ኢየሱስ አንዱን ባህሪዉን ከአባቱ ሌላዉኛዉን ደግሞ ከእናቱ ከነሳ አባቱ እና እናቱ ምን እና ምን ናቸዉ?

 


86. ክርስቲያኖች እንደሚሉት ኢየሱስ “ሰዋዊ” ባህሪዉን ከማርያም (ከእናቱ) መለኮታዊ ባህሪዉን ደግሞ ከአባቱ (ከአብ) ነስቶ ተወለደ፡፡ ታዲያ አንዱን ባህሪዉን ከአባቱ ሌላዉኛዉን ደግሞ ከእናቱ ከነሳ አባቱ እና እናቱ ምን እና ምን ናቸዉ??

አብ የኢየሱስ አባት የተባለው ኢየሱስ ከማርያም በመወለዱ ምክንያት ባለመሆኑ ይህ ጥያቄ አሕመዲን ክርስቲያናዊውን አስተምህሮ ባለማወቃቸው ምክንያት መደነጋገራቸውን ከማሳየት የዘለለ ቁምነገር የለውም፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ በማርያም ማህፀን አድሮ ከእርሷ ሥጋን በመንሳት ፍፁም ሰው ሆኖ መወለዱን እንጂ ግማሽ ባሕርዩን ከእግዚአብሔር ግማሽ ባሕርዩን ከሰው ነስቶ እንደተወለደ የሚያምን ክርስቲያን የለም፡፡ ቁርኣን ግን ዒሳ ከአላህ የሆነ መንፈስ መሆኑን ይናገራል፡፡ ስለዚህ ዒሳ አንዱን ባሕርዩን ከአላህ ሌላ ባሕርዩን ከመርያም ካገኘ አላህ እና መርየም ምንና ምን ናቸው? በተጨማሪም “የመጽሐፉ እናት” በመባል የምትታወቀው በአላህ ዘንድ የምትገኘው ያቺ ነገር ለአላህ ምኑ እንደሆነች ቢብራራልን? ይህንን የጠየቅንበት ምክንያት አሕመዲን የጠየቁት ጥያቄ ምን ትርጉምና ስሜት እንደሚሰጥ ሙስሊሞች በክርስቲያኖች ቦታ ሆነው እንዲያውቁ ያህል እንጂ የሙስሊሞች መልስ ምን ሊሆን እንደሚችል ጠፍቶን አይደለም፡፡