የሥላሴ ፅንስ ሐሳብ ትክክለኛው ገለጻ የትኛው ነው? የይሖዋ ምስክሮች ወይስ የስላሴአዊያን?

 


18. የሥላሴ ፅንስ ሐሳብ ትክክለኛው ገለጻ የትኛው ነው? ከፊል ክርስቲያኖች “ሥላሴ” ከጣኦት አምላኪዎች ወደ ክርስትና የገባና ፈጠራ ነው ብለው ያምናሉ፡፡ (የይሖዋ ምስክሮች/ ጀሆቫ ዊትነስ)፡፡ በሥላሴ ያመኑት አብያተ ክርስቲያናትም ቢሆኑ በትርጉሙ ሳይስማሙ “በሥላሴ ማመን ወሳኝ ነው” ይላሉ፡፡ ታዲያ የትኛው አብያተ ክርስቲያን ይሆን ትክክለኛው?

የይሖዋ ምስክሮች ከክርስትና የሚለዩዋቸው ብዙ አፈንጋጭ አስተምህሮዎች አሏቸው፡፡ ለምሳሌ ያህል፡- ይሖዋ ትልቅ አምላክ ሲሆን ኢየሱስ ትንሽ አምላክ ነው፣ ከሙታን በሥጋ አልተነሳም፣ መልአኩ ሚካኤል ነው ይላሉ፡፡ በተጨማሪም መንፈስ ቅዱስ ኃይል ብቻ ነው፣ ሰው ነፍስ የለውም፣ ወደ ሰማይ የሚሄዱት የመጀመርያዎቹ የይሖዋ ምስክሮች ብቻ ናቸው፣ ወዘተ. በማለት ያምናሉ፡፡ ራሳቸውን እንኳ “ክርስቲያን” በማለት አይጠቅሱም፡፡ ታድያ እንዲህ ዓይነት ቡድኖች ክርስቲያን ሊሰኙ ይችላሉን? አስተምህሮተ ሥላሴ ከቅዱሳት መጻሕፍት እንጂ ከአረማውያን የተገኘ አይደለም፡፡ እግዚአብሔርን በዚህ መልኩ የሚገልፅ ሃይማኖት በዓለም ላይ ክርስትናና ክርስትና ብቻ ነው፡፡ ይልቁኑ አብ ትልቅ አምላክ፣ ልጁ ደግሞ ፍጡርና ትንሽ አምላክ ነው የሚለው የአርዮሳውያን ትምህርት ከአረማውያን የመድብለ አማልክታዊነት አስተሳሰብ የተቀዳ ነው፡፡ የይሖዋ ምስክሮችን የመሳሰሉት ቡድኖች ክርስቲያናዊ ናቸው ከተባለ በሃኢዝምና ሲክህን የመሳሰሉት ከእስልምና የተገኙ ቡድኖችም እስላማዊ ሊሆኑ ነው፡፡ ይህንን የሚቀበል ሙስሊም ግን የለም፡፡