አምላክ ነው የሚባለው ኢየሱስ ከመላእክት ያንስ ነበርን? ዕብ 1፡4

 


54. ዕብራውያን 1:4 «ስለዚህ የወረሰው ስም ከመላዕክት ስም እንደሚበልጥ ሁሉ እርሱም ከመላዕክት እጅግ የላቀ ሆኗል፡፡» ይላል፡፡ “ኢየሰስ ከመላዕክት እጅግ የላቀ ሆኗል“ ሲል “የላቀ ነው” ከሚለው ጋር እጅጉን ይለያያል ፡፡ “ሆኗል” ሲል መጀመሪያ አልሆነም በኋላ ላይ ሆነ የሚል ትርጉም ያሲዘናል፡፡ ታድያ አምላክ ነው የሚባለው ኢየሱስ ከመላእክት ያንስ ነበርን?

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ወደ ምድር በመምጣቱ ምክንያት በሰውነቱ ከመላእክት በጥቂት አንሶ እንደነበር በዕብራውያን መልዕክት ውስጥ ተጽፏል፡፡ አሕመዲን የዕብራውያንን መልዕክት እየቆራረጡ ከሚያነቡ አንድ ምዕራፍ ጨምረው ቢያነቡ ኖሮ ይህንን ጥቅስ ባገኙ ነበር፡-

“ነገር ግን በእግዚአብሔር ጸጋ ስለ ሰው ሁሉ ሞትን ይቀምስ ዘንድ፥ ከመላእክት ይልቅ በጥቂት አንሶ የነበረውን ኢየሱስን ከሞት መከራ የተነሣ የክብርና የምስጋናን ዘውድ ተጭኖ እናየዋለን” (ዕብራውያን 2፡7-9)፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመላእክት ተፈጥሮ ያነሰውን የሰውን ተፈጥሮ ስለወሰደ ለጥቂት ጊዜ ከመላእክት አንሶ ቢታይም አሁን ግን እንደ እግዚአብሔር ወልድ ወደነበረው የቀድሞ ክብሩ ስለተመለሰ ከመላእክት እጅግ ልቆ ይገኛል፡፡ ለተጨማሪ ማብራርያ መልስ ቁጥር 21 እና ቁጥር 30ን ይመልከቱ፡፡