ኢየሱስ ሟች ከሆንና አምላክ የማይሞት ከሆነ ኢየሱስ አምላክ እንዳልሆነ አያሳይምን?

 


65. ኢየሱስ መሞቱን ክርስቲያኖች ያምናሉ፡፡ አምላክ ግን እንደማይሞት እንደሚከተለው ተገልጿል፡፡ “የተባረከውና ብቻውን ገዥ የሆነው የነገሥታት ንጉሥ፣ የጌቶች ጌታ እግዚአብሔር በራሱ ጊዜ የሚያሳየው ነው፡፡ እርሱ ብቻ የማይሞት ነው፡፡ ሊቀረብ በማይችል ብርሃን ውስጥ ይኖራል፡፡ እርሱን ያየ ማንም የለም፡፡ ሊያየውም የሚችል የለም፡፡ ለእርሱ ክብርና ኃይል ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም ይሁን! አሜን፡፡” (1ኛ ጢሞቴዎስ 6፡16)፡፡ እንዲሁም “ብቻውን አምላክ ለሚሆን፣ ለማይሞተው ለማይታየውም ለዘመናት ንጉስ ምስጋናና ክብር እስከ ዘለዓለም ድረስ ይሁን፣ አሜን” (1ኛ ጢሞቴዎስ 1፡17)፡፡ ታዲያ ኢየሱስ ሟች ከሆንና አምልክ የማይሞት ከሆነ ኢየሱስ አምላክ እንዳልሆነ አያሳይምን? እንዲሁም “ብቻውን አምላክ ለሚሆን” ሲል ጥቅሱ አምላክ ብቸኛ እርሱም እግዜአብሔር መሆኑንና ኢየሱስ የሚባል ሌላ አምላክ እንደሌለ አያሳይምን?

የክርስቶስ መሞት አምላክ አለመሆኑን እንደማያሳይ እና እግዚአብሔር ኢ-ሟቲ መሆኑን ከሚናገሩት ጥቅሶች ጋር እንደማይጣረስ በቁጥር 8 ላይ ተብራርቷል፡፡ በተመሳሳይ ልዩ መሆንን የሚያመለክት የቋንቋ አጠቃቀም (Exclusive Language) አምላክነቱን ለማስተባበል የሙግት ግብአት እንደማይሆን በቁጥር 5 ላይ ስለተብራራ ራሳችንን መድገም አያስፈልገንም፡፡ በእርግጥ የግሪኩ በኩረ ጽሑፍ በጥልቀት ሲጠና 1ጢሞቴዎስ 6፡16 ላይ የሚገኘው ቃል ለክርስቶስ የተነገረ መሆኑን እንደሚያመለክት ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ሊቃውንት ይናገራሉ፡፡ በጥቅሱ ውስጥ የተዘረዘሩት ባሕርያት እርሱን የሚያመለክቱ መሆናቸውን ከሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች መረዳት ይቻላል (2ጢሞቴዎስ 1፡8-11፣ ራዕይ 17፡14፣ 19፡11-16፣ 1፡5 ይመልከቱ)፡፡ ለአሕመዲን ጀበል ብዙዎቹ ጥያቄዎች ምንጭ የሆኑትና የኢየሱስን አምላክነት የማይቀበሉት የይሖዋ ምስክሮች (አርዮሳውያን) እንኳ ሳይቀሩ በጽሑፎቻቸው ውስጥ ይህንን አምነው መቀበላቸውን ገልጸዋል፡፡[10] 1ጢሞቴዎስ 1፡17 ላይ የሚገኘው ደግሞ ለአሐዱ ሥሉስ የተነገረ አለመሆኑን እርግጠኛ ሊያደርገን የሚችል ምንም ነገር የለም፡፡ ኢየሱስ ከአብ እና ከመንፈስ ቅዱስ የተነጠለ ሌላ አምላክ ሳይሆን እንደ አብ እና እንደ መንፈስ ቅዱስ ሁሉ የአንዱ ግፃዌ መለኮት አካል ነው፡፡