ዳዊት “የአምላክ ልጅ” ከተባለ የኢየሱስ ልጅነት ጉዳይ ከሱ በምን ይለያል?

 


63. በመዝሙረ 89፡27 ዳዊት “የአምላክ ልጅ” ተብሏል፡፡ እንዲሁም ሰለሞን (1ኛ ዜና መዋዕል 22፡10)፣ እስራኤል (ዘፀአት 4:22፣ በመዝሙር 82፡6)፣ ኤፍሬም (ኤርምያስ 31:9)፣ በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ (ሮሜ 8:14)፣ ሰላም አስፋኞች (በማቴዎስ 5፡9)፣ በክርስቶስ ኢየሱስ ያመኑ (ገላትያ 3:13)፣አዳም (ሉቃስ 3:38) እና ኢየሱስን የተቀበሉት ሁሉ (ዮሐንስ 1፡10) “የአምላክ ልጅ” ተብለዋል፡፡ የኢየሱስ “የአምላክ ልጅ” መባል ከሌሎች የተለየና የሥጋ (እውነተኛ) ከሆነ ለምን ኢየሱስም ሆነ አምላክ ለይተው ይህን አልገለፁም? ያለ ማስረጃ በራሳችን ለምን እንለያለን፡፡

ጠያቂያችን “የኢየሱስ የአምላክ ልጅነት የተለየና የሥጋ (እውነተኛ) ከሆነ” ሲሉ በቁርኣን ውስጥ የሚገኘውን ስሁት መረዳት እያንፀባረቁ ነው፡፡ የቁርኣን ደራሲ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ መባሉን እግዚአብሔር ሚስት አግብቶ ልጅ እንደወለደ የተነገረ በማስመሰል ይተረጉማል፡፡ አላህ ሚስት ስለሌለችው ልጅ ሊኖረው እንደማይችል በመናገርም የአላህን ሁሉን ቻይነት ውድቅ ያደርጋል (ሱራ 6፡101)፡፡ ጠያቂያችን መጽሐፍ ቅዱስን በጥቂቱም ቢሆን የማንበብ ዕድል በማግኘታቸው ምክንያ ክርስቲያኖች እንደርሱ እደማያምኑ ከቁርኣን ጸሐፊ በተሻለ ሁኔታ ማወቅ ነበረባቸው፡፡ “አባት” እና “ልጅ” የሚሉት ቃላት በሁለቱ የሥላሴ አካላት መካከል የሚገኘውን ዘለዓለማዊ ቁርኝት የሚገልፁ ቃላት እንጂ ቀጥተኛ ትርጉም ያላቸው አይደሉም፡፡ ግብፃውያን “የአባይ ልጆች” ተብለው መጠራታቸው ከወንዙ ጋር ያላቸውን ቁርኝት የሚገልፅ እንጂ አባይ ሚስት አግብቶ ልጅ ወለደ ተብሎ ሊተረጎም እንደማይችል ሁሉ ለሁለቱ የሥላሴ አካላት የተሰጡት እነዚህ መጠርያዎችም ቁርኝታቸውን የሚገልፁ እንጂ ቃል በቃል ሊተረጎሙ የሚገባቸው አይደሉም፡፡ እግዚአብሔር አብም ሆነ ራሱ ኢየሱስ ልጅነቱ የተለየና በመካከላቸው ቀጥተኛ ቁርኝት መኖሩን የሚገልፅ መሆኑን ግልፅ አድርገዋል፡፡ አብ በኢየሱስ የአገልግሎት ዘመን ቢያንስ ሁለት ጊዜ የሚወደው በእርሱም ደስ የሚለው ልጁ መሆኑን መስክሯል (ማቴዎስ 3፡17፣ 17፡5፣ ማርቆስ 1፡10፣ 9፡17፣ ሉቃስ 3፡22፣ 9፡35)፡፡ እግዚአብሔር አብ በእንዲህ ያለ ሁኔታ የመሰከረለት አንድም ፍጥረት የለም፡፡ መላእክትና አማኞች ሁሉ የእግዚአብሔር ልጆች ቢሆኑም የኢየሱስ ልጅነት የተለየ መሆኑንና አብ ለማንም አባትነቱን ባልገለፀበት የተለየ መንገድ ለኢየሱስ መናገሩን መጽሐፍ ቅዱስ በግልፅ አስፍሮልናል (ዕብራውያን 1፡5፣ ሉቃስ 20፡13)፡፡ ጌታችን ራሱን “አንድያ የእግዚአብሔር ልጅ (ሞኖጌኔስ)” በማለት ነው የገለፀው (ዮሐንስ 1፡13)፡፡ ይህ ደግሞ እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ በሆነበት መንገድ ማንም አለመሆኑንና የእርሱ ልጅነት የተለየ መሆኑን ያሳያል፡፡ ከአብ ወጥቶ ወደ ዓለም መምጣቱንም በመናገር የአብ ባሕርይ ተካፋይ መሆኑን በግልፅ ተናግሯል (ዮሐንስ 8፡42፣ 16:28)፡፡ ሐዋርያው ዮሐንስ አይሁድ ኢየሱስን ለምን ሊገድሉት ይፈልጉ እንደነበር ሲገልፅ እንዲህ ይላል፡- “እንግዲህ ሰንበትን ስለ ሻረ ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን ደግሞ ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር አስተካክሎ፦ እግዚአብሔር አባቴ ነው ስላለ፥ ስለዚህ አይሁድ ሊገድሉት አብዝተው ይፈልጉት ነበር” (ዮሐንስ 5፡18)፡፡

አሕመዲን ከሀኬተኛነታቸው የተነሳ ለማስረጃዎቹ ትኩረት ሳይሰጡ ክርስቲያኖችን ያለማስረጃ እንደሚናገሩ በማስመሰል መወንጀላቸው አስገራሚ ነው፡፡