“አንዱ እግዚአብሔር” ሲባል ክርስቶስ ይጨምራል ወይንስ አይጨምርም? ከጨመረስ ክርስቶስ ስንተኛ አምላክ ሊሆን ነው?

 


66. በ2ኛ ቆሮንቶስ 5፡18 ላይ “ነገር ግን የሆነው ሁሉ በክርስቶስ ከራሱ ጋር ካስታረቀን የማስታረቅንም አገልግሎት ከሰጠን ከእግዚአብሔር ነው” ይላል፡፡ በክርስትና ጽንሰ ሐሳብ አምላክ “ከሰማየ ሰማያት ወርጄ ከድንግል ማርያም ተወልጄ አድንሃለሁ” ስላለ ወርዶና ተዋርዶ አዳነን ይባላል፡፡ ነገር ግን ጥቅሱ ”በክርስቶስ ከራሱ ጋር ካስታረቀን” ይላል፡፡ አምላክ የሚባለው ክርስቶስ ነው ወይንስ በክርስቶስ አማካኝነት ከራሱ ጋር የስታረቀው ነው? ጥቅሱ ይቀጥልና የማስታረቅም አገልግሎት ከሰጠን ከእግዚአብሔር ነው” ይላል፡፡ “አንዱ እግዚአብሔር” ሲባል ክርስቶስ ይጨምራል ወይንስ አይጨምርም? ከጨመረ እንዴት አንዴም ቢሆን ይህ አልተገለጸም? ከጨመረስ ክርስቶስ ስንተኛ አምላክ ሊሆን ነው?

ጠያቂያችን የጠቀሱት አባባል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኝ ባለመሆኑ ጥብቅና ልንቆምለት አያሻንም፡፡ በተደጋጋሚ እንደገለፅነው አውዱ ግልፅ ካላደረገ በስተቀር አዲስ ኪዳን እግዚአብሔር ሲል የተጠቀሰው አካል አብ ነው፡፡ ሐዋርያው እየተናገረ ያለው አብ በክርስቶስ መስዋዕትነት በኩል ከራሱ ጋር እንዳስታረቀንና የምስራቹን በማስተላለፍም ሌሎችን ወደዚህ እርቅ እንድናመጣ የማስታረቅን አገልግሎት እንደሰጠን ነው፡፡ አሕመዲን የክርስቶስን መስዋዕትነት ክደው ከእግዚአብሔር ጋር ጥለኛ ሆነው ከሚኖሩ ንስሐ በመግባት ቢመለሱና ለእግዚአብሔር አንድያ ልጅ እንደ አምላክነቱ የሚገባውን ክብር ቢሰጡ ይሻላቸዋል፡፡