ኢየሱስ ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት በሰማይ ከነበረ ለአምላክ ታዛዥ በመሆኑ ወደ ነበረበት ይመለሳል ወይስ እንደ አዲስ “ከፍ” ይደረጋል? 

 


75. ፍልጵስዩስ 2፡8-9 ላይ “ሰው ሆኖ ተገልጦም፤ ራሱን ዝቅ አደረገ፤ እስከ መሞት ድረስ ታዛዥ ሆነ፡፡ “ስለዚህ እግዚአብሔር እጅግ ከፍ አድርገው፤ ከስምም ሁሉ በላይ የሆነውን ስም ሰጠው” ይላል፡፡ ኢየሱስ ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት በከፍተኛ ደረጃ ሥልጣን ከነበረው ለአምላክ ታዛዥ በመሆኑ ወደ ነበረበት ይመለሳል ወይስ እንደ አዲስ “ከፍ” ይደረጋል? ይሰጠዋል? ጥቅሱ እንደ አዲስ ስለ ማግኘቱ እንጂ “ወደ ነበረበት ይመለሳል” አይልም፡፡ አንዱ የሥላሴ ክፍል ሌላኛውን ያዘዋልን? ከፍ ያደርገዋልን? ስጦታ ይሰጠዋልን?

አንዱ የሥላሴ አካል ሌላኛውን ይልከዋል፣ ያዘዋል እንዲሁም ክብርን ይሰጠወዋል (ዮሐንስ 5፡32፣ 6፡39፣ 16፡7 ሉቃስ 24፡49፣ ዮሐንስ 16፡14፣ 17፡1-2፣ 17:4፣ 17፡5)፡፡ ጠያቂው መጽሐፍ ቅዱስን በወጉ ቢያነቡና የክርስትናን አስተምህሮ ቢያጠኑ ኖሮ ይህንን ጥያቄ ባልጠየቁ ነበር፡፡ ጠያቂው ቆርጠው ያስቀሩት የጥቅሱ ቀዳማይ ክፍል ኢየሱስ በባሕርዩ አምላክ እንደሆነና ከአብ ጋር የነበረውን እኩልነት በመተው ሥጋን እንደለበሰ ይናገራል (ቁ. 6-7)፡፡ ጥቅሱ አብ ኢየሱስን ከፍ ስለማድረጉ እንጂ አሕመዲን እንዳሉት ክብርን እንደ አዲስ ስለማግኘቱ አይናገርም፡፡ “እንደ አዲስ አገኘ” የሚል ቃል በጥቅሱ ውስጥ ባለመኖሩ ያልተጻፈውን እያነበቡ ነው፡፡ ነገር ግን ወደ ቀድሞ ክብሩ መመለሱን የምናውቅበት መንገድ አለ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት በአምላክነት ክብር ይኖር እንደነበር በዚሁ ጥቅስ ውስጥ ተነግሯል፡፡ ከአምላክ በላይ የከበረ ክብር ባለመኖሩ ወደ ቀድሞ ክብሩ ካልተመለሰ በስተቀር እንደ አዲስ ከፍ ተደረገ ማለት ትርጉም የሚሰጥ አይደለም፡፡ ወደ መስቀሉ ከመሄዱ ከጥቂት ጊዜ በፊት ወደ ቀድሞ ክብሩ ይመልሰው ዘንድ አብን ጠይቋል (ዮሐንስ 17:5)፡፡