በኢየሱስ መስዋዕት የሴቶች የወሊድ እርግማን ለምን አልተነሳም?

 


99. ሔዋን የተከለከለችውን ዛፍ በመብላቷ አምላክ ቅጣት አዘዘባት፡፡ በወሊድ ጊዜ በስቃይ ትወልድ ዘንድ፡፡ ዘፍጥረት 3:16 “ሴቲቱንም እንዲህ አላት፤ በምጥ ጊዜ ጭንቅሽን አበዛለሁ፤ በሥቃይም ትወልጃለሽ፤ ፍላጎትሽም ወደ ባልሽ ይሆናል ፤ እርሱም የበላይሽ ይሆናል” ይላል፡፡ በዚህ ጥቅስ ላይ የክርስቲያን ምሁራን እዲህ ሲሉ ማብራርያ ጽፈዋል ፦ “ሔዋንና ሴቶች ተፈረደባቸው፡፡ ከዚህ የተነሳ ልጅ መውለድ አስጨናቂ ሂደት ሆነ፡፡ ሴቶች ከባሎቻቸው ጋር የነበራቸው የእኩልነት ግንኙነት ተለውጦ ለባሎቻቸው የሚገዙ ሆኑ ፡፡” (ቲሞ ፌሎስ፣ የብሉይ ኪዳን የጥናት መምህርና ማብራርያ 1ኛ መፅሐፍ ገፅ 126)፡፡ እንደ ክርስትና እምነት አዳምና ሔዋን ባጠፉት ጥፍት ምክኒያት የደረሠባቸውን ኃጢአት (“የውርሥ”) ኢየሱስ መስዕዋት ሆኖ በደሙ ከዝርያቸው ላይ አንጽቷል፡፡ ይህ አስተምሕሮት እውነት ከሆነ ታድያ በዚያው ጥፋት ምክንያት ሔዋን ላይ የተጣለው (ጭንቅና ስቃይ) አሁንም ለምን ቀጠለ? ወይንስ “ኢየሱስ ለኛ ሲል ቤዛ ሆነ” የሚባለው ሀሰት ነው?

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ኃጢአታችን በመስቀል ላይ ቤዛ ሆኖ ዕዳችንን ከፍሎልናል፡፡ ይህ ማለት ግን በዚህች ምድር ላይ እስካለን ድረስ በሰው ውድቀት ምክንያት ከመጡት መከራዎች እና ህመሞች ነፃ እንሆናለን ማለት አይደለም፡፡ መዳናችን የሚገለጠው በዳግመኛ ምፅኣቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲመለስ ሲሆን ያኔ ከዚህች ዓለም ስቃይ እንገላገላለን፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ ያላመኑት ሰዎች በመጪው ዓለም ስቃያቸው እጅግ በዝቶ ከእግዚአብሔር ፍርድ በታች የሚኖሩ ሲሆኑ አማኞች ግን ከየትኛውም ስቃይ ነፃ በመሆን ወደ ዘለዓለም ፍስሐ ይሄዳሉ (ሮሜ 8፡18-25፣ ራዕይ 21፡4)፡፡

ስለዚህ ክርስቶስ የኃጢአት ዕዳችንን ሁሉ በመክፈል በውርስ ኃጢአት ከመጡት ሥቃዮች ሁሉ አድኖናል ነገር ግን ይህ መዳናችን እውን የሚሆነው በትንሣኤ ወቅት የሚሞተው ሥጋችን ተለውጦ የማይሞተውን ሲለብስ ነው፡፡ እስከዚያው ድረስ ግን በዚህች ምድር ላይ የምናሳልፋቸው የትኞቹም መከራዎች ወደ እግዚአብሔር ይበልጥ የሚያቀርቡንና መጪውን ተስፋችንን በናፍቆት እንድንጠባበቅ የሚያደርጉን አጋጣሚዎች እንደሆኑ በመቁጠር ሳናጉረመርም የጌታችንን መገለጥ ተስፋ እናደርጋለን፡፡

ቁርኣን የመጀመርያዎቹ ሰዎች ኃጢአትን ከሰሩ በኋላ ከገነት እንደተባረሩና አላህን ይቅርታ በመጠየቃቸው ምክንያት ይቅር እንደተባሉ ይናገራል (ሱራ 2፡37)፡፡ ታድያ የኃጢአታቸውን ይቅርታ ከተቀበሉ ለምን እስካሁን ድረስ የሰው ልጆች በሥቃይ ውስጥ ይኖራሉ? ወደተባረሩባትስ ገነት እንዲመለሱ ለምን አልተፈቀደላቸውም?