ማርያም ልጇ ኢየሱስ የዓለም ፈጠሪ ኃያሉ አምላክ ነዉ ብላ ታምን ነበርን?

 


85. በሉቃስ ወንጌል 2፡41-48 ላይ “ወላጆቹም በያመቱ በፋሲካ በዓል ወደ ኢየሩሳሌም ይወጡ ነበር፡፡ የአሥራ ሁለት ዓመት ልጅ በሆነ ጊዜ፥ እንደ በዓሉ ሥርዓት ወደ ኢየሩሳሌም ወጡ፤ ቀኖቹንም ከፈጸሙ በኋላ፥ ሲመለሱ ብላቴናው ኢየሱስ በኢየሩሳሌም ቀርቶ ነበር፥ ዮሴፍም እናቱም አላወቁም ነበር፡፡ ከመንገደኞች ጋር የነበረ ስለ መሰላቸው የአንድ ቀን መንገድ ሄዱ፥ ከዘመዶቻቸውም ከሚያውቋቸውም ዘንድ ፈለጉት፤ባጡትም ጊዜ እየፈለጉት ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ፡፡ ከሦስት ቀንም በኋላ በመምህራን መካከል ተቀምጦ ሲሰማቸውም ሲጠይቃቸውም በመቅደስ አገኙት፤ የሰሙትም ሁሉ በማስተዋሉና በመልሱ ተገረሙ፡፡ ዮሴፍና ማርያም በቤተ መቅደሱ ባዩትም ጊዜ ተገረሙ፥ እናቱም “ልጄ ሆይ፥ ለምን እንዲህ አደረግህብኝ? እነሆ፥ አባትህና እኔ ተጨነቅን ስንፈልግህ ነበርኮ” አለችው” ይላል፡፡ ማርያም ልጇ ኢየሱስ የዓለም ፈጠሪ ኃያሉ አምላክ ነዉ ብላ ታምን ነበርን? አምላክ መሆኑን ብታዉቅ “አባትህና እኔ ተጨንቀን ስንፈልግህ ነበር እኮ!” ትል ነበርን? አምላክነቱን ካወቀች ምን ያስጨንቃታል? ታዲያ ወላጅ እናቱ ማርያም ልጇ አምላክ ነዉ ብላ ካላመነች ክርስቲያኖች እንዴት አምላክ ሊሉት ቻሉ?

ይህ ንግግር ማርያም ኢየሱስ አምላክ ከመሆኑም በተጨማሪ ፍፁም ሰው መሆኑን ማመኗን እንጂ አምላክ መሆኑን አለማወቋን አያመለክትም፡፡ በልደቱ ወቅት እረኞች የተወለደው ህፃን የዓለም መድኃኒትና ጌታ መሆኑን መላእክት እደነገሯቸው መስክረው ነበር (ሉቃስ 2፡8-20)፡፡ “የሰሙትም ሁሉ እረኞቹ በነገሩአቸው ነገር አደነቁ፤ ማርያም ግን ይህን ነገር ሁሉ በልብዋ እያሰበች ትጠብቀው ነበር፡፡” (ቁ. 19-20)፡፡ ከጥቅሱ እንደምንረዳው ማርያም ስለ ኢየሱስ የምታውቀውን ሁሉ በልቧ ለመያዝ መርጣ እንጂ በብሉይ ኪዳን ትንቢት የተነገረለት መሲህ፣ ጌታ እና የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን ሳታውቅ ቀርታ አይደለም፡፡ መጨነቋ ደግሞ የኢየሱስ ሰብዓዊ ባሕርይ እንደማንኛውም ሰው እንክብካቤ የሚሻ መሆኑን መገንዘቧን ያመለክታል፡፡ ማርያም በወቅቱ የኢየሱስን ማንነት ሙሉ በሙሉ አልተገነዘበችም ቢባል እንኳ የእርሷ አለመገንዘብ ማንነቱን የሚለውጠው እንዴት ሆኖ ነው? ነገር ግን አሕመዲን እንደልማዳቸው ቆርጠው ያስቀሩት የኢየሱስን ምላሽ የያዘው የጥቅሱ ቀጣይ ክፍል እንዲህ ይላል፡- “እርሱም፦ ስለ ምን ፈለጋችሁኝ? በአባቴ ቤት እሆን ዘንድ እንዲገባኝ አላወቃችሁምን? አላቸው፡፡” (ቁ. 49)፡፡ ኢየሱስ በኢየሩሳሌም የሚገኘውን የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ነው “የአባቴ ቤት” በማለት የጠራው፡፡ ነገር ግን ጠያቂያችን አንባቢያኖቻቸው ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን መናገሩን እንዲያውቁ ስላልፈለጉ ለአላማቸው ብቻ የሚመቸውን በመጥቀስ ሌላውን ቆርጠው አስቀርተውታል፡፡