አምላክ እግዛብሔር ነው ወይስ ከእግዚአብሔር ቀኝ የቆመው ኢየሱስ ነው? ወይንስ ሁለቱም?

 


46. በሐዋሪያት ሥራ 7:55 ላይ «እስጢፋኖስ ግን በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ ወደ ሰማይ ትኩር ብሎ ሲመለከት የእግዚአብሔርን ክብር እንዲሁም ኢየሱስ በእግዚአብሔር ቀኝ ቆሞ አየና “እነሆ ሰማያት ተከፍተው የሰው ልጅም በእግዚአብሔር ቀኝ ቆሞ አያለሁ» አለ ይላል፡፡ እንዲሁም በማርቆስ ወንጌል 16:19 ላይ «ጌታ ኢየሱስ ይህን ከተናገራቸው በኋላ ወደሰማይ ዐረገ በእግዚአብሔርም ቀኝ ተቀመጠ፡፡» ይላል፡፡ አምላክ እግዛብሔር ነው ወይስ ከእግዚአብሔር ቀኝ የቆመው ኢየሱስ ነው? ወይንስ ሁለቱም? ታድያ ምኑ ላይ ነው “እግዚአብሔር አንድ ነው” የሚባለው? “አምላክ (እግዚአብሔር)” ስንል ኢየሱስን ይጨምራል ወይስ አይጨምርም? እግዚአቤሔር በዙፋን ላይ ያለው ነው ወይስ ከቀኙ የቆመው ኢየሱስ? አንድሁም በክርስትና “መንፈስ ቅዱስ አምላክ ነው”፡፡ ታድያ እስጢፋኖስ የተሞላው በአምላክ ነውን ? እስጢፋኖስ ኢየሱስ ካረገ በኋላ ከእግዚአብሔር ጎን ሲቆም “የሰው ልጅ” ሲል ጠራው ታድያ ካረገም በኋላ ሰው መሆኑን ሊነግረን ፈልጎ አይደል?

አሁንም ይህ ጥያቄ በተደጋጋሚ ከገለፅነው የአሕመዲንን ዕይታ ከጋረደው አስተምህሮ የመነጨ ነው፡፡ እግዚአብሔር አሃዱ ሥሉስ በመሆኑ በዚህ ቦታ ላይ የሥላሴ አካላት፣ ማለትም አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ በሦስት አካላት መገለፃቸው ታሪካዊው የክርስትና ነገረ መለኮት (Historical Christian Theology) መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡ እስጢፋኖስ ኢየሱስን “የሰው ልጅ” ብሎ መጥራቱ ኢየሱስ የትንሣኤውን ሥጋ ይዞ ማረጉን የሚገልፅ በመሆኑ አሁንም ጥቅሱ ክርስቲያናዊውን አስተምህሮ የሚደግፍ እንጂ የሚቃወም አይደለም፡፡ ነገር ግን “የሰው ልጅ” የሚለው ማዕርግ ከሰውነቱ ባለፈ ኢየሱስ በሥጋ የተገለጠ አምላክ መሆኑን ያሳያል (ዳንኤል 7፡13-14)፡፡ ለዚህ ነው በዚህ ቦታ ላይ እስጢፋኖስ የወጋሪዎቹን ኃጢአት ይቅር እንዲል ነፍሱንም እንዲቀበል ወደ ኢየሱስ የጸለየው (የሐዋርያት ሥራ 7፡59-60)፡፡

የኢየሱስን አምላክነት ያልተቀበለ ሰው እንዲህ ዓይነት ጸሎት ሊያቀርብ አይችልም፡፡ የትኛውም ሙስሊም “ጌታ ሙሐመድ ሆይ ነፍሴን ተቀበል” ወይም “ጌታ ሆይ ይህን ኃጢአት አትቁጠርባቸው” በማለት ወደ ሙሐመድ አይጸልይም፡፡ ምክንያቱም ይህ ሙሐመድን አምላክ ማድረግ ነውና፡፡ የኢየሱስን አምላክነት በመመስከር የመጨረሻ እስትንፋሱን የተነፈሰውን የእስጢፋኖስን ንግግር በማጣመም የኢየሱስን አምላክነት እንደካደ በማስመሰል መናገር ህሊና ቢስነት ነው፡፡

ጠያቂያችን ክርስቲያኖች በእግዚአብሔር አንድነት የሚያምኑ መሆናቸውን ነገር ግን አንዱ አምላክ ሦስት የማይነጣጠሉና የማይደባለቁ አካላት እንዳሉት፣ ወልድ በሥጋ እንደተነሳና እንዳረገ ማመናቸውን ቢያውቁ ኖሮ ይህንን ጥያቄ ባላቀረቡ ነበር፡፡ አለማወቅ ኃጢአት አይደለም፡፡ ነገር ግን የማያውቁትን ለማወቅ ማንበብና መማር እንጂ በቁንፅል እውቀት የሞነጫጨሩትን በመጽሐፍ በማሳተም የሌላውን ሃይማኖት ማብጠልጠል አግባብ አይደለም፡፡