ክርስቲያኖች ሲፀልዩ ለአብ ነው? ወይስ ለወልድ? ወይስ ለመንፈስ ቅዱስ ነው?

 


5. “አብ፣ ወልድ” እና “መንፈስ ቅዱስ” የሚሉ ቃላቶችን ስናስብ ስለነርሱ ከተገለፀው ጋር ቃላቶቹ በምናባችን የሚፈጥሩት ምስል አለ፡፡ ክርስቲያኖች ሲፀልዩ ለአብ ነው? ወይስ ለወልድ? ወይስ ለመንፈስ ቅዱስ ነው? “አንዱ አምላክ” ብለው ሲለምኑ ማንን ማለታቸው ነው? የሦስቱ አምሳል ነው? ወይስ አንድ አምሳል ነው በዓእምሯቸው የሚመጣው? ወይስ ሦስቱ ተያይዘው አንድ አምሳል ይፈጥራሉ?

ስንጸልይም ሆነ ስለ እግዚአብሔር ስንናገር በአዕምሯችን ውስጥ የምንስላቸው ምስሎች እግዚአብሔርን የሚወክሉ ባለመሆናቸው በነዚያ ምስሎች ላይ በመደገፍ የእግዚአብሔርን መልክ መረዳትም ሆነ ማስረዳት ትክክል አይደለም፡፡ ብዙ ጊዜ አዕምሯችን መንፈሳዊውን ዓለም በቁሳዊው ዓለም መነፅር በማየት የሚፈተን ቢሆንም መጽሐፍ ቅዱስን የሚያውቁ ክርስቲያኖች ሲጸልዩ የሥላሴን አካላት በመከፋፈልም ሆነ በመደባለቅ በአዕምሯቸው ውስጥ መሳል ትክክለኛ መረዳት አለመሆኑን ያውቃሉ፡፡ ክርስቲያኖች “አንድ አምላክ” በማለት ሲጸልዩ በሦስት አካላት የሚኖረውን አንዱን አምላክ ማለታቸው ነው፡፡ ወደ እያንዳንዱ የሥላሴ አካልም ሆነ ወደ አንዱ ግፃዌ መለኮት መጸለይ እንችላለን፡፡ ነገር ግን በአዕምሯችን ውስጥ የሚከሰተው ምስል ምንም ይሁን ምን ትክክለኛውን የእግዚአብሔርን ማንነት የሚወክል አለመሆኑ መታወቅ አለበት፡፡