አብ ዓለም ከመፈጠሩ በፊት አንድ ልጅ (ወልድን) ወልዶ ከነበረ ለምን የብሉይ ኪዳን ነቢያት አላወቁትም?

 


26. እውን አብ ዓለም ከመፈጠሩ በፊት አንድ ልጅ (ወልድን) ወልዶ ከነበረ ይህን የሚመስል “ድንቅ” ነገር እንዴት አንዱም ነብይ እንኳን ሳያስተምር አልያም አንዴም ቢሆን ሳይናገር አለፈ? ለምንስ ነው በብሉይ ኪዳን ይህንን የሚመለከት አስተምህሮ ያልተገኘው?

ጠያቂው ከተናገሩት በተፃራሪ እግዚአብሔር ልጅ እንዳለው በዘመነ ብሉይ በተደጋጋሚ ተጠቅሷል፡- “ወደ ሰማይ የወጣ የወረደስ ማን ነው? ነፋስንስ በእጁ የጨበጠ ማን ነው? ውኃንስ በልብሱ የቋጠረ ማን ነው? የምድርን ዳርቻ ሁሉ ያጸና ማን ነው? ይህን ታውቅ እንደ ሆንህ፥ ስሙ ማን የልጁስ ስም ማን ነው?” (ምሳሌ 30፡4)፡፡

“አሕዛብ ለምን ያጕረመርማሉ? ወገኖችስ ለምን ከንቱን ይናገራሉ? የምድር ነገሥታት ተነሡ፥ አለቆችም በእግዚአብሔርና በመሢሑ ላይ እንዲህ ሲሉ ተማከሩ፡፡ ማሰርያቸውን እንበጥስ፥ ገመዳቸውንም ከእኛ እንጣል… ትእዛዙን እናገራለሁ፤ እግዚአብሔር አለኝ፦ አንተ ልጄ ነህ፥ እኔ ዛሬ ወለድሁህ…” (መዝሙር 2፡1-12 ከዕብራውያን 1፡5 ጋር ያነፃፅሩ)፡፡

እነዚህና ሌሎች መሲሃዊ ጥቅሶች ስለ እግዚአብሔር ልጅ ይናገራሉ፡፡ እነዚህ ጥቅሶች በብሉይ ኪዳን ውስጥ እንደሌሉ ቢታሰብ እንኳ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ ስለመሆኑ ክርስትና የሚያስተምረው ትምህርት በአዲስ ኪዳን ዘመን ይፋ መሆኑን እንጂ ስህተት መሆኑን አያሳይም፡፡

ብሉይ ኪዳን ስለ እግዚአብሔር አንድያ ልጅ ከመናገሩም በተጨማሪ የመንፈስ ልጆች እንደሚወልድ ይናገራል፡፡ ይህ “መውለድ” ግን መንፈሳዊ ትርጉም ያላቸውን አባባሎች በሥጋዊ አስተሳሰብ ለሚተረጉሙት ለአሕመዲንና ለመሰሎቻቸው ላይገባቸው ይችላል፡- “እግዚአብሔር ተናግሮአልና ሰማያት ስሙ፥ ምድርም አድምጪ፤ ልጆችን ወለድሁ አሳደግሁም…” (ኢሳይያስ 1፡2)፡፡