ኢየሱስ አምላክ ከሆነ ለምድነው “ከራሴ ምንም ላደርግ አይቻለኝም” ያለው?

 


  1. ኢየሱስ ለምድነው በዮሐንስ 8፡28 ላይ “ከራሴ ምንም ላደርግ አይቻለኝም” ያለው? ታዲያ እንደሚሉት ኢየሱስ አምላክ ሆኖ ከራሱ ምንም ማድረግ የማይችል ከሆነ ምንም ማድረግ የማይችል አምላክ አለ ልንል ነውን? ወይሥ የሰው ስጋ ስለለበሰ? ታድያ በመጽሐፍ ቅዱሥ አንድም ሥፍራ “ኢየሱስ ካረገም በኃላ ሥጋውን ይተዋል” አይልም፡፡ ታዲያ እስከ መጨረሻ ምንም ማድረግ ለማይችለው ኢየሱስ ፍፁማዊ አምላክነትን ልንሰጥ እንዴት ይቻለናል?

ክርስቲያኖች ሦስቱም የሥላሴ አካላት ተነጣጥለው ይሠራሉ የሚል እምነት ስለሌላቸው ኢየሱስ ከአብ ተነጥሎ ከራሱ ምንም ማድረግ አለመቻሉን ከመለኮታዊ ባሕርዩ አኳያ ቢናገር እንኳ የሥላሴን አስተምህሮ የሚያረጋግጥ እንጂ የሚቃወም አይደለም፡፡ በተጨማሪም ኢየሱስ በምድር ላይ በነበረበት ጊዜ አምላክነቱን ባያቆምም ነገር ግን አምላካዊ ሥልጣኑን በመተው እንደ አገልጋይ ተመላልሷል (ፊልጵስዩስ 2፡5-11)፡፡ ስለዚህ ከራሱ አንዳች ማድረግ እንደማይቻለው መናገሩ ሰብዓዊ ባሕርዩን የሚያመለክት ነው፡፡ የትንሣኤ ሥጋውን ይዞ ወደ ሰማይ ቢያርግም ነገር ግን ወደ ቀደመው መለኮታዊ ክብሩ ስለተመለሰ አሁን በሥራ ላይ የሚገኘው መለኮታዊ ባሕርዩ እንጂ ሰብዓዊ ባሕርዩ ባለመሆኑ የጠያቂው ሙግት ውድቅ ነው፡፡