ኢየሱስን የገረዙት ሰዎች ሲገርዙት “የዓለምን ፈጣሪ ኃያሉን አምላክ ገረዝን” ብለዉ ነበር ያሰቡት?

 


83.የሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 2 ቁጥር 21 ላይ “ሊገርዙት ስምንት ቀን በሞላ ጊዜ፥ በማኅፀን ሳይረገዝ በመልአኩ እንደ ተባለ፥ ስሙ ኢየሱስ ተብሎ ተጠራ” ይላል፡፡ ኢየሱስን የገረዙት ሰዎች ሲገርዙት “የዓለምን ፈጣሪ ኃያሉን አምላክ ገረዝን” ብለዉ ነበር ያሰቡት? እንደ ክርስቲያኖች እምነት አምላክ የኢየሱስን ስጋ ተዋህዶታል፡፡ ያቺ በግርዛት የተቆረጠችዉ የኢየሱስ ቁራጭ ስጋስ የአምላክ ቁራጭ ልትሆን?

ጌታችን ፍፁም ሰው ሆኖ ወደ ምድር በመምጣቱ ምክንያት ከኃጢአት በስተቀር እንደ እኛው ሰው ነበር፡፡ ያ ባይሆን ኖሮ ቤዛችን በመሆን የኃጢአት እዳችንን ለመክፈል ባልቻለም ነበር፡፡ ከሕግ በታች እንደመወለዱ እና የአብርሃም ዘር እንደመሆኑ መጠን መገረዝ አስፈልጎታል፡፡ በስምንተኛው ቀን የገረዙት ሰዎች ማንነቱን ማወቅ አለማወቃቸው ማንነቱን ስለማይለውጥ ጠያቂያችንን ሊያሳስባቸው አይገባም፡፡ የሰው ሥጋ ቁራጭ የነፍሱ ቁራጭ እንዳልሆነው ሁሉ የኢየሱስም የሥጋው ቁራጭ የመለኮቱ ቁራጭ አይደለም፡፡