አብ ጌታ ነው ወልድ ጌታ ነው መንፈስ ቅዱስ ጌታ ነው፡ የሥላሴን ምስጢር ማን ይሆን የሚፈታው?

 


14. “አብ አምላክ ነው፤ ወልድም አምላክ ነው፤ መንፈስ ቅዱስም አምላክ ነው፡፡ ግን አንድ አምላክ እንጂ ሦስት አምላክ አይባሉም፡፡ አብ ጌታ ነው ወልድ ጌታ ነው መንፈስ ቅዱስ ጌታ ነው፡፡ ግን አንድ እግዚአብሔር እንጂ ሦስት ጌቶች አይባሉም፡፡ እንደው የሥላሴን ምስጢር ማን ይሆን የሚፈታው?

ውድ አሕመዲን፤ የእግዚአብሔርን ምስጢር መፍታት የሚችል ፍጥረት ከሰው መካከል የሚፈልጉ ከሆነ ተስፋ ይቁረጡ፤ እርሱን የማድረግ አቅምና ችሎታ ያለው ሰው በምድር ላይ የለም! እግዚአብሔር እግዚአብሔር ነው፡፡ እርሱነቱ ከፍጥረት አዕምሮ ያለፈና የላቀ ነው፡፡ እግዚአብሔርን በሰው አዕምሮ ለክቶና መርምሮ ለማወቅ መሞከር ከባቢ አየርን በሞላ በሳንባችን የመሳብ ያህል የማይታሰብ ነው፡፡ የእርስዎ አምላክ አሐዳዊነቱ የሒሳብ ቁጥር ሽርፍራፊ የሆነው ሌጣ አንድ ሲሆን በሰው አዕምሮ የተመጠነ ነው፡፡ ይህ ደግሞ እርስዎ ብዙ ጊዜ ከሚቀስሯት አንድ ጣትዎ ጀምሮ በየትየለሌ ምሳሌዎች ሊገለፅ የሚችል ተራ አንድነት ነው፡፡ አምላካችን ከሰው አዕምሮ ያለፈ፤ አንድነቱና ሦስትነቱ በሰው የሒሳብ ስሌት ሊገለፅ የማይችል፤ ታላቅና ምስጢራዊ አምላክ ነው፡፡