መንፈስ በሚለው ቦታ እግዚአብሔርን ተክተን ስናነብ ብዙ እግዚአብሔሮች አይኖሩም?

 


30. “ሐዋርያው” የሚባለው ጳውሎስ እንዲህ ብሏል፡- “ከእግዚአብሔር የሆነውን መንፈስ እንጂ የዓለምን መንፈስ አልተቀበልንምና፤ ይህም እግዚአብሔር በነፃ የሰጠን እናውቅ ዘንድ ነው” (1ኛ ቆሮንቶስ 2፡12)፡፡ እንደ ሥላሴ አስተምህሮት መንፈሱም (መንፈስ ቅዱስም) እግዚአብሔር ነው፡፡ እንደዚህ ጥቅስ “ከእግዚአብሔር የሆነውን መንፈስ” ሲል «መንፈስ» በሚለው ምትክ «እግዚአብሔር» የሚለውን ከተካን (አንድ ናቸው ስለተባለ) ከእግዚአብሔር የሆነውን እግዚአብሔር የሚል ይሆናል፡፡ ታድያ ስንት እግዚአብሔር ነው ያለው?

መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል (የሐዋርያት ሥራ 5፡3-4)፡፡ መንፈስ ቅዱስ “እግዚአብሔር” የተባለው ከአብ እና ከወልድ ጋር የአንዱ መለኮት ተካፋይ በመሆኑ እንጂ ከእነርሱ የተነጠለ ህልውና ስላለው አይደለም፡፡ የሥላሴ አካላት ልዩ (Distinct) እንጂ የተለያዩ (Separated) አይደሉም፤ ስለሆነም ሐዋርያው ከእግዚአብሔር አብ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስን መቀበላችንን መናገሩ ስለ ሁለት የአንዱ የእግዚአብሔር አካላት እየተናገረ መሆኑን እንጂ ስለ ሁለት እግዚአብሔሮች እየተናገረ መሆኑን አያሳይም፡፡