ክርስቲያኖች ስላሴን ለማብራራት ሲሉ ለምን ይዋሻሉ?

 


27. አንድ የክርስቲያን ጸሐፊ ስለ ሥላሴ ሦስት አካላት እንዲህ ይላሉ ፡-“ከሦስቱ አካላት እያንዳንዱ አካል በገጹ ፍጹም ነው፡፡ በሦስቱ አካላት ውስጥም መገዛዛት አንዱም ከአንዱ የሚያንስበት በማዓረገ መለኮት አንዱ ከሁለተኛው በልቆ የሚታይበት አንዱም ለሁለተኛው እንደ መልዕክተኛ አድርጎ በሥልጣኑ የሚያዝበት ሁኔታ የለም፡፡ ነገር ግን በአንዱ መለኮት በአንዱ አገዛዝ በአንድ ክብር ሁሉን የሚችል የብርሃን ልዕልና አንድ ናቸው” (መሠረት ሰብሐት ለአብ፣ ሥላሴ በተዋህዶ፣ አዲስ አበባ፣ 1988 ዓ.ም፣ ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት ታተመ፣ ገጽ 284)፡፡

 

መጽሐፍ ቅዱስ የክርስቶስም ራስ እግዚአብሔር እንደሆነ ሲገልጽ እንዲህ ይላል ፡-“ነገር ግን የወንድ ሁሉ ራስ ክርስቶስ፣ የሴትም ራስ ወንድ፣ የክርስቶስም ራስ እግዚአብሔር እንደሆነ ልታውቁ እወዳለሁ” 1ኛ (ቆሮንቶስ 11፡3)፡፡

ታድያ እግዚአብሔር የክርስቶስ (ወልድ) ራስ እንደሆነ እየተገለጸ ለምን ይዋሻል? በተጨማሪ በዚሁ መጽሐፍ ውስጥ የሚያገኟቸው በርካታ ጥቅሶች እግዚአብሔር የኢየሱስ (ወልድ) የበላይ እንደሆነ ያስረዳል፡፡ ታድያ እውነታውን መቃረን ለምን አስፈለገ?

በሥላሴ አካላት መካከል ስላለው እኩልነት ስንናገር በመለኮታዊ ባሕርይ (Essence) ማለታችን እንጂ በሥራ ድርሻ (Function) ማለታችን አይደለም፡፡ ከአገራችን ታላላቅ የሥነ መለኮት ሊቃውንት መካከል አንዱ የነበሩት መሠረት ስብሐት ለአብም ከላይ የተጠቀሰውን ሐሳብ ከቅዱስ ሳዊሮስ ዘአንጾኪያ ጠቅሰው የጻፉት ይህ አስተምህሮ ጠፍቷቸው ሳይሆን በሥላሴ አካላት መካከል ፍቅር እንጂ በሥልጣንና በኃይል መገዛዛት አለመኖሩን አፅንዖት ለመስጠት ነው፡፡ አንዱ የሥላሴ አካል ለሌላው የሚገዛውና የሚላከው በኃይል፣ በሥልጣን ወይም በመለኮታዊ ባሕርይ ከሌላው ያነሰ በመሆኑ ምክንያት ሳይሆን ፍፁም በሆነ ፍቅር የሚኖሩ በመሆናቸው ነው፡፡