴት በመለያየት 33,000 ቦታ ከፋፈላቸው?

 


61. ኢንሳይክሎፒድያ ብሪታንካ በ2006 እትሙ ላይ እንደገለፀው የክርስቲያኖች ክፍፍል (የክርስትና አይነት) 33,000 (ሠላሳ ሦስት ሺህ) ደርሷል፡፡ (Encyclopedia britannica 2006 /Ultimate Reference suited D V D/ electronic) “ሁሉም “በመንፈስ ቅዱስ ተነድተናል፣ ተሞልተናል፣ ሰርፆብናል” ወዘተ. ይላሉ፡፡ እውን መንፈስ ቅዱስ የሚያድናቸው ከሆነ እንዴት ክርስቲያኖች በመለያየት 33,000 ቦታ ከፋፈላቸው? የትኛውስ ነው ትክክለኛ ክርስትና?

አሕመዲን ጥያቄ ያለቀባቸው ይመስላል፡፡ ትክክለኛው ክርስትና የመጽሐፍ ቅዱስ ክርስትና ነው፡፡ አንድነት የሚገለጸው በቃሉ ውስጥ ራሱን የገለጠውን አንዱን አምላክ በማምለክ እንጂ በአንድ መዋቅራዊ አስዳደር ስር በመግባትም ሆነ በያንዳንዱ ጥቃቅን ትምህርት ላይ በመስማማት አይደለም፡፡ በክርስትና ውስጥ የሚገኙት አብዛኞቹ ቤተ እምነቶች መሠረታዊ በሆኑ ትምህርቶች ላይ የሚስማሙ ሲሆኑ ልዩነታቸው እጅግ በጣም የጠበበና በአስተዳደራዊ መዋቅር ብቻ የተከፋፈሉ መሆናቸውን መገንዘብ ይቻላል፡፡ መሠረታዊ ከሆነው የመጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ ጋር የማይስማሙት አርዮሳውያንና ሰባልዮሳውያንን የመሳሰሉት ቡድኖች ቃሉን የካዱ ቡድኖች ስለሆኑ ክርስቲያኖች ተብለው ሊጠሩ አይችሉም፡፡ ከዚህ ውጪ ግን ታሪካዊውን ክርስትና የሚወክሉት የሥላሴ አማኞች የዳር ዳር በሆኑ ትምህርቶች እና በአስተዳደራዊ መዋቅር እንዲሁም በአምልኮ ሥርኣት የተለያዩ መሆናቸው የትክክለኛውን ክርስትና ድንበር የሚያስት አይደለም፡፡ ክፍፍሉም “በእኔ ስር ካልገባህ” በማለት በሰይፍ የሚያስገድድ አምባገነን አካል አለመኖሩንና ክርስትና የሰዎችን ነፃ አስተሳሰብ የሚያከብር እምነት መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ አሕመዲን መንፈስ ቅዱስ ክርስቲያኖችን በአንድ የአስተዳደር መዋቅር ስር እንዲጠቀለሉና በያንዳንዱ ጉዳይ ላይ እንዲስማሙ እንደሚያደርጋቸው የተጻፈበትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል እንዲያሳዩን እንጠይቃቸዋለን፡፡ ስለ ክርስትና ያነሱትን ተመሳሳይ ጥያቄ ብንጠይቃቸው ኡስታዙ መልስ እንደሌላቸውና መግቢያ እንደሚጠፋቸው ግልፅ ነው፡፡ እስልምና በውስጡ ለቁጥር የሚያታክቱ ክፍፍሎች እንዳሉበትና እነዚህ አንጃዎች ደም እስከመቃባት ድረስ ጥላቻቸው የከረረ መሆኑ እንዲሁም በከሃዲነት መፈራረጃቸው የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ የገዛ ነቢያቸው ሙሐመድ እንኳ ሕዝባቸው 73 ቦታ እንደሚከፋፈልና ከእነዚህ ቡድኖች መካከል አንዱ ብቻ ገነት እንደሚገባ መተንበያቸውን ትውፊቶች ዘግበዋል፡፡[4] ክፍፍሉ ከዚያ እጅግ በዝቶ ትንቢቱ ሀሰት መሆኑ ቢረጋገጥም ነገር ግን እነዚህን ቡድኖች አንድ ላይ ጨፍልቆ የሌሎችን ህልውና በመካድ 73 ለማድረግ የሚታገሉ ሙስሊም ሊቃውንት አልታጡም፡፡ ሆኖም ግን ከሰባ ሦስቱ ቡድኖች መካከል ገነት የሚገባው የትኛው እንደሆነና እሳቸውም በትክክለኛው ቡድን ውስጥ ስለመገኘታቸው ያላቸውን እርግጠኛነት ቢጠየቁ መልሳቸው መንተባተብ እና መደነጋገር እንደሚሆን ግልፅ ነው፡፡ ታድያ ለእስልምና የማይሰራውን መመዘኛ በክርስትና ላይ መጫን ለምን አስፈለገ? “የራሷ አሮባት…”