ኢየሱስ “መንገዱ እኔ ነኝ” አለ እንጂ “መድረሻ ነኝ” መች አለ?

 


  1. ዮሐንስ 14፡6 “ኢየሱስም እንዲህ አለው፦ “መንገዱ እኔ ነኝ፤ እውነትና ሕይወትም እኔው ነኝ፤ በእኔ በኩል ካልሆነ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም” ይለል፡፡ አንዳንድ ክርስቲያኖች ይህን ጥቅስ ለኢየሱስ “አምላክነት” መከራከሪያ አድርገው ያቀርባሉ፡፡ ኢየሱስ “መንገዱ እኔ ነኝ” አለ እንጂ “መድረሻ ነኝ” መች አለ? መንገድ አድረሽ ነው እንጂ መድረሻ አይደለም፡፡ ነቢያት ሁሉ ያስተምራሉ፤ ወደ አምላክ ጥሪ ያደርገሉ፡፡ ማንም ገነት ለመግባት የግድ የነቢያቱን መንገድ መከተል አለበት፡፡ ወደ አምላክ የሚያደርሱ መንገድ ናቸው፡፡ ታድያ ኢየሱስ “አምላክ ነኝ” መች አለ? ኢየሱስ በዘመኑ ብቸኛ የአምላክ መንገድ ነው፡፡ ያለርሱ መንገድነት በቀር (እርሱን ከመከተል ውጭ) ማንም ወደ አምላክ አይቀርብም፡፡ ኢየሱስ በግልጽ “በእኔ በኩል ካልሆነ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም” ብሏል፡፡ ታድያ ክርስቲያኖች ምነው ይህን መመርመር አቃታቸው?

ይህ ጥቅስ ኢየሱስ አምላክ መሆኑን እንደሚያሳይ ክርስቲያኖች የሚናገሩበት ምክንያት ፍጡር “እውነት እና ሕይወት” (The Truth and the Life) ተብሎ ሊጠራ እንደማይችል ስለሚያምኑ ነው፡፡ አሕመዲን እነዚህን ሁለቱን ነጥቦች ወደ ጎን በማድረግ “መንገድ” በሚለው ላይ ብቻ ማተኮራቸውን ልብ በሉ፡፡ ይህንን ያደረጉበት ምክንያት ደግሞ እነዚህ ቃላት በገዛ ሃይማኖታቸው መስፈርት መሠረት ኢየሱስ አምላክ መሆኑን ስለሚያረጋግጡ ነው፡፡ ለማንም ፍጡር ሊሰጡ ከማይችሉ 99ኙ የአላህ ስሞች መካከል አል-ሐቅ (እውነት) እና አል-ሐዩን (ህያው የሆነው) የሚሉት ይገኙበታል፡፡ በእስልምና እምነት መሠረት ከእነዚህ ስሞች መካከል አንዱን እንኳ በቁሙ ለፍጡር መስጠት ያንን ፍጡር አምላክ ማድረግ በመሆኑ ይቅርታ የሌለው “የሽርክ” ኃጢአት ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ቦታ ከተጠቀማቸው ማዕረጋት መካከል ሁለቱ በእስልምና ሃይማኖት መሠረት እንኳ አምላክነቱን የሚያሳዩ ሆነው ሳሉ አሕመዲን ሁለቱን አይተው እንዳላየ በመሆን አንዱን ብቻ ነጥለው ማውጣታቸው ለእውነት ያደረ ህሊና እንደሌላቸውና አወናባጅ መሆናቸውን ያመለክታል፡፡ ሁለቱ ማዕረጋት አምላክ መሆኑን ስለሚያሳዩ ኢየሱስ “መንገድ” ተብሎ መጠራቱ ፍጡር መሆኑን አያሳይም፡፡ ይልቁኑ ሰው መዳንና አብን ማወቅ የሚችለው አንድያ ልጁ በሆነው እና በመለኮት ከእርሱ ጋር በተካከለው በእርሱ በኩል ብቻ መሆኑን ያሳያል፡፡ ኢየሱስ ማንም ሰው በእርሱ በኩል ካልሆነ በስተቀር ወደ አብ መምጣት እንደማይችል ተናገረ እንጂ ይህ ሥልጣኑ በጊዜ የተገደበ መሆኑን ስላልተናገረ የጠያቂው ትንታኔ ከገዛ ኪሳቸው የተገኘ እንጂ ከመጽሐፍ ቅዱስ የተገኘ አይደለም፡፡ እውነት መንገድና ሕይወት እንደሆነ የተናገረ ነቢይ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥም ሆነ በእስላማዊ ቅዱሳት መጻሕፍት ስለመኖሩ የተጻፈ አንድ ማስረጃ ማቅረብ ይችሉ እንደሆን እንጠይቃቸዋለን፡፡