ኢየሱስ በሥላሴ ካመነና የሥላሴ አባልም ከሆነ የዘለዓለም ሕይወትን ለማግኘት ምን ማድረግ እንደሚገባ ሲጠየቅ ለምን “ትዕዛዝን ጠብቅ” ሲል መለሰ?

 


34. በማቴዎስ 19:16-17 እንደተዘገበው ኢየሱስ የዘለዓለም ሕይወትን ለማግኘት ምን ማድረግ እንደሚገባ ሲጠየቅ “ትዕዛዝን ጠብቅ” ሲል መልሷል፡፡ የመጀመሪያው ትዕዛዝ በአምላክ አንድነት ማመን ነው (ዘፀአት 20:3)፡፡ ታዲያ ኢየሱስ በሥላሴ ካመነና የሥላሴ አባልም ከሆነ ለምን እንዲህ ሲል መለሰ? ቤተክርስቲያን የሚዳነው በሥላሴ በማመን እና ኢየሱስ ለሰው ልጆች ኃጢአት ቤዛ መሆኑን በማመን እንደሆነ ታስተምራለች፡፡ ታዲያ እውነተኛው አስተምህሮት የትኛው ነው? የኢየሱስ ወይንስ የቤተክርስቲያን?

አሕመዲን ክፍሉን እስከ መጨረሻው ድረስ ቢያነቡት ኖሮ የኢየሱስን መልእክት በትክክል በተረዱ ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትእዛዛትን ቢጠብቅ እንደሚድን ለባለጠጋው ከነገረው በኋላ ባለጠጋው ትእዛዛትን ሁሉ እንደጠበቀ ነገረው፡፡ ኢየሱስ ግን “ይህ ይበቃል፣ በቃ ድነሃል” አላለውም ነገር ግን ያለውን ሁሉ ሽጦ ለድሆች በመስጠት እንዲከተለው ነገረው፡፡ ይህም ማለት አንድ ሰው መዳን ከፈለገ ሕግን ሁሉ እንኳ የጠበቀ ቢሆን ሙሉ በሙሉ ሕይወቱን ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በመስጠት ሊከተለው ይገባል ማለት ነው፡፡ አሕመዲን በአምላክ አንድነት ማመን ማለት የነጠላ አሃዳዊነት እምነት ተከታይ መሆን ማለት እንደሆነ በማስመሰል ደግመው ደጋግመው ይናገራሉ፡፡ እስከ አሁን ድረስ እንደተመለከትነው ይህንን እምነታቸውን የሚደግፍ እና ሥላሴያዊ አሃዳዊነትን (Trinitarian Monotheism) የሚቃወም ምንም ዓይነት የቅዱሳት መጻሕፍት ማስረጃ ሊያቀርቡ አልቻሉም፡፡

 

 

ለአሕመዲን ጀበል 303 ጥያቄዎች የተሰጠ መልስ ማውጫ