ኢየሱስ አምላክ ነው ከተባለ እንዴት ከሙሴ ጋር ይነጻጸራል? ዕብራውያን 3:3

 


67. በዕብራውያን 3:3 ላይ ስለ እየሱስ ሲገልጽ “ቤትን የሚያዘጋጀው ከቤቱ ይልቅ የሚበልጥ ክብር እንዳለው መጠን እንዲሁ እርሱ ከሙሴ ይልቅ የሚበልጥ ክብር የተገባው ሆኖ ተቆጥሮአልና፡፡” ይላል፡፡ ታዲያ ኢየሱስ አምላክ ነው ከተባለ እንዴት ከሙሴ ጋር ይነጻጸራል? አምላክ ከማን ጋር ሊነጻጸራል ይችላል?

የዕብራውያን ጸሐፊ ኢየሱስን ከሙሴ ጋር እንዲያነፃፅር ያስገደደው የሕዝቡ የተሳሳተ አመለካከት እንጂ ኢየሱስ የሙሴ ፈጣሪ መሆኑን ዘንግቶ አይደለም፡፡ አሕመዲን አላስተዋሉትም እንጂ በዚሁ ቦታ ላይ ጸሐፊው ኢየሱስ የሙሴ ፈጣሪ መሆኑን እየተናገረ ነው፡፡ ኢየሱስ ከሙሴ ያለው ብልጫ አንድ ሰው የራሱ እጅ ሥራ ከሆነው ቤት ባለው ብልጫ ተመስሏል፡፡ ቤትን የሚሰራ ሰው በእጁ ከሰራው ቤት የበለጠ ክብር የተገባው የሆነበት ምክንያት ቤቱ በእርሱ የተሰራ መሆኑ ነው፡፡ ኢየሱስም ከሙሴ የበለጠ ክብር አለው፤ ምክንያቱም ሙሴ የኢየሱስ ፍጥረት ነውና፡፡ ጸሐፊው ኢየሱስ የአፅናፈ ዓለም ፈጣሪ፣ የሁሉ ጌታ ዘለዓለማዊ አምላክ መሆኑን በምዕራፍ 1 ላይ በመግለፅ ነው የጀመረው፡፡ የሕዝቡን የተሳሳተ አመለካከት ለማረም ኢየሱስን ከፍጥረታት ጋር በማነፃፀር ማቅረቡን ጠያቂያችን ከስህተት ከቆጠሩ የቁርኣን ጸሐፊ አላህን ከፍጥረታት ጋር እያነፃፀረ ማቅረቡን ምን ሊሉት ነው? ለምሳሌ ያህል አላህ ከመሓሪዎች ጋር (ሱራ 7፡155)፣ ከፈራጆች ጋር (ሱራ 12፡80)፣ ከሰዓሊዎች ጋር (ሱራ 23፡14)፣ ከሲሳይ ሰጪዎች ጋር (ሱራ 20፡131፣ 5፡114)፣ ወዘተ. ተነፃፅሯል፡፡