ኢየሱስ አምላክ ከሆነ “ለወልድ በራሱ ሕይወት አንዲኖረው ሰጥቶታል” ለምን ይላል?

 


74. የአምላክ ሕልውና በማንም ላይ ጥገኛ አይደለም፡፡ አይሆንምም፡፡ በዮሐንስ ወንጌል 5:26 ላይ መጽሐፍ ቅዱስ “አብ በራሱ ሕይወት እንደለው እንዲሁ ደግሞ ለወልድ በራሱ ሕይወት እንዲኖረው ሰጥቶታል ፡፡፡” ይላል፡፡ ነገር ግን እንደዚህኛው ጥቅስ ገለጻ የኢየሱስ ህልውና በአብ (አምላክ) ላይ ጥገኛ ነው፡፡ “ለወልድ በራሱ ሕይወት አንዲኖረው ሰጥቶታል፡፡” ይላል፡፡ ወልድ ህልውና (ሕይወት) ያገኘው አብ ስለሰጠው ነው፡፡ የኢየሱስ ሕልውና በአብ ላይ ጥገኛ ነው፡፡ ኢየሱስ ያለ አብ በራሱ ህልውና ሊኖረው ካልቻለ እንዴት አምላክ ሊሰኝ ይችላል?

ይህ የኢየሱስን ዘለዓለማዊ መገኘት (Eternal Generation) የሚያመለክት በመሆኑ የሥላሴን አስተምህሮ የሚደግፍ ነው፡፡ በሥላሴ አስተምህሮ መሠረት ኢየሱስ በዘለዓለማዊ መገኘት ከአብ የተገኘ ነው፡፡ ለዚህ ነው የኒቅያ የሃይማኖት መግለጫ “ከአምላክ በተገኘው አምላክ፣ ከብርሃን በተገኘ ብርሃን፣ ከእውነትኛ አምላክ በተገኘ እውነተኛ አምላክ፣ በተፈጠረ ሳይሆን በተወለደ…” የሚሉ አንቀፆችን ያካተተው፡፡ የኢየሱስ ሕይወት ከአብ የተገኘ ነው፡፡ ይህ መገኘት ዘለዓለማዊና በጊዜ ያልተገደበ ሲሆን የኢየሱስን መለኮታዊ ባሕርይ ከአብ አያሳንስም፡፡ አብ ያሉት ባሕርያተ መለኮት ሁሉ ወልድም አሉት፡፡ እግዚአብሔርን በትክክል መግለፅ የሚችል ምሳሌ ባይኖርም የወልድን ዘለዓለማዊ መገኘት ለመረዳት ተከታዩ ምሳሌ ይረዳል፡፡ እስኪ በጊዜ ያልተገደበ ከዘለዓለም ዘመናት በፊት ሲያበራ የነበረ አንድ ኮከብ አስቡ፡፡ ብርሃኑ ኮከቡ በነበረበት ጊዜ ሁሉ አብሮት ነበር፡፡ ነገር ግን የኮከቡ ብርሃን ከኮከቡ የተገኘ ነው፡፡ ብርሃኑ ከሌለ ኮከብነቱ ይቀራል፡፡ ኮከቡ ከሌለ ብርሃኑም ሊኖር አይችልም፡፡ የአብ እና የኢየሱስ ቁርኝትም ልክ እንደዚሁ ነው፡፡ ለዚህ ነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱና አብ አንድ መሆናቸውን፤ እርሱን ያየ አብን ማየቱን እዲሁም እርሱ በአብ አብም ደግሞ በእርሱ እዳለ የተናገረው (ዮሐንስ 14፡9-11)፡፡ “አብ” እና “ወልድ” የሚሉት መጠርያዎች ይህንን ዘለዓለማዊ አንድነት የሚገልፁ ናቸው፡፡