ዮሐንስ 1፡1 “በመጀመሪያ” ሲባል የምን መጀመሪያ? ለመሆኑ አምላክ መጀመሪያ አለውን?

 


95. ዮሐንስ 1፡1 የኢየሱስን “አምላክነት” ይገልፃል ብለው ያምናሉን?“በመጀመሪያ ቃል ነበር፡፡ ቃልም እግዚያብሔር ዘንድ ነበር፡፡ ቃልም እግዚያብሔር ነበር” ይላል፡፡ “እርሱም በመጀመሪያ ከእግዚአብሔር ጋር ነበር፡፡” (ዮሐንስ 1:2)

ሀ) “በመጀመሪያ” ሲባል የምን መጀመሪያ? ለመሆኑ አምላክ መጀመሪያ አለውን? እንዴት “በመጀመሪያ” ይባላል? ዘለዓለማዊ አይደለምን?

ጠያቂው ጥቅሶችን በትክክል ያለማንበብ ችግር በእጅጉ ይስተዋልባቸዋል፡፡ በመጀመርያ፣ ማለትም መጀመርያ የተባለው ቅፅበት ሲፈጠር ቃል ነበረ፡፡ ቃል በመጀመርያ ወደ መኖር የመጣ ሳይሆን በመጀመርያ የነበረ ነው፡፡ ይህ ቃል ጊዜና ቦታን (Time and Space) ጨምሮ የሁሉ ፈጣሪ በመሆኑ (ቁ.3) ለመኖር ጊዜና ቦታ አያስፈልገውም፡፡ ይህ ባሕርይ ደግሞ የአምላክ እንጂ የሌላ ሊሆን አይችልም፡፡

ለ) “የአምላክ ቃል” የሚባለው ኢየሱስ ክርስቲያኖች እንደ ሚሉት “ዘለዓለማዊ ነው” ከተባለ እንዴት “መጀመሪያ” ይኖረዋል?

በዚህ ቦታ ኢየሱስ በመጀመርያ እንደነበረ እንጂ መጀመርያ እንደነበረው አልተጻፈም፡፡ ጠያቂው አንብቦ የመረዳት ችሎታቸው ደካማ ነው፡፡

ሐ) በዮሐንስ 1:1 በሦስተኛው ዐረፍተ ነገር ቃልና እግዚአብሔር አንድ መሆናቸውን ተነግሮናል፤ ቃል በሚለው ምትክ “እግዚአብሔር”ን ብንተካ “በመጀመሪያ” እግዚአብሔር ነበር፤ እግዚአብሔርም እግዚአብሔር ዘንድ ነበር፤ እግዚአብሔርም እግዚአብሔር ነበር” ይሆናል፡፡ የትኛው እግዚአብሔር ነው እግዚአብሔር ዘንድ የነበረው? አእምሮ መጠቀም አይሻልምን? ኧረ እባካችሁ እናስብ!!

አሕመዲን ኧረ ባክዎትን ከሐዋርያት፣ ከቅዱሳን አባቶች፣ በየዘመናቱ ከኖሩት ክርስቲያን ሊቃውንት እና ከመላው ሕዝበ ክርስቲያን ይልቅ እርስዎ የተሻለ የማሰብ ችሎታ እንዳሎት በማስመሰል አይንጠባረሩ! ያልገባዎትንና ልክ ያልመሰልዎትን ነገር በትህትና ከመጠየቅ ይልቅ ራስዎን ብቻ አሳቢ ሌላውን ማሰብ የተሳነው ማስመሰሉ ለምን አስፈለገ? የዚህች የተለመደች የአላዋቂዎች ስላቅ ምንጭ እንኳ እርስዎ እንዳልሆኑ ጠንቅቀን እናውቃለን፡፡

ሐዋርያው እየተናገረ ያለው ከሥላሴ አካላት መካከል ስለ ሁለቱ ሲሆን ሁለቱንም “እግዚአብሔር ብሎ መጥራቱ የሚያመለክተው አብ እና ወልድ በመለኮት አንድ በአካል ግን ልዩ መሆናቸውን ነው፡፡ ጥቅሱ እየተናገረ ያለው እግዚአብሔር ወልድ ከእግዚአብሔር አብ ጋር ስለመኖሩ ነው፡፡ ከአሕመዲን በስተቀር ይህንን ሐቅ ሊስት የሚችል አሳቢ አዕምሮ ያለው ሰው ሊኖር አይችልም፡፡