እውን ኢየሱስ አምላክ ቢሆን ኖሮ ሌላኛውን አምላክ ማስደሰት እንዴት ፈለገ?

 


8. ዮሐንስ 8፡29 “የላከኝ እርሱ ከእኔ ጋር ነው፤ ምን ጊዜም የሚያስደስተውን ስለማደርግ ብቻዬን አልተወኝም” ይላል፡፡ እውን ኢየሱስ አምላክ ቢሆን ኖሮ ሌላኛውን አምላክ ማስደሰት እንዴት ፈለገ?

አንዱ የሥላሴ አካል ሌላውን ለማስደሰት መፈለጉ አምላክ አለመሆኑን የሚያሳየው እንዴት ሆኖ ነው? አምላክ ለመሆን ሌላውን የማስደሰት ፍላጎት ሊኖረው አይገባም ማለት ነውን? የሥላሴ አካላት ተፎካካሪ አማልክት ሳይሆኑ ፍፁም በሆነ አንድነት እና ፍቅር የሚኖሩ የአንዱ ግፃዌ መለኮት አካላት ናቸው፡፡

“ምን ጊዜም የሚያስደስተውን ስለማደርግ ብቻዬን አልተወኝም” የማያስደስተውን ቢያደርግ ብቻውን ይተወዋል ማለት አይደል? አምላክ ብቻውን እንዳይሆን የሌላኛውን አምላክ (አብ) ውዴታ ይፈልጋልን?

ምን ጊዜም አብን የሚያስደስት ነገር ማድረግ የኢየሱስ ባሕርይ በመሆኑ ኢየሱስ ባሕርዩን በመፃረር አብን የማያስደስት ነገር አያደርግም፡፡ አብን የማያስደስት ነገር ማድረግ ባሕርዩ ካልሆነ ደግሞ ንግግሩን በመገልበጥ “የማያስደስተውን ቢያደርግ… ” በማለት መናገር ትርጉም የሚሰጥ አይደለም፡፡ አንድ ሰው “እግዚአብሔር ስለማይዋሽ ተስፋው ይታመናል” ብሎ ቢናገር “አሃ… ከዋሸ ተስፋው አይታመንም ማለት ነው” ብሎ እንደማሰብ ነው፡፡ መዋሸት የእግዚአብሔር ባሕርይ ስላልሆነ ተስፋው ይታመናል ስለዚህ “ቢዋሽ…” ብሎ ማሰብ ትርጉም የሚሰጥ አይደለም፡፡ በተመሳሳይ አብን የማያስደስት ነገር ማድረግ የኢየሱስ ባሕርይ ባለመሆኑ “የማያስደስተውን ቢያደርግ…” ብሎ ማሰብ ራስን ማቄል ነው፡፡