አምለክ ከእንቅልፍ እንዴት ይነቃል? ኃያሉን አምላክ በዚህ መልኩ መግለጽ ተገቢ ነውን?

 


5. መዝሙር 78፡65 “ጌታም ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሳ፤ የወይን ጠጅ ስካር እንደ በረደለት ጀግናም ብድግ አለ” ይላል፡፡ አምለክ ከእንቅልፍ እንዴት ይነቃል? ኃያሉን አምላክ በዚህ መልኩ መግለጽ ተገቢ ነውን?

እግዚአብሔር ባልተጠበቀ ሰዓት ድንገት ክፉዎች ላይ እርምጃ መውሰወዱን ለማመልከት የተነገረ ዘይቤያዊ ገለፃ በመሆኑ በቀጥታ ካልተረጎምነውና ዘይቤያዊ አነጋገር መሆኑን ከተገነዘብን ንግግሩ ችግር የለበትም፡፡ “እግዚአብሔርም ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ፥ የወይን ስካር እንደ ተወው እንደ ኃያልም ሰው፤ ጠላቶቹንም በኋላቸው መታ፤ የዘለዓለምን ኀሣር ሰጣቸው፡፡” (ቁ.65-66)፡፡

ጠያቂው ዘይቤያዊ ንግግሮችን በቀጥታ የሚተረጉሙ ከሆነ ተከታዮቹን የቁርኣን ጥቅሶች ምን ሊሏቸው ነው?፡- “እናንተ ያመናችሁ ሆይ! አላህን (ሃይማኖቱን) ብትረዱ፤ ይረዳችኋል፡፡” (ሱራ 47፡7) – አላህ የኛን እርዳታ የሚሻ ደካማ አምላክ ነው ማለት ነውን? በቅንፍ የተቀመጠው (ሃይማኖቱን) የሚለው በተርጓሚዎቹ የተጨመረ እንጂ በአረብኛው ንባብ ውስጥ አይገኝም፡፡

“ለአላህ መልካም ብድርን ብታበድሩ (ምንዳውን) ለናንተ ይደራርበዋል፤ ለናንተም ይምራል፤ አላህም አመስጋኝ ታጋሽ ነው፡፡” (ሱራ 64፡17) – አላህ ኃጢአትን የሚምረው ለአበዳሪዎቹ ነው ማለት ነውን? የሚበደር አምላክ ምን ዓይነት አምላክ ነው? እነዚህን ጥያቄዎች የጠየቅነው የአሕመዲን ዕይታ ምን ያህል ደካማ እንደሆነ ለማሳየት ያህል ነው፡፡ እነዚህ የቁርኣን ጥቅሶች ዘይቤያዊ በሆነ መንገድ የሚተረጎሙ ከሆነ ችግር የለባቸውም፡፡ በቀጥታ ከተተረጎሙ ግን በአላህ ባሕርይ ላይ ከባድ ጥያቄዎችን ያስከትላሉ፡፡ ጠያቂው የጠቀሷቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶችም ልክ እንደእነዚህ የቁርኣን ጥቅሶች ሁሉ ዘይቤያዊ በመሆናቸው በቀጥታ መተርጎም የለባቸውም፡፡