መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ አንድ መሆኑን የሚያስተምር ከሆነ ኢየሱስ እንዴት አምላክ ይሆናል?

 


7. አምላክ አንድ ብቻ ከሆነ ኢየሱስ እንዴት አምላክ ሊሆን ይችላል? በሚከተሉት ጥቅሶች ላይ አምላክ አንድ ብቻ መሆኑ ተገልጿል፦ ሮሜ 3:30፣ 1ኛ ጢሞቴዎስ 2:5፣ ማርቆስ 12:32፣ ያዕቆብ 2:19፣ ሚልኪያስ 2:10፣ 1ቆሮንቶስ 8:6፣ ኤፌሶን 4:5-7 እና ዘዳግም 6:4-5፡፡ አምላክ አንድ ብቻ መሆኑን ከተስማማን በኋላም ግን ክርስቲያኖች ኢየሱስ አምላክ ነው ይላሉ፡፡ ለምንድን ነው ታድያ በ1ኛ ቆሮንቶስ 8:6 ላይ “አንድ አምላክ” የተባለው ኢየሱስ ሳይሆን አብ የሆነው? ታድያ ብቸኛው አምላክ አብ ከሆነ የኢየሱስ አምላክነት ምኑ ላይ ነው?

አሁንም ጸሐፊው በራሳቸው ንፅረተ ዓለም የነጠላ አሃዳዊነት መነፅር ነው ጥቅሶችን እየተረጎሙ የሚገኙት፡፡ ክርስቲያኖች በአንድ አምላክ ነው የሚያምኑት፡፡ የሥላሴ ትምህርት ልብ አምላክ አንድ ነው የሚል ነው፡፡ ነገር ግን ይህ አምላክ ሦስት አካላት አሉት፡፡ ሦስቱም የሥላሴ አካላት ብቸኛ አምላክ ተብለው መጠራታቸው ከሥላሴ ትንተና ጋር አብሮ የሚሄድ መሆኑን ለመረዳት ለጥያቄ ቁጥር 5 የተሰጠውን መልስ ይመልከቱ፡፡ እስኪ ጸሐፊው የጠቀሱት 1ቆሮንቶስ 8፡6 ላይ የሚገኘው ጥቅስ ሐሳባቸውን ይደግፍ እንደሆን እንመልከት፡፡ ጥቅሱ እንዲህ ይነበባል፡- “ለእኛስ ነገር ሁሉ ከእርሱ የሆነ እኛም ለእርሱ የሆንን አንድ አምላክ አብ አለን፥ ነገር ሁሉም በእርሱ በኩል የሆነ እኛም በእርሱ በኩል የሆንን አንድ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ አለን፡፡”

የጥቅሱ ሁለተኛ አጋማሽ የሁሉ ፈጣሪ የሆነ አንድ ጌታ ኢየሱስ መሆኑን ይናገራል፡፡ አብ አንድ አምላክ ስለተባለ ኢየሱስ አምላክ አይደለም ከተባለ በተመሳሳይ መንገድ ኢየሱስ የሁሉ ፈጣሪ አንድ ጌታ ስለተባለ አብ የሁሉ ፈጣሪና ጌታ አይደለም ሊባል ነውን? በፍፁም! ሐዋርያው ጳውሎስ አብንም ሆነ ወልድን አንድ አምላክ አንድ ጌታ ብሎ መጥራቱ የአንዱ ግፃዌ መለኮት አካላት መሆናቸውንና የተነጣጠሉ አለመሆናቸውን መረዳቱን ያመለክታል፡፡ ከዚህም በላይ ሐዋርያው ጳውሎስ ዘዳግም 6፡4 ላይ የሚገኘውን የአይሁድ ሼማ በሥላሴ አስተምህሮ መሠረት በመተርጎም ማቅረቡን የለዘብተኛ ሥነ መለኮት ምሑራን ሳይቀሩ ይስማሙበታል፡፡[4] “እስራኤል ሆይ፥ ስማ፤ አምላካችን እግዚአብሔር አንድ እግዚአብሔር ነው፡፡” “Hear, O Israel: The Lord our God is one Lord.” ይህ የሚያመለክተው አብ እና ወልድ የተለያዩ ሁለት አማልክት ወይም አንዱ ፈጣሪ አንዱ ፍጡር ሳይሆኑ የአንዱ ግፃዌ መለኮት (Godhead) አካላት መሆናቸውን ነው፡፡

 

 

ለአሕመዲን ጀበል 303 ጥያቄዎች የተሰጠ መልስ ማውጫ