ኢየሱስ ወደ ሰማይ ከተመለሰ በኋላስ በስጋ እንዳለ ይቆያል ወይስ አስቀድሞ ነበረ በተባለበት ሁኔታ ይመለሳል?

 


91. ክርስቲያኖች “ኢየሱስ አምላክ ነዉ፤ ወደ ምድር የሰዉ ስጋ ለብሶ መጥቷል” ይላሉ፡፡ ወደ ሰማይ ከተመለሰ በኋላስ በስጋ እንዳለ ይቆያል ወይስ አስቀድሞ ነበረ በተባለበት ሁኔታ ይመለሳል?? ኢየሱስ የሰዉ ሥጋ በመተዉ አስቀድሞ ነበረ ወደ ተባለበት አምላካዊ ሁኔታ ይመለሳል? መጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተገለጸዉ ግን ኢየሱስ የሰዉ ሥጋ ለብሶ እስከ መጨረሻዉ መቀጠሉን እንጂ ሰዉነቱን (ሥጋ መልበሱን) እንደሚተዉ አይናገርም!! ታዲያ አንዱ የሥላሴ አባል ኢየሱስ እስከ መጨረሻ ሰዉ ነዉን?

አሕመዲን ይህንን ጥያቄ የጠየቁት ክርስቲያኖች ኢየሱስ ወደ ምድር ሲመጣ ሰው ወደ መሆን እንደተቀየረ ያምናሉ የሚል የተሳሳተ ግንዛቤ ስለያዙ ነው፡፡ ስለዚህ በእሳቸው አመለካከት መሠረት ኢየሱስ ወደ ሰማይ ያረገው ከመለኮትነት ወደ ሰብዕነት የተቀየረውን ባሕርዩን በመተው ባለመሆኑ አሁን በሰማይ አምላክ ሆኖ ሊኖር አይችልም፡፡ ይህንን የተሳሳተ መረዳታቸውን በጥያቄ ቁጥር 25 ላይ አንጸባርቀዋል፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ሰው የሆነው አምላክ መሆኑን በመተው (ከአምላክነት ሰው ወደመሆን ተቀይሮ) ባለመሆኑ በምድር ላይ በነበረበት ጊዜ እንደሆነው ሁሉ በሰማይም ሰውም አምላክም ነው፡፡ እነዚህ ሁለቱ ባሕርያት ሳይከፋፈሉና ሳይደባለቁ በአንዱ የክርስቶስ ማንነት ውስጥ ይኖራሉ፡፡