መጽሐፍ ቅዱስ “አንድ አምላክ አብ አለን” ካለ ኢየሱስ እንዴት አምላክ ይሆናል?

 


78. በ1ኛ ቆሮቶስ 8:5-7 ላይ “መቼም ብዙ አማልክትና ብዙ ጌቶች አሉ፣ ነገር ግን በሰማይ ሆነ በምድርም ሆነ አማልክት የተባሉ ምንም ቢኖሩ ለእኛስ ነገሩ ሁሉ ከእርሱ የሆነ እኛም ለእርሱ የሆንን “አንድ አምላክ አብ አለን፣ ነገር ሁሉም በእርሱ በኩል የሆነ እኛም በእርሱ በኩል የሆንን አንድ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ አለን” ይላል፡፡ ይህን ጥቅስ ልብ ብለው ካስተዋሉ ክርስታኖች እንደሚሉት ከአንድ አምላክ ክፍል የሆኑ “አንድ ጌታ” እና “አንድ እግዚአሔር” አይልም፡፡ ነገር ግን ”አንድ አምላክ አብ” ነው የሚለው፡፡ ኢየሱስንም በዚህ አንዱ በተባለው አምላክ ውስጥ አልጨመረምውም፡፡ ለብቻው ነው “አንድ ጌታ” የሚለው፡፡

አሕመዲን በቁጥር 7 ላይ መልስ የሰጠንበትን ጥያቄ ነው የደገሙት፡፡ ጥያቄዎችን በመደጋገም ብዛታቸውን 303 ለማድረስ የፈለጉ ነው የሚመስሉት፡፡ ሐዋርያው ስለ እግዚአብሔር አንድነት አጥብቆ የሚያስተምረው የአይሁድ ሼማ (ዘዳግም 6፡4) አብ እና ወልድን እንደሚያመለክት እያስተማረ ነው (መልስ ቁጥር 7 እና የግርጌ ማስታወሻውን ይመልከቱ)፡፡ የመልዕክቱ ተደራሲያን ይህንን እውነታ ስለሚያውቁ ሐዋርያው አሕመዲን የተናገሩት ዓይነት ሐተታ ውስጥ መግባት አላሻውም፡፡

እንዲህ ሲሉ ጥያቄያቸውን ይቀጥላሉ፡- ይህ ጌትነት አምለክ ውስጥ ካልተጠራ እንዴት ጌታ ከተባሉ ሌሎች ግለሰቦች ለይተን ኢየሱስን “አምላክ” ልንለው ይቻለናል? “ጌታ” እና “እግዚአብሔር” ማለት አንድ ቢሆኑ ለምንድነው በመጽሐፍ ቅዱስ በበርካታ ስፍራ ሰዎች ኢየሱስን “ጌታ” ሲሉት አንድም ጊዜ “እግዚአብሔር” አልያም “እግዚአብሔ አብ” እንደሚባል ”እግዚአብሔር ወልድ/ኢየሱስ” የልተባለው? ካልሆነ ለምንደነው አብ፣ ወልድ እና መንፈስ ቅዱስ በአንድነት በአንዱ አምላክ “እግዚአብሔር” ውስጥ ተካተው ወልድን ያልገለጹት?

የኢየሱስ ጌትነት እንደ ሌሎች ሰዎች ጌትነት የማይሆንበት እና አምላክነቱን የሚያሳይበት ምክንያት አሕመዲን በጠቀሱት በዚያው ክፍል ውስጥ ተነግሯል፡፡ ብዙ ጌቶች የተባሉ ፍጥረታት ቢኖሩም ነገር ግን ኢየሱስ ከእነርሱ የተለየ ብቸኛ ጌታ ነው፡፡ ብቸኛ ጌታ ተብሎ ሊጠራ የሚችለው ፈጣሪ ብቻ መሆኑን አሕመዲንም ሆኑ ሌሎች ሙስሊሞች የሚክዱ አይመስለኝም፡፡ ታድያ ኢየሱስ ብቸኛ ጌታ ተብሎ እያለ ከሌሎች ጌቶች ለይተን አናየውም ማለት ምን የሚሉት አማርኛ ነው? ኢየሱስ እግዚአብሔር አልተባለም የሚለው የጠያቂያችን አባባል ምን ያህል ከመጽሐፍ ቅዱስ የራቁና የተለቃቀሙ ጥቅሶችን ብቻ የሚያነቡ መሆናቸውን የሚያመለክት ነው፡፡ ኢየሱስ በብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ውስጥ አምላክ/ እግዚአብሔር ተብሎ ስለመጠራቱ ተከታዮቹን ጥቅሶች ማየት ይቻላል፡- (ዮሐንስ 1፡1-3፣ 20፡28፣ የሐዋርያት ሥራ 20፡28፣ ሮሜ 9፡5፣ ቲቶ 2፡13፣ 2ጴጥሮስ 1፡1፣ 1ዮሐንስ 5፡20)፡፡ አብ፣ ወልድ እና መንፈስ ቅዱስ በአንድነት አንዱን ግፃዌ መለኮት ይገልፃሉ እንጂ አሕመዲን እንዳሉት አንዱን የሥላሴ አካል አይገልፁም፡፡ ይህንን ጥያቄ ከምን አኳያ እንደጠየቁ ለእሳቸውም ግልፅ የሆነ አይመስልም፡፡