እግዚአብሔር አንድ ከሆነ፤ ኢየሱስ በአምላክና በሰው መካከል አስታራቂ ከሆነ እንዴት መልሶ አምላክ ይሆናል?

 


77. 1ኛ ጢሞቴዎስ 2:5 ላይ “አንድ እግዚአብሔር አለና፤ ደግሞም በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል አንድ አስታራቂ አለ፤ እርሱም ሰው የሆነው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው” ይላል፡፡ አምላክ ስንት ነው? አንድ፤ እሱም እግዚአብሔር ነው፡፡ ኢየሱስስ? ጥቅሱ ”ደግሞም በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል አንድ አስታራቂ አለ፤” ይላል፡፡ እርሱ ማነው? ከተባለ “ሰው የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ይላል፡፡ ታዲያ እግዚአብሔር አንድ ከሆነ ኢየሱስ ሰው፤ በአምላክና በሰው መካከል አስታራቂ እንደሆነ አምላክ ይሆናል? በምን ስሌት ነው ኢየሱስ የተባለው ሰው አምላክ ልንለው የምንሞክረው?

እስኪ መጀመርያ ሐዋርያው ጳውሎስ ስለ ኢየሱስ አምላክነት ምን እንደተናገረ እንመልከት፡፡ ኢየሱስ ከሁሉ በላይ ሆኖ ለዘለዓለም የተባረከ አምላክ ነው (ሮሜ 9፡5)፤ ታላቁ አምላክ ነው (ቲቶ 2፡13)፤ በባሕርዩ አምላክ ሆኖ ሳለ ክብሩን ጥሎ የመጣ ነው (ፊልጵስዩስ 2፡6)፤ የሁሉ ፈጣሪ ነው (ቆላስይስ 1፡16-17)፤ የመለኮት ሙላት ሁሉ በሰውነቱ ተገልጦ የሚኖር ነው፣ ይህ ማለት ኢየሱስ ፍፁም አምላክ ፍፁም ሰው ነው (ቆላስይስ 2፡9)፤ የሰው ልጆች ሁሉ አንድ ቀን በእግዚአብሔር[11] የፍርድ ዙፋን ፊት ይቆማሉ (ሮሜ 14፡10)፤ የሰው ልጆች በፍርዱ ዙፋን ፊት የሚቆሙት ይህ እግዚአብሔር ኢየሱስ ነው (2ቆሮንቶስ 5፡10)፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ሐዋርያው በብሉይ ኪዳን ለያሕዌ እግዚአብሔር የተነገሩትን ጥቅሶች በመውሰድ ለኢየሱስ መነገራቸውን ተናገሯል፤ ይህንን በማድረግም ኢየሱስ ያሕዌ እግዚአብሔር መሆኑን በግልፅ አሳይቷል፡፡ ተከታዮቹን ጥቅሶች ያነፃፅሩ፡- ሮሜ 10፡13 ከኢዩኤል 2፡32 ጋር፣ 1ቆሮንቶስ 2፡16 ከኢሳይያስ 40፡13 ጋር፣ 2ቆሮንቶስ 10፡17 ከኤርምያስ 9፡24 ጋር፡፡

ስለዚህ ከላይ የተጠቀሱት የሐዋርያው ትምህርቶች ከግምት ውስጥ ሲገቡ ጠያቂያችን በጠቀሱት ጥቅስ ውስጥ ኢየሱስን “ሰው” ብሎ መጥራቱ አምላክ ብቻ አለመሆኑን ነገር ግን ሰውም ጭምር መሆኑን ለማስገንዘብ እንጂ አምላክነቱን አለመቀበሉን የሚያሳይ አይደለም፡፡ በእርግጥ ከእኛ ከሰብዓውያን ወገን ሆኖ ወደ አብ የሚያቀርበን ባሕርዩ ሰብዓዊነቱ በመሆኑ ምክንያት በጥቅሱ ውስጥ አፅንዖት ተሰጥቶታል፡፡ ነገር ግን ሐዋርያው ጳውሎስ ኢየሱስ ሰው መሆኑን ተናገረ እንጂ ሰው ብቻ መሆኑን በመናገር በሌሎች ቦታዎች ላይ ስለ አምላክነቱ የተናገራቸውን ነጥቦች አልተጣረሰም፡፡ በጥቅሱ ውስጥ አንድ እግዚአብሔር ተብሎ የተጠቀሰው ፍጥረትን በመዋጀት ተግባር ውስጥ ልጁን የላከልን እና መስዋዕትነቱን የተቀበለው እግዚአብሔር አብ ነው፡፡[12] ሐዋርያው በሌላ ቦታ ኢየሱስን “አንድ ጌታ” ብሎ መጥራቱ አብ ጌታ አለመሆኑን እንደማያሳይ ሁሉ አብንም አንድ እግዚአብሔር በማለት መጥራቱ ኢየሱስ እግዚአብሔር አለመሆኑን አያሳይም (1ቆሮንቶስ 8፡6፣ ኤፌሶን 4፡5)፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አብ መንፈስ መሆኑ ተነግሮናል (ዮሐንስ 4፡23)፤ ወልድም መንፈስ መሆኑ ተነግሮናል (2ቆሮንቶስ 3፡17)፡፡ ነገር ግን በሌላ ቦታ ላይ አንድ መንፈስ (መንፈስ ቅዱስ) ብቻ መኖሩ ተጽፏል (ኤፌሶን 4፡5)፡፡ “አንድ”፣ “ብቸኛ”፣ “ከሁሉ በላይ”፣ “ታላቁ”፣ ወዘተ. የሚሉት ልዩ መሆንን የሚያመለክቱ አነጋገሮች (Exclusive Languages) ለሦስቱም የሥላሴ አካላት በተናጠል ሊነገሩ የሚችሉ ሲሆኑ ሌላውን የሚያገልሉ አይደሉም፡፡ ለበለጠ ማብራርያ መልስ ቁጥር 5 ይመልከቱ፡፡